Saturday, June 30, 2012

ስምህ


 ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! መንፈሳዊ ምስጋና ሁሉ ለአንተ ይገባል፡፡ ዋጋው የማይታወቅ ነጋዴ ገንዘቡን ሁሉ ሰጥቶ የተወዳጀው እውነተኛ ዕንቁ ደንጊያ አንተ ነህ፡፡ ይህንን የዕንቁ ደንጊያ በሰውነታችን ውስጥ ያበራ ዘንድ ደግሞ ዛሬ ለእኛ አድርግልን፡፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የተቀደሰው ስምህ የልባችን ደስታ የሰውነታችን ሽልማት ጌጥ ነው፡፡

Friday, June 29, 2012

ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ለ2004 ዓ.ም. ተመራቂ ደቀ መዛሙርት ያስተላለፉት አባታዊ መልእክት!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
የዘማናችሁን ዐሥራት ሳይሆን መላ ዕድሜአችሁን ለወንጌል አገልግሎት የሰጣችሁ፣ ዘመናዊውን ዓለም ተላምዳችሁ ዘመናውያን ሰዎች ለመሆን ሳይሆን መንፈሳዊውን ዕውቀት ቀስማችሁ የዓለም ብርሃን ለመሆን በመንፈሳውያን ኰሌጆች ውስጥ እየተማራችሁ የምትገኙና የትምህርታችሁን የመጀመርያው ምዕራፍ አጠናቃችሁ በእግዚአብሔር ስም ልትመረቁ የበቃችሁ የተወደዳችሁ ልጆቼ! በፍቅሩ ቅመም አልጫውን ምድር ባጣፈጠው፣ ጨለማውን ዓለም በቃሉ ባበራው በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰላም እላችኋለሁ፡፡

የተወደዳችሁ ልጆቼ! እግዚአብሔር አምላካችን የአንድ ቀንን መታመን የማይረሳ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔርን ለማገልገል ብቁዎች መሆን አለብን ብላችሁ ወደ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የመጣችሁበትን የአንዷን ቀን ፍቅራችሁን የሚያስብ አምላክ ነው፡፡ ምንም እንኳን የጓዳውና የቤቱ ሥራ አስፈላጊና የማይታለፍ ቢሆንም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ከማርታ ይልቅ በማርያም ደስ ተሰኝቷል፡፡ ማርታ ያላትን ለትልቁ እንግዳ ልታቀርብ ባለቤቱን ጌታ እንደ እንግዳ ቆጥራ መባረክን ጀመረች፡፡ ማርያም ግን በቤቷም የሚያስተናግዳትን፣ የታዛዋ ብቻ ሳይሆን የሕይወቷም ራስ የሆነውን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ልታደምጥ ከእግሩ ሥር ቁጭ አለች /ሉቃ.10፡38-42/፡፡ ጌታችን ለእርሱ ከማድረጋችን በፊት ያደረገልንን፣ ስለ እርሱ ከመናገራችን በፊት የነገረንን እንድናስተውል ይፈልጋል፡፡ የማርታ እኅት ማርያም ይህን የተረዳች ትመስላለች፡፡ እናንተም ደቀ መዛሙርት ያሳለፋችኋቸው ዓመታት ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብላችሁ ድምፁን የሰማችሁበት ዓመታት ናቸውና ደስ ይበላችሁ! ምንም እንኳን የዘወትር ትካዜአችን እንደ ቃሉ መኖር አለመቻል ቢሆንም በቃሉ የመኖርን ኃይል በንስሐና በጸሎት ልንለምን ይገባናል፡፡

  የተወደዳችሁ ደቀ መዛሙርት ልጆቼ! እስከ ዛሬ የሚታሰብላችሁ ልጆች ነበራችሁ፡፡ ዛሬ ግን የምታስቡ ወላጆች እንድትሆኑ ለወንጌል ሙሽራይት ቤተ ክርስቲያን ትድራችኋለች፡፡ በዘመናት ሁሉ እንደታየው ወንጌል ዝም ማለት የማትወድ ናት፡፡ ወንጌልም መክና አታውቅም፡፡ የወንጌል የማጌጫ ዘውዷ አክሊለ ሦክ፣ የሥልጣን ዘንጓም መስቀል፣ መገለጫዋም መገፋት ነው፡፡ የማትገድለው ወንጌል ለሰማዕትነት የጨከነች ናትና አዲሱ ኑሮአችሁን ቤተ ክርስቲያን ትመርቃለች፡፡

የተወደዳችሁ ልጆቼ! ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ለሦስት ዓመታት ከሦስት ወራት ያህል ካስተማራቸው በኋላ በኃይለ መንፈስ ቅዱስ ከልሎ ወደ ዓለም ልኳቸዋል፡፡ እናንተም ላለፉት ዓመታት የደቀ መዝሙርነት ትምህርታችሁን ተከታትላችኋል፡፡ ትምህርታችሁን በሞገስ ለሕዝብ እንዲደርስ የመንፈስ ቅዱስ ኃይል የምታገኙት በጽሞናና በጸሎት በመቆየት ነው /ሉቃ.24፡49/፡፡ ቤተ ክርስቲያን እናንተን መምህራን አድርጋ ሳይሆን ደቀ መዛሙርት አድርጋ መርቃለች፡፡ ስለዚህ የሁል ጊዜ ተማሪዎች እንደሆናችሁ፣ ትምህርቱም የማያልቅ መሆኑን ልትገነዘቡ ይገባችኋል፡፡

  የተወደዳችሁ ልጆቼ! ምንም ብታስተምሩ፣ ምንም ብትጽፉ ዓለም አበባ ይዛ እንደማትቀበላችሁ እወቁ፡፡ ይህ በእናንተ የተጀመረ ሳይሆን የዓለም መገለጫዋ መሆኑን አትዘንጉ፡፡ ልዩ ልዩ ነቀፋና ስደት ሲመጣባችሁ ከዓለም እንደተጣላችሁ አትቁጠሩት፡፡ እንዲያውም ከዓለም ጋር እንደተዋወቃችሁ ቁጠሩት፡፡ ዓለም እንደዚህ ናትና፡፡ ጎበዝ የሚባለው ሳይቀር በመገፋት ውስጥ በኀዘን ይጐዳል፡፡ የሚታይ ተስፋ እያጣም በብቸኝነት ይንገላታል፡፡ ይሁንና ሰው መተማመኛ የማይሆን የሸምበቆ ምርኩዝ መሆኑን ቃሉ ይነግረናል /ኢሳ.36፡6/፡፡ ስለዚህ በሁሉም ነገር ውስጥ የጠራችሁን ጌታ ክርስቶስን ተመልከቱ /ዕብ.3፡1/፡፡ የተቀበላችሁትን ለመስጠት ብቻ ሳይሆን ያልተቀበላችሁትንም ለመስጠት ፈቃደኞች ሁኑ፡፡ ፍቅርን አላያችሁ ከሆነ ከእናንተ ይልቅ የፍቅርን ረሀብ የሚያውቅ የለምና ፍቅርን ስጡ፡፡ የሚያዝንላችሁ አባት አላገኛችሁ እንደሆነ ለሚጠጓችሁ እናንተ ደግሞ አዛኝ አባቶች ሁኑ፡፡ ተራራውን ስትጨርሱ መስክ እንደሚያጋጥማችሁ እያሰባችሁ በተራራው አትዘኑ፡፡ እናንተ ዱር መንጣሪዎች ናችሁና የተመቸ ቦታን ፍጠሩ እንጂ ምቹ ቦታን አትጠብቁ፡፡ የደረሰባችሁ ችግርም እስከ ዕድሜአችሁ ፍጻሜ የምትናገሩትን ትምህርት ይሰጣችኋልና አትበሳጩ፡፡ ከምትፈልጉት ነገር ይልቅ ያገኛችሁት ይበልጣል፤ እርሱም የሰማይ ዜጐች መሆናችሁ ነውና ደስ ይበላችሁ!

የተወደዳችሁ ልጆቼ! እግዚአብሔር የሚባርከው አሳባችሁን ሳይሆን ቃል ኪዳናችሁን ነውና አገልግሎታችሁን በቃል ኪዳን ያዙ፡፡ መጽናናትን የሚሹ ብዙዎች ኀዘንተኞች፣ በማዕበል የሚንገላቱ ብዙዎች ደካሞች እየጠበቋችሁ ነውና ፍጠኑ፡፡ እናንተን ኑ ለማለት አቅም የሌላቸው ብዙ አሉና ሳይጠሯችሁ ሂዱ፤ ወንጌል ሀገሯ እስከ ምድር ዳርቻ ነውና፡፡ ዘመናዊነትና ሥልጣኔ የማይሞላው የሕይወትን ክፍተት በወንጌል የምትሞሉ እናንተ ናችሁ፡፡ የያዛችሁት እንደ ቀላል አትቁጠሩት፡፡ የዓለምን ኃይልና ዕውቀት ሁሉ የምትማርኩ የዕውነት ዘማቾች ናችሁ፡፡ እንደማይፈለግ ሰው ራሳችሁን አትቁጠሩት፡፡ የሞተላችሁ ጌታ ውበቱ የማያረጅ፣ ዛሬም ያደመቃችሁ እርሱ ነው፡፡

የተወደዳችሁ ልጆቼ! ዋጋችሁ በሰማያት እንደሆነ እያሰባችሁ በትንንሽ የምድር ዋጋ ክብራችሁን እንዳትጥሉ ተጠንቀቁ፡፡ እኔም በጸሎትና በአባታዊ ፍቅር ከእናንተ ጋር ነኝ፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በሰማያዊና በምድራዊ በረከቱ ይባርካችሁ! ዛሬ እንደ ያዕቆብ በሌጣ ወጥታችሁ፣ ለከርሞ ግን በብዙ ፍሬ ይመልሳችሁ! እግዚአብሔር አገልግሎታችሁን ይባርክ! የቅድስተ ቅዱሳን የድንግል ማርያም ልጅ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አገራችን ኢትዮጵያን ይባርክ!”
      

የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ- የዮሐንስ ወንጌል የ29ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.6፡22-40)!



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
“በነገው” ማለትም ኅብስቱን አበርክቶ ከሰጣቸው በኋላ፤ ደቀ መዛሙርቱን ወደ ቅፍርናሆም እንዲሻገሩ ግድ ካላቸው በኋላ፤ እርሱም ወደ ተራራ ፈቀቅ ብሎ ቆይቶ በማዕበሉ ላይ እየተረገጠ የጌንሴረጥ ዕጣ ወደ ምትሆን ወደ ቅፍርናሆም ከተሻገረ በኋላበባሕር  ማዶ” ማለትም ገና ወደ ቅፍርናሆም ሳይሻገሩቆመው የነበሩ ሕዝቡ ከአንዲት ጀልባ በቀር በዚያ ሌላ ጀልባ እንዳልነበረች” ተመለከቱ፡፡ ግራ ገባቸው፡፡ ጌታችን በዚያ የለም፡፡ “ደቀ መዛሙርቱም ለብቻቸው እንደ ሄዱ እንጂ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ ታንኳይቱ እንዳልገባ” አስተውለዋል /ቁ.22/፡፡  ይህ የእነርሱ ግራ መጋባት በምክንያት የተደረገ ነበር፡፡ ጌታችን ማዕበሉን እየተረገጠ መሻገሩ በግልጽ ሳይሆን በጭላንጭል እንዲያውቁ የተደረገ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ “ሌሎች ጀልባዎች ጌታ የባረከውን እንጀራ ወደ በሉበት ስፍራ አጠገብ ከጥብርያዶስ መጡ፡፡ ሕዝቡም ኢየሱስ ወይም ደቀ መዛሙርቱ በዚያ እንዳልነበሩ ባዩ ጊዜ ሳቸው በጀልባዎቹ ገብተው ኢየሱስን እየፈለጉ ወደ ቅፍርናሆም መጡ” /ቁ.23-24/። ጌታችንን አገኙት፡፡ አሁን ጥያቄው “ጌታ እንዴት ተሻገረ? በእግሩ ነውን?” የሚል መሆን ነበረበት፡፡ ምክንያቱም “በጀልባ ነዋ!” እንዳንል ወንጌላዊው “ደቀ መዛሙርቱ ከተሳፈሩባት ውጪ ሌላ ጀልባ አልነበረችም፤ መዛሙርቱም ለብቻቸው እንደ ሄዱ እንጂ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ ታንኳይቱ እንዳልገባ አዩ” ብሎናልና፡፡ “ታድያ እንዴት ተሻገረ?” ሕዝቡ ይህን ሊጠይቁ በተገባ ነበር፡፡ ሆኖም ግን አመጣጣቸው ለሌላ፤ የጌታችንን ጌትነት በማመን ሳይሆን ስለ ሌላ ዓላማ ነበርና መጠየቅስ ይቅርና አላሰቡትምም፡፡ ለዚህም ነው በባሕር ማዶ ሲያገኙትመምህር ሆይ! ባሕሩን እንዴት ተሻገርክ?” ሳይሆን “መምህር ሆይ፥ ወደዚህ መቼ መጣህ?” የሚሉት /ቁ.25/። ምን ያህል ወላዋይ እንደሆኑ እናስተውል፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ጌታችን ኅብስቱን አበርክቶ ሲሰጣቸውና ሲጠግቡ “ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣ ነቢይ ነው” ብለው ሲገረሙ ነበር፡፡ ከዚህም በላይ ነጥቀው ሊያነግሡት ሽተው ነበር፡፡ አሁን ግን እንደከዚህ በፊቱ አይደነቁም፡፡ አስቀድመን እንደተነጋገርነው ጌታችንን የሚፈልጉት ስለ በሉና ስለ ጠገቡ እንጂ ምልክትን ስላዩ አይደለምና /ቁ.26፣ Saint John Chrysostom Homilies on St. John, Hom.43:l./፡፡
 ሰው አፍቃሪው ጌታ ግን “እናንተ የሆድ ባርያዎች፤ እናንተ ሆድ አምላከቸው እስከ መቼ ድረስ እታገሣችኋለሁ?“ አይላቸውም፡፡ ይልቁንም እነርሱን በሚያቀርብ ጥበባዊ አነጋገር፡-ለሚጠፋ መብል አትሥሩ፤ ነገር ግን ለዘላለም ሕይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ሥሩ፤ እርሱን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና” ይላቸዋል እንጂ /ቁ.27/።  እንዲህ ማለቱ ነበር፡- “ልጆቼ! አመጣጣችሁ ምድራዊ መብልን ብቻ በመሻት አይሁን፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ ክርስቶስ ለሚሰጣችሁ ደግሞም ለሚበልጠውና የዘላለምን ሕይወት ለሚሰጠው ለማያልፈው ምግብ እንጂ፡፡ አባታችን የምትሉት እግዚአብሔር አብ የእኔም የባሕርይ አባቴ ይህን ሰማያዊ መና እሰጣችሁ ዘንድ ልኮኛልና፤ ሾሞኛልና፤ አትሞኛልና /መዝ.45፡7/፡፡ ስለዚህ አስቀድማችሁ ኃላፊ ጠፊ የሚሆን መብልን ሳይሆን የዘላለምን ሕይወት የሚሰጥ መብልን ፈልጉ፤ ይህም ይጨመርላችኋል /ማቴ.6፡34/፡፡ እንዲህም ብዬ ስነግራችሁም ግራ የምትጋቡ አትሁኑ፡፡ እኔ የሰው ልጅ ስሆን እንደ እናንተ ዕሩቅ ብእሲ (ፍጡር) አይደለሁምና /ማቴ.16፡16/፡፡ ስለዚህ እኔ የምሰጣችሁ እንጀራ ሌላ ሰው እንደሚሰጣችሁ አይደለምና ይህን የማያልፈው መብል እሰጣችሁ ዘንድ ለምኑ” /St. Augustine: On the Gospel of St. John, tractate 25:11./፡፡
    እነርሱ ግን አሁንም በውስጣቸው የሚፈልጉት ያን ምድራዊ መብል ስለሆነ  እንግዲህ  የእግዚአብሔርን ሥራ (እግዚአብሔር የሚወደውን ሥራ) እንድንሠራ ምን እናድርግ? አሉት /ቁ.28/።  ጌታም፡-ይህ የእግዚአብሔር ሥራ (እግዚአብሔር የሚወደው ሥራማ) እርሱ (አባቴ) በላከው (በእኔ) እንድታምኑ ነው” አላቸው /ቁ.29/። እነርሱ ግን አስቀድመን እንደተነጋገርነው አመጣጣቸው በጌትነቱ ለማመን ስላልነበረ ከአንድ ቀን በፊት የተደረገውን ምልክት (ተአምር) ረሱትና እንኪያ አይተን እንድናምንህ አንተ ምን ምልክት ታደርጋለህ? ምንስ ትሠራለህ? ይበሉ ዘንድ ከሰማይ እንጀራ ሰጣቸው ተብሎ እንደ ተጻፈ ቀድሞ አባቶቻችን በምድረ በዳ መናውን ተመግበዋልና” አሉት /ቁ.30-31/። እንዲህ ማለታቸው ነበር፡-“በእውነት አንተ አባታችን ሙሴ ይመጣል ብሎ የነገረን ነቢይ ከሆንክ እናምንብህም ዘንድ እርሱ ከሰማይ መና አውርዶ እንደመገባቸው ከደረቅ ዓለትም ውኋውን አፍልቆ እንዳጠጣቸው ለእኛም አድርግልን፤ እንዲህ ካልሆነ ግን እናምንብህ ዘንድ አይቻለንም፤ የምትነግረንን ለመስማትም ጀሮአችን ድፍን ነው፡፡” /St. Ephrem the Syrian, Commentary on Tatian’s Diatessaron, 12:10/፡፡

  እንደነርሱ ሐሳብ ሙሴ ካደረገው የበለጠ ተአምር እንደሌለ በእርጠኝነት ይናገሩ ነበር፡፡ ጌታችን ግን እንደ ልማዱ ሰዎቹን ቀስ በቀስ ወደ እርሱ ያቀርባቸው ዘንድ ወድዶ በአንድ ጊዜ “እኔ ከሙሴ እበልጣለሁ” አይላቸውም፡፡ “እበልጣለሁ” ቢላቸው ምን ያህል ለቁጣ የፈጠኑ እንደሆኑ ያውቃቸዋልና፡፡ ስለዚህ ንግግሩን ሙሴ የተነገረለትን ታላቅ ተአምራት እንዲሠራ ወደ አስቻለው ምንጭ መለሳቸው፡፡ እንዲህም አላቸው፡- “በእናንተ ሐሳብ እስማማለሁ፡፡ ሙሴ ታላላቅ ተአምራትን አድርጓል፡፡ ነገር ግን እንደ እግዚአብሔር አገልጋይ እንጂ በራሱ ኃይልና ሥልጣን መናን መስጠት ውኃን ከዓለት ማፍለቅ የሚችል አልነበረም፡፡ እግዚአብሔርን በሰማያት ማን ይተካከለዋል? ከአማልክትስ ልጆች እግዚአብሔርን ማን ይመስለዋል? /መዝ.89፡6/ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እውነተኛ እንጀራ ከሰማይ የሚሰጣችሁ አባቴ ነው እንጂ ከሰማይ እንጀራ የሰጣችሁ ሙሴ አይደለም፡፡ ያም ቢሆን የተሰጠው መና ሊመጣ ላለው እኔም ለምሰጣችሁ ለአማናዊው መና ጥላ ነበር፡፡ ከዚያ መና የተመገቡ ሰዎች ከዚያ ውኃ የጠጡ ወገኖች እንደገና ተርበዋልና፤ እንደገና በውኃ ጥም ተይዘዋልና፡፡ ስጦታው ጊዜአዊ ችግርን የፈታ እንጂ ዘለአለማዊ ደኅንነትን የሰጣችሁ አይደለም፡፡ አማናዊው የእግዚአብሔር እንጀራከሰማይ የሚወርድ (ደግሞም ለእስራኤል ዘሥጋ ብቻ ሳይሆን) ለዓለም (ለሰው ልጅ ሁሉ) ሕይወትን የሚሰጥ ነው” አላቸው /St. Cyril of Alexandria, Commentary on the Gospel Of John 3፡6/።  
  አሁንም በዚሁ ምድራዊ አስተሳሰብ ይንፏቀቃሉ፡፡ ስለ መንፈሳዊው መብል ቢነግራቸውም ስለ ሥጋዊ መብል የነገራቸው ስለመሰላቸው፡-ጌታ ሆይ፥ ይህን እንጀራ ዘወትር ስጠን” ሉታልና /ቁ.34/።  ጌታ ግን እንዲህ ሲል መለሰላቸው፡-የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም። ነገር ግን አይታችሁኝ እንዳላመናችሁ አልኋችሁ። አብ የሚሰጠኝ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፥ ወደ እኔም የሚመጣውን ከቶ ወደ ውጭ አላወጣውም፤ ፈቃዴን ለማድረግ አይደለም እንጂ የላከኝን ፈቃድ ለማድረግ ከሰማይ ወርጃለሁና። ከሰጠኝም ሁሉ አንድን ስንኳ እንዳላጠፋ በመጨረሻው ቀን እንዳስነሣው እንጂ የላከኝ የአብ ፈቃድ ይህ ነው። ልጅንም አይቶ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወትን እንዲያገኝ የአባቴ ፈቃድ ይህ ነው፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ”።  እንዲህ ማለቱ ነበር፡- “ልጆቼ! አሁንም የምትጠይቁኝ ተራና ሥጋዊ መብል ነው፡፡ አስቀድሜ እንደነገርኳችሁ ያ ሥጋዊ መብል ጊዜአዊ ችግርን የፈታ እንጂ ዘላለማዊ ደኅንነትን የሰጣችሁ አይደለም፡፡ ወደ እኔ የሚመጣ ግን እንደገና አይራብም፤ በእኔም የሚያምን ዳግመኛ አይጠማም፡፡ የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝና፤ በእኔ ፈቃድ በአባቴ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ስለ ሰው ልጆች ሰው የሆንኩኝ ሰማያዊ እንጀራ እኔ ነኝና፡፡ ወደ እኔ ብትመጡ ከቶ አትራቡም፤ በእኔም ብታምኑ ከቶ አትጠሙም፡፡ በግብረ መንፈስ ቅዱስ የተዘጋጀውን ቅዱስ ሥጋዬንና ክቡር ደሜን ብትቀበሉ ከሞት ወደ ሕይወት ትመለሳላችሁ፤ የተያዛችሁበት የባርነት ቀንበር ይሰበራል፤ የኃጢአት ሰንሰለታችሁ ይበጣጠሳል፤ ባሕረ እሳቱን ተሸግራችሁ ወደ ገነት መንግሥተ ሰማያት ትነጠቃላችሁ፡፡ ሆኖም ግን ልታምኑብኝ አልወደዳችሁም፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ “በአብ በሕልውና ያየውንና የሰማውን ይመሰክራል ምስክሩም የሚቀበለው የለም” እንዳለ ልትቀበሉኝ አልወደዳችሁም /ዮሐ.3፡32/፡፡  አባቴ በሀብት ስቦ በረድኤት አቅርቦ የሰጠኝ ሁሉ ግን በእኔ ያምናል፡፡ በእኔ ያመነም ከመንግሥተ ሰማያት አፍአ ወደ ገሃነም አላወጣውም፡፡ መንግሥተ ሰማያት ከገቡ መውጣት ካገኙ ማጣት የለምና፡፡ ከሰማይ የወረድኩት የእኔ ፈቃድ ከአባቴ ፈቃድ ልዩ ሆኖ የእኔን ፈቃድ ብቻ ላደርግ አይደለም፡፡ ስለ እናንተ ድኅነት ስል በእኔ ፈቃድ በአባቴ ፈቃድ በባሕርይ ሕይወቴ በመንፈስ ቅዱስም  ፈቃድ ሞትን በፈቃዴ እቀበል ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ስለዚህ እኔን አይቶ ያመነብኝ ሁሉ የዘላለም ድኅነት ያገኛል፤ በመጨረሻው ቀንም ለሐሳር ሳይሆን ለሕይወት አነሣዋለሁ፡፡” /ቅ.ቄርሎስ ዘእስክንድርያ፣ ዝኒ ከማሁ/፡፡
    አሜን ትንሣኤ ለዘክብር እንድንነሣ ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን!!




Wednesday, June 27, 2012

መርከቤ- በልዑል ገ/እግዚአብሔር!


የሰማይ መስኮት ተከፈተ
የፀሐይ ውበት ተከተተ
ነጎድጓድ ተደባለቀ
መብረቅ ተባረቀ
የምድር ፍልቅልቂት ፈሰሱ
የውሃ ቆሬዎች ተቸለሱ

እንዴ...
መሬት ከውሃ ነው
..........................
የተሰራች ?
መሠረቷ ግድግዳዋ
......................
ማይ የሆነች!

ግራ ቀኙ ጎርፍ
ላይ ታቹ ዝናመ ዶፍ
አለ ጣይ በረዶው ተኮሰ
ዝርጉ ባህር ተን ተነፈሰ
እምቡቅ እምቡቅ
ማየ አይህ መረቅ

ክምችት የውቅያኖስ ሙላት
ነፈረ ተንተከተከ ምድርን አጋላት

እንጃልኝ....
ከሥጋ ከእፁ ከፍጥረቱ
አንዱም ላይተርፍ ከጥፋቱ

አቤት ቁጣ...
ለምን ሰማይ ጎረፈ
ሙላቱ እስተላይ ሰፈፈ?
ክህደቱ:-
የጠፈሩን ቧንቧ ከፈተው
የእልቂቱን ዝናም አዘነመው
ሀጥያቱ:-
የምድርን ምድጃ ለኮሰው
የረጋውን ውሃውን አጋለው

እንግዲህ...
ክህደት ከሀጥያት ከተራመደ
ጎርፍ ከንፍር ተዛመደ

አይኔ እያየ...
ፍጥረት በውሃ ሲወሰድ
በሞቀባት መሬት ሲነድ

እኔ ግን...
የማትሰጥመውን ተመለከትኩ
የማትበገረውን ተከተልኩ
ጎፈር እንጨት በዙሪያዋ
አልቦ ሽንቁር መለያዋ
በጉርጆች የተሰራች
በለምለሞች የተዋበች

ውብ መርከብ መዳኛ
ስርግው ልሂቅ ተአምረኛ
ጣራ ክዳኗን ዶፍ አልበሳው
ግድግዳዋን ግለት አልበገረው
ነፋስ አውሎው አልቀየሳት
ሞገድ ማዕበል አልሰበራት

ተገረምኩ...
እኔስ:-
አይኔን አላሸሁ
ኋላዬን አላየሁ
ስራዬማ...
አካሌ ዋና አይችልም
ሰውነቴ ንፍር አያልፍም

ተፈሳህኩ ርኢክዋ
ለሐመር የዋህ

ገባሁ...
በታላቋ መርከብ ተከለልኩ
ከስጥመት ከንፍረት ተሰወርኩ

ገረምክኒ...
በጣራዋ ታቅፌ
በአጥሯ ተደግፌ
ወገኔ...
ከውስጥ ሲገቡባት
በክዳኗ ሲጠለሏት
ለካ...
ሐሴት
ድህነት
እናት ናት::

ተደሰትኩ...
ሳይ:-
ከውስጥ ወደ ደጅ
ፍጥረት ሲሰጥም ሲፈጅ

ምስኪን...
'
ዋና እችላለሁ' ያለ
...................
ሲሰጥም አየሁት
'
ንፍር አይበግረኝ' ያለ
...................
ሲቀቀል አየሁት

መርከቢቷ ተንሳፈፈች ቀዘፈች
ውስጧ አይሞላ ለሁሉ ነች::

እኔስ...
በመርከቤ አለሁ
ከጥፋቱ እድናለሁ::
..........=//=.........


(
ሰኔ21/2004..)


FeedBurner FeedCount