Monday, July 30, 2012

በግብዝነት አትፍረዱ- የዮሐንስ ወንጌል የ33ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.7፡11-24)!!


   በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
   ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በሚመላለስበት ጊዜ ሥግው ቃልነቱን ብቻ ያስተማረን ያስረዳን አይደለም፡፡ አስቸጋሪ ጊዜአትን እንዴት ማለፍ እንዳለብን አርአያ በመሆንም ራሱ አድርጎም ጭምር አስተማረን አስረዳን እንጂ፡፡ ለምሳሌ ፍጹም አምላክ እንደ መሆኑ መጠን ሊገድሉት በሚፈልጉት አይሁድ መካከል ምንም ሳያደርጉት ያስተምራል፤ ይገስጻል፤ ይዘልፋል /ቁ.25/፡፡ ፍጹም ሰው እንደመሆኑ መጠን ደግሞ “ወደ በዓል ከእናንተ ጋር አልወጣም” ብሎ ለወንድሞቹ ለደቂቀ ዮሴፍ ይነገራቸዋል /ቁ.8/፡፡ ወንጌላዊውም በገሊላ ቀረ አለን /ቁ.9/፡፡ “ወንድሞቹ ወደ በዓሉ ከወጡ በኋላ” ግን “እርሱም በግልጥ በይፋ ያይደለ በስውር፣ ሰውን ሳያስከትል፣ ከወንድሞቹ ጋር ያይደለ ብቻውን ወጣ” /ቁ.10/። አስቀድሞም ቢሆን ጭራሽ አልወጣም ሳይሆን ከእናንተ ጋር አልወጣም ነበርና ያላቸው (ወንድሞቹ ጠይቀውት የነበረው ምድራዊን እንጂ እውነተኛውን ክብሩ እንዲያሳይ አልነበረምና)፡፡ ስለዚህ አስቀድመን እንደተናገርነው በዚህ ምልልሱ ጌታችን በአስቸጋሪ ጊዜአት እንዴት በዘዴ በጥበብ ማለፍ እንዳለብን አስተማረን፤ አስረዳን /St. John Chrysostom, Hom 49. /፡፡

 ከዚህ በኋላ ማለትም በግልጥ በይፋ ያይደለ በስውር፣ ሰውን ሳያስከትል፣ ከወንድሞቹ ጋር ያይደለ ብቻውን ወደ በዓሉ ከወጣ በኋላ አይሁድ በበዓል እንይዘዋለን የሚል ምኞት ነበራቸውና /ዮሐ.11፡56/ በንቀት አነጋገር ወዴት ነው?” እያሉ በበዓሉ ይፈልጉት ነበር /ቁ.11/። ተወዳጆች ሆይ! የክፋታቸውን ብዛት የምታስተውሉ ሁኑ፡፡ ጌታችንን ፍጹም ከመጥላታቸው የተነሣ ስሙን እንኳን መጥራት አልፈለጉምና፡፡

  በዚያን ጊዜም በሕዝቡ መካከል ስለ እርሱ ብዙ ማንጐራጐር ነበረ፤ አንዳንዶቹአረ ደግ ሰው ነው” አሉ፤ ሌሎች ግንአረ ደግ ሰው አይደለም፤ ሕዝቡን ያስታል እንጂ የምን ደግ ሰው ነው?” ይሉ ነበር። ዳሩ ግን አይሁድን (መሪዎቹን) ስለ ፈሩ ውስጥ ለውስጥ አጉረመረሙ፣ በማጉተምተም ተነጋገሩ እንጂ ማንም ስለ እርሱ ገልጦ በይፋ የተናገረ የለም /ቁ.12-13/። ለምን ቢሉ በክርስቶስ ያመነ ሰው ቢኖር ከምኩራብ ይባረር ይሳደድ ብለው አዋጅ ነግረው ስለነበር በተለይ ደግነቱን ደፍሮ በይፋ ገልጦ የተናገረ የለም /ዮሐ.9፡22፣ Saint Cyril the Great/፡፡

  አይሁድ ይህን የዳስ በዓል የሚያከብሩት ሰባት ቀን ሙሉ እንደ አንድ ቀን ነውና /ዘሌ.23፡34/ በበዓሉ እኩሌታ ማለትም በአራተኛው ቀን ጌታችን ወደ መቅደስ ወጥቶ ያስተምር ጀመረ /ቁ.14/።

  ሲያስተምራቸውም አይሁድ፡-ይህ ሰው ያስተማረው ሳይኖር እንዴት መጻሕፍትን ያውቃል?” ብለው ትምህርቱን ያደንቁ ነበር። ነገር ግን ሁሉም አይደሉም፡፡ ግማሾቹ አደነቁለት (የበጎ አንክሮ) ገሚሶቹ ደግሞ አደነቁበት (የነቀፋ) /ቁ.15፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ ገጽ 491/፡፡

  ከዚህ በኋላ ማለትም ግማሾቹ የበጎ አንክሮ ግማሾቹ የነቀፋ አንክሮ ካደነቁና እንዴት ሳይማር መጻሕፍትን ያውቃል ካሉ በኋላ ጌታችን እንዲህ ሲል መለሰላቸው፡- ትምህርቴስ ሙት፣ ተሰቀል፣ ውረድ፣ ተወለድ ብሎ ከላከኝ ከባሕርይ አባቴ ከአብ የተገኘች ናት እንጂ ከእኔ ብቻ አይደለችም (በሥልጣን በአገዛዝ አንድ ናቸውና፤ ፈቃዳቻው የማይለያይ ነውና እንዲህ አለ)፤  ፈቃደ እግዚአብሔር ሊያደርግ ሊፈጽም የሚወድ ቢኖር፥ ውስጡ እኔን ለመግደል በቅንዓት በቁጣ ሳይቃጠል በትሕትና በአንቃዕዶ የሚመጣ ቢኖር፣ ትንቢተ ነቢያትን በመመርመር የሚቀርብ ቢኖር እርሱ ትምህርቴ ከእግዚአብሔር ቢሆን ወይም እኔ ከራሴ ብቻ (እናንተ እንደምታስቡት ከአባቴ ተቃራኒ) የምናገር ብሆን ያውቃል። መንፈስ ቅዱስ ያድርበታልና ምድራዊ መምህር እንዳላስተማረኝ ይልቁንም የባሕርዬ እንደሆነ ይረዳል፤ ያውቃል፡፡ ከራሱ ብቻ አንቅቶ የሚያስተምር የሚናገር ሰው የራሱን ክብር ተድላ ደስታ ይሻል ይፈልጋል፡፡ የላከውን ክብር የሚፈልግ ግን፣ ላኪውን ደስ ሊያሰኝ የሚፈልግ ግን እርሱ እውነተኛ ነው፤ በእርሱ ዓመፃ የለበትም፤ ሐሰተኛ አይደለም፡፡ እኔም ከባሕርይ አባቴ ጋር የተለየ ፈቃድ የለኝምና የራሴን ክብር ተድላ ደስታ ብቻ የምሻ አይደለሁም (ይህን የሚላቸው በቀላሉ የባሕርይ አምላክ መሆኑን ያምኑበት ዘንድ ነው!)። ሙሴ ሕግን የሰሰጣችሁ አይደለምን? እናንተስ “እግዚአብሔር የተናገራቸውን ቃሎች ሁሉ እናደርጋለን” ያላችሁ አይደላችሁምን? /ዘጸ.24፡4/፡፡ ነገር ግን እላችኋለሁ፡- በከንቱ ትመጻደቁባታላችሁ እንጂ ከእናንተ አንድ ስንኳ  ሕግን ኦሪትን የሚያደርጋት የሚፈጽማት የለም። እርሷን የምትፈጽሙ ብትሆኑስ “እውነተኛውን በሐሰት አትግደል” ትላለችና ልትገድሉኝ ባልፈለጋችሁ ነበር፡፡ አብ አባቴ ነው ብዬ ብነግራችሁ፤ ከአባቴ ጋር የተካከልኩ መሆኔን በእውነት ያለ ሐሰት ብነግራችሁ፤ ወደ እውነት (ወደ ራሴ) ልመልሳችሁ ብመጣ ባልተቆጣችሁ ባልተናደዳችሁ ነበርአላቸው /ቁ.16-19፣  St. John Chrysostom,Ibid/፡፡

  እነርሱ ግን ቁጣቸው በዛ፤ ፍቅሩን ከማየት ይልቅ ስድብን ለመናገር ፈጠኑ፡፡ ስለዚህም ፡- “ጋኔን አድሮብሃልን? ማንስ ሊገድልህ ይፈልጋል?” አሉት /ቁ.20/።

  ጌታችንም መልሶ እንዲህ አላቸው፡-አንድ ሥራ ሠራሁ (ሕሙማንን ፈወስኩ)፤ ሁላችሁም ታደንቃላችሁ። አይ ሥራ! አይ ተአምራት! ትላላችሁ፡፡ ደግሞም በዚያ አሳብባችሁ በዓል ሰንበት ሻረ ብላችሁ ልትገድሉኝ ትሻላችሁ፡፡ እናንተ በበዓል ምንም አይደረግም ብትሉም ሙሴ መገረዝን ሥርዓት ሰጣችሁ፡፡ ይህም ከአባቶቹ ከእነ አብርሃም ያገኘው የወረሰው ነው እንጂ ከራሱ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን ሕግ የሰጣችሁን “ሙሴን ሰንበትን ሻርክ” አላላችሁትም፤ ይህ ብቻ ሳይሆን እናንተም ራሳችሁ በሰንበት ሰውን ትገርዛላችሁ፤ ጥንቃቄ የላችሁም፡፡ በዓል መሻር ማለት እንዲህ ከሆነ በሰንበት የተወለደውን ልጅ በሰንበት መግረዝም በዓል መሻር ነው፡፡ ምክንያቱም ምላጩ ይለመጣል/ይሳላል፤ ከዚያም የልጁ ደም ይፈሳል፤ ጅማቱ ይበጠሳልና፡፡ ሆኖም ግን እንዲህ ማድረጋችሁ “የሙሴ ሥርዓት” ተብሎ በዓል እንደመሻር አልተቆጠርባችሁም፡፡ ታድያ እኔ በሰንበት ቀን ሰውን ሁለንተና ሥጋውን በተአምራት፣ ሁለንተና ነፍሱን በትምህርት ጤናማ ባደርገው ስለምን ትቈጡኛላችሁ? ስለምን በዓል ሻረ ትሉኛላችሁ? /ቁ.21-23፣ Saint Cyril the Great /፡፡ ስለዚህ እላችኋለሁ፡-ከሙሴ የበለጠ ግርዛትን ብፈጽም፣ ሰው ሁለንተናውን ጤናማ ባደርገው ቅን እውነተኛ ፍርድ ፍረዱ እንጂ በሐሰት የምትፈርዱ አትሁኑ፡፡ በእውነት ፍረዱ እንጂ በመልክ በግብዝነት አትፈረዱ፡፡ የምትመጻደቁበት ሕግም ቢሆን በጽድቅ ፍረዱ ትላለችና” /ቁ.24፣ ዘዳ.1፡17፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ/፡፡

 ወዮ አምላክ ሆይ!ቃልህ ለአይሁድ ብቻ የተነገረ አይደለም፡፡ ዛሬም ላለነው ለሁላችን እንጂ፡፡ እንግዲያውስ ካስተማርከን ጥበብ ካስተማርከን ምግባር የምንማር አድርገን፡፡ ከክፋት ሁሉ የራቅን ክፋትን ሁሉ የምንጸየፍበት ዓቅም ብርታት አድለን፡፡ አንተን ከሚነቅፉ ወገን ሳይሆን አንተን ከሚያመሰግኑ ባለ ማቋረጥም ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያሉ ከሚያመሰግኑህ ጻድቃን ወገን የምንሆን አድርገን፡፡ ሁል ጊዜም በትሕትናና በአንቃዕዶ ሆነን ፈቃድህን የምንፈጽም አድርገን፡፡ ብሩክ አባት ሆይ! በተሰማራንበት ሁሉ በምንውልበት ሁሉ በጉዞአችን ሁሉ በቅንነት እንድናገለግል አድርገን፡፡ መዝሙረኛው እንደተናገረ ጽድቅን የምትወድ ነህ፡፡ ዓመፃን የሚወዳትም ነፍሱን ይጠላታል /መዝ.11፡7፣5/፡፡ እንግዲያውስ ባለማወቅ ጎዳና ተጉዘን አንተን ከማየት ተከልክለን ዓመፃን ከሚወድዋት ነፍሳቸውንም ከሚጠልዋት ወገኖች እንዳንሆን ደግፈን፡፡ አንተን እንዳናሰድብ፣ በግብዝነት እንዳንፈርድ፣ ደሀን እንዳንበድል፣ ፍትሕ እንዳናጓድል፣ ጽድቅን እንድንከታተላት፣ ከሕግህም ፈቀቅ ያልን እንዳንሆን አጋዥ የሚሆነን ቅዱስ መንፈስህን ላክልን፤ አሳድርብን፡፡ አሜን!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!! 

Thursday, July 26, 2012

ከእናንተ የሚፈለገው… በቅ/ዮሐንስ አፈወርቅ!


 
… ይህ ቃል (“ለዚህ ክፉ ትውልድ ደግሞ እንዲሁ ይሆንበታል” የሚለው ቃል) በየወቅቱ ሊነገር የሚገባው እንጂ ለአይሁድ ብቻ ተነግሮ የሚያበቃ አይደለም፡፡ ዛሬ ብዙዎቻችን ብርሃን ከወጣልንና /ዕብ.6፡4/ ከብዙ ደዌዎቻችን ከተፈወስን በኋላ መልሰን ወደ ከፋ ዐዘቅት እንገባለን፡፡ ስለዚህም የሚያገኘን መከራ ከድሮ ደዌአችን በጣም የባሰ ነው፡፡ ጌታ ሽባውን ከፈወሰው በኋላ “ናሁኬ ሐየውከ- እነሆ አሁን ከደዌህ ድነሀል፤ ዑቅ ኢተአብስ ዳግመ እንከ ከመ ዘየአኪ ኢይረክበከ- ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ወደ ፊት ኃጢአትን አትሥራ” ነበር ያለው /ዮሐ.5፡14/፡፡ 38 ዓመት ሙሉ ለተሰቃየው መጻጕዕም እንደዚሁ ነግሮታል /ዮሐ.5፡14/፡፡ ከእናንተ መካከል “ከዚህ የሚብስ ምን ያገኟል?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ ከዚህ የባሰ እማ አለ እንጂ፡፡ ደዌ ነፍስ ይቅርና በዚህ ምድር እንኳን ሊቋቋመው የማይችል ደዌ ሥጋ ሊያገኘው ይችላል፡፡ አያድርስብን እንጂ መቋቋም የምንችለው መቋቋም የምንችለውን ብቻ ነው፡፡…

 ጌታ ኢየሩሳሌምን ሲወቅሳት እንዲህ ብሎ ነበር፡- “በአብርሃም አድሬ ወዳንቺ መጣሁ  በደመ ጣዖትም ተበክለሽ አየሁሽ፣ በደምሽ እንዳለሽ በሕይወት ኑሪ አልሁሽ፤ አዎን በደምሽ እንዳለሽ በሕይወት ኑሪ አልሁሽ…ወሐጸብኩኪ በማይ- በውኃም አጠብሁሽ፣ወአጽረይኩ ደመኪ- ከደምሽም አጠራሁሽ፣ ወቀባእኩኪ በዘይት- በዘይትም ቀባሁሽ…ባንቺ ላይ ካኖርኋት ከክብሬ የተነሣ ውበትሽ ፍጹም ነበረና ዝናሽ በአሕዛብ መካከል ወጣ፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር…ወዘመውኪ ምስለ ውሉደ ግብጽ አግዋርኪ እለ ዐብይ ሥጋሆሙ- ሥጋቸውም ከወፈረ ከጐረቤቶችሽ ከግብጻውያን ጋር አመነዘርሽ፥ ወአብዛኅኪ ዝሙትኪ ከመ ታምዕዕኒ- እኔንም ታስቈጭ ዘንድ ግልሙትናሽን አበዛሽ” /ሕዝ.16፡6፣9፣14፣26/፡፡ አዎን! ሁል ጊዜ በኃጢአት ተለውሰን ለምንኖር ለእኛም ወቀሳው ይህን የመሰለ “አሌ ለክሙ” ነው፡፡

…ትላንት ወደ ሠራነው ኃጢአት ስንቴ ተመለስን? ስንቴስ የባሰ ነገር አገኘን? ወንድሞቼ! ይህን ሁሉ የምላችሁ እንድትማሩበት እንጂ ተስፋ እንድትቆርጡ አይደለም፡፡ ፎርዖንን ታስታውሳላችሁ አይደል? እርሱ ከመጀመርያው መቅሰፍት ተምሮ ቢሆን ኖሮ ከነሙሉ ሠራዊቱ ጋር በባሕረ ኤርትራ ሰጥሞ የዓሳ ቀለብ ሁኖ ባልቀረ ነበር፡፡ እኛ እኮ አሁን ከፊታችን የምንሻገረው ቀይ ባሕር የለንም፤ ነገር ግን በዓይነቱም ይሁን በመጠኑ የቀይ ባሕርን የሚያክል ሳይሆን በጣም ግዙፍና ሙቀቱ ኃይለኛ የሆነ፣ ማዕበሉም ታይቶ የማይታወቅ አስጨናቂ የእሳት ባሕር ነው፡፡ በዚህ እንጦርጦስ እሳቱ የማይጠፋ ትሉ የማያንቀላፋ ስቃይ አለ፡፡ በዚህ የእሳት ባሕር ውስጥ በየትኛውም አቅጣጫ እንደ አረመኔ የበረሀ አውሬ በቅጽበት የሚዞር ወላፈን አለ፡፡ እኛ የምናውቀው የዚህ ዓለም እሳት እንኳ ከሩቅ የነበሩትን የናቡከደነጾር መልእክተኞች ለመፍጀት ኃይለኛ ከሆነ /ዳን.3፡22/ ይህ እሳት ያውም ወደ ራሱ የተጣሉለትንማ ምን ያህል ይፈጃቸው ይሆን?
…ወንድሞቼ ያኔ ከዚህ እቶን እንኳንስ ሊያድነን ቀርቶ ምላሳችንን የምናርስበት የውኃ ጠብታ ሊሰጠን የሚችል ማንም የለም፡፡…አሁን ወደ እግዚአብሔር ቀርቦ መለመን ከፍርድም ነጻ መሆን ይቻላል፡፡ ያኔ ግን ጌታ ይህን ስለማይፈቅድ በሚያንገበግብ እሳት እየተጨነቁ ቃላትም ሊገልጹት በማይችሉ እሳትና ጭንቅ መጣል ብቻ ነው፡፡ አሁን በዚህ ዓለም ወደ እሳት የሚጣሉትና የሚቃጠሉት ቃጠሎ ቃላት አይገልጸውም አይደል? ይህ ግን በጣም ቀላል ነው፡፡ “እንዴት?” ብትሉኝ ከጊዜ አንጻር ሲታይ በጣም አጭር ነውና፡፡ በዚያ ያለው ቃጠሎ ግን መጨረሻ የለውም፡፡…

 በምነግራችሁ ነገር እያበሳጨኋችሁና እያሳመምኳችሁ እንደሆነ ይገባኛል፡፡ ግን ምን ላድርግ? እኔም እናንተም በምግባር በሃይማኖት የታነጽን እንሆን ዘንድ ብቻ ሳይሆን ከዚያም እናመልጥ ዘንድ ነው፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ከመጨማለቃችን የተነሣ እንዴት አድርጌ ላሳምማችሁ እችላለሁ? ብትሰሙኝና ብተለወጡስ እኔም ማረፍ እንኳን በቻልኩ ነበር፡፡ ስለዚህ እስካልተለወጣችሁ ድረስ እናንተን መገሰጼና መምከሬ አላቆምም፡፡… ስለ ገሀነመ እሳት ተደጋግሞ ሲነገር የሚበሳጭ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እኔ ግን “ከዚህ በላይ አስደሳች ትምህርት የለም” እለዋለሁ፡፡ “እንዴት ይህ አስደሳች ትምህርት ነው ትለናለህ?” ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም “ወደዚያ መጣል ከደስታ ሁሉ የራቀ ነውና” ብዬ እመልስላችኋለሁ፡፡ ስለዚህ ነፍሳችን ከመታሰሯ በፊት የነቃን እንሆን ዘንድ ይህን ደጋግሜ እነግራችኋለሁ፡፡…

 እንግዲያውስ ማንም ለራሱ ንስሐ ይግባ እንጂ እንደተወቀሰ አያስብ፤ በንግግሬም የሚቆጣ አይሁን፡፡ ሁላችንም ወደ ጠባቢቱ መንገድ እንግባ፡፡ እስከ መቼስ በስፍና አልጋ እንተኛለን? ዛሬ ነገ ማለት አይበቃንምን? ሰማያዊ ቪላችንን ቀና ብለን ብንመለከት እኮ በዚህ ምድር ይህንን ለመሥራት ባልደከምን ነበር፡፡ እሰኪ ንገሩኝ! ሩጫችን ስንጨርስ ከሬሳ ሳጥንና ከመግነዝ ጨርቅ ውጪ ይዘነው የምንሄድ ነገር አለን? ታድያ ለምን እንከራከራለን?

ስለዚህ ተወዳጆች ሆይ ከዛሬ ጀምረን አዲስ ሕይወትን እንጀምር፡፡… አሕዛብ ምን ያህል በረከት እንደራቃቸው እናሳያቸው፡፡ በእኛ ዘንድ መልካምነትን ካዩ መንግሥተ ሰማያትን በእኛ ውስጥ ያይዋታል፡፡ አዎ! ጨዋ ስንሆን፣ ከክፋት፣ ከክፉ ምኞት፣ ከቅናትና ከጠበኝነት ርቀን ሲመለከቱን፡- “እነዚህ ክርስቲያኖች ገና እዚህ ምድር እያሉ መላእክትን ከመሰሉ ወደዚያኛው ዓለም ሲሸጋገሩ ወደ እውነተኛው ሀገራቸው ሲሄዱ ምን ይመስሉ ይሆን? በእንግድነት ዘመናቸው እንዲህ ብርሃን ከለበሱ ወደ ትውልድ ሀገራቸው ሲሄዱማ እንዴት ይሆኑ ይሆን?” ይላሉ፡፡ በእኛ ምክንያት እነርሱ ይለወጣሉ፤ የእግዚአብሔር ቃል ከእኛ የተነሣ ይከብራል /2ተሰ.3፡1/፤ ወንጌል ከሐዋርያት ዘመን በላይ ይፋጠናል፡፡ ሐዋርያት አሥራ ሁለት ብቻ ሆነው ዓለምን ከለወጡ ከእነርሱ በቁጥር የበዛን እኛማ በመልካም ምግባራችን አስተማሪዎች ብንሆን እግዚአብሔር ምን ያህል ሊወደስ ሊቀደስ እንደሚችል አስቡት፡፡ አሕዛብ ራስን ከመግዛት በላይ ሙት ማስነሣትን አይማርካቸውም፡፡ ምክንያቱም ሙት ሲነሣ ይገረማሉ፤ በመልካም ምግባራችን ግን ይጠቀማሉ፡፡ ሙት ሲነሣ የአንድ ጊዜ ክስተት ነው፤ መልካም ምግባር ግን ሁል ጊዜ ከነፍሳቸው ጋር ተዋሕዶ የሕይወት ልምድ ይሆንላቸዋል፡፡

 ስለዚህ እነሱንም እናመጣ ዘንድ እንፍጨርጨር፡፡ ደግሞም እኮ ከባድ ነገር አልተናገርኳችሁም፡፡ አትጋቡ አላልኳችሁም፤ ከሰው ተለይታችሁ ከማኅበራዊ ኑሮ ራቁም አላልኳችሁም፤ ከእነርሱ ጋር ሆናችሁ መልካምነትን አሳዩ እንጂ፡፡ አዎ! በከተማ መሀል ሆነው መልካም ምግባርን የሚያሳዩ ክርስቲያኖች በገዳም ካሉ መነኰሳት ይበልጣሉ፡፡ ምክንያቱም በከተማ ያሉት ሊሰወሩ አይቻላቸውም፤ መብራታቸውንም አብርተው ከእንቅብ በታች ሊያኖሩት አይችሉም /ማቴ.5፡15፣ ሉቃ.11፡33/፡፡

 ስለዚህ ከዛሬ ጀምረን ለመብራታችንን ዘይት እንጨምርበት፤ በጨለማ ላሉትንም ከስሕተታቸው ይወጡ ዘንድ ምክንያት እንሁንላቸው፡፡ “ትዳር አለኝ፤ ልጆችን አሳድጋለሁ፤ የቤት አባወራ ስለሆንኩኝ ይህንን ማድረግ አልችልም” አትበሉኝ፡፡ ከእናንተ የሚፈለገው ፈቃዳችሁ ብቻ ነውና፡፡ ዕድሜም ቢሆን፣ ባለጸግነትም ቢሆን፣ ማጣትም ቢሆን ሌላም ቢሆን ይኸን ሁሉ ከማድረግ አይከለክላችሁምና፡፡ ምክንያቱም ሽማግሌዎችም፣ ወጣቶችም፣ ሚስቶችም፣ ሕፃናት አሳዳጊዎችም፣ ዕደ ጥበቦኞችም፣ ወታደሮችም ይህን ሁሉ ፈጽመውታልና፡፡ ዳንኤል ወጣት ነበር፤ ሠለስቱ ደቂቅ ሕፃናት ነበሩ፤ ዮሴፍ ባርያ ነበር፤ ሉቃስ ሐኪም ነበር፤ ሊድያም ሐር ሻጭ ነጋዴ ነበረች፤ ጳውሎስንና ሲላስን በወኅኒ ሲጠብቅ የነበረውም ፖሊስ ነበር፤ ቆርነሌዎስ ደግሞ አሥራ አለቃ ነበር፤ ጢሞቴዎስ በሽተኛ ነበር… ነገር ግን ይኸን ከማድረግ የከለከላቸው አንዳችም ምክንያት አልነበረም፡፡ እነዚህ ሁሉ እንደ እኛ ሴቶች፣ እንደ እኛ ወጣቶች፣ እንደ እኛ ሽማግሎች፣ እንደ እኛ ነጋዴዎች፣ እንደ እኛ አሠሪዎች፣ እንደ እኛ ሠራተኞች፣ ወታደሮችና ሲቪል ነበሩ፡፡

 እንግዲያስ መልካም ፈቃድ ይኑረን እንጂ ከንቱ ሰበብን የምናበዛ አንሁን፡፡ ምንም ዓይነት ማንነት ይኑረን ፈቃደኞች ከሆንን ከእግዚአብሔር ጋር መልካምነትን መያዝ እንችላለን፡፡ ይህንን ሁሉ እንድናደርግና በቸርነቱ መንግሥቱን እንዲያወርሰን ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን፡፡ አሜን!!



Tuesday, July 24, 2012

የቁልቢ ገብርኤል አመሠራረት- በዲ/ን ዳንኤል ክብረትና ቀሲስ ከፍያለው መራሒ!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

 ከአዲስ አበባ በስተምሥራቅ 461 ኪ/ሜ. ርቀት ላይ በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጋራ ሙለታ የሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ የዚህን ደብር አመሠራረት በተመለከተ በብዙ ሊቃውንት የሚተረከው የሚከተለው ነው፡፡

በዘጠነኛው መ/ክ/ዘ. ዮዲት ጉዲት ተነሥታ አብያተ ክርስቲያናትን ስትመዘብር፣ ክርስቲያኖችን ስትገድልና መጻሕፍትን ስትቆነጻጽል ንጉሥ አንበሣ ውድም በአኩስምና በአከባቢዋ የነበሩ ታቦታትንና ንዋያተ ቅዱሳትን በመያዝ ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ ወደ ዝዋይ መጣ፡፡

ከ40 ዓመታት ስደት በኋላ አንበሣ ውድም ወደ አኵሱም ሲመለስና የንዋያተ ቅዱሳት ቆጠራ ሲደረግ ታቦተ ቅዱስ ገብርኤል በዝዋይ መቅረቱ ታወቀ፡፡ ከኤርትራ ደብረ ሲና ማርያም የመጡና አባ ሌዊ የተባሉ አባት ታቦቱን ለማምጣት ከንጉሡ አስፈቅደው ወደ ዝዋይ መጡ፡፡

አባ ሌዊ ከሰባት ቀን ሱባኤ በኋላ ታቦተ ቅዱስ ገብርኤልን ይዘው ወደ አኵሱም ሲጓዙ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጦ “እኔ ወደማሳይህ ቦታ ታቦቱን ይዘህ ሂድ” አላቸው፡፡ አባ ሌዊም ታቦቱን ይዘው ተከተሉት፡፡ በመጨረሻም ቁልቢ ደረሱ፡፡ ለአባ ሌዊም የተፈቀደላቸው ቦታ ይሄ መሆኑን ታቦቱም በኋላ ዘመን ለሕዝቡ ድንቅ ሥራ እንደሚሠራ ቅዱስ ገብርኤል ነግሯቸው ተሠወረ፡፡ አባ ሌዊ በቦታው ለ130 ዓመታት ያህል አገልግለው በንጉሥ ግርማ ሥዩም ዘመነ መንግሥተ ታኅሳስ 14 ቀን ዐርፈዋል፡፡

ግራኝ አሕመድ ኢትዮጵያን ሲወርር ብዙ ካህናት ከሰሜን ኢትዮጵያ ታቦታትንና ንዋያተ ቅዱሳትን ይዘው ሲጓዙ ቁልቢ ደረሱ፡፡ መልአከ ገነት መብረቁ፣ መምህር የማነ አብ፣ አባ ተከስተ ሥሉስ የተባሉ ካህናት ከተነጠፈ ድንጋይ ላይ የተጻፈ ነገር ያገኛሉ፡፡ ጽሑፉም ታቦተ ቅዱስ ገብርኤል በሥዉር መቀመጡን፣ ልዩ ልዩ ተአምራት እንደሚፈጸምበት፣ ወደ ፊትም ታላቅ ቤተ መቅደስ እንደሚሠራበት፣ እንዴት አባ ሌዊ ታቦቱን ወደዚህ ቦታ እንዳመጡት የሚገልጽ ነበር፡፡ እነርሱም ይህን ታሪክ ይዘውት በነበረው መጽሐፈ ቀሌሜንጦስ ሕዳግ ላይ ጻፉት፡፡ ወደ ዝዋይ ደሴት ሲደርሱም መጽሐፉን በዚያ አኖሩት፡፡

ልዑል ራስ መኰነን ከዝዋይ ደሴት መጽሐፈ ቀሌሜንጦስን አስመጥተው ሲያነቡ የቁልቢ ገብርኤልን ታሪክ በማግኘታቸው የቅዱስ ገብርኤልን ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ተነሡ፡፡ ልዑል ራስ መኰንን በአከባቢው የአየር ንብረት ተማርከው በሥፍራው ቤት ሠርተው ነበር፡፡ ልዑል ራስ መኰንን ቁልቢ ገብርኤልን ከመትከላቸው በፊት ቦታው የአከባቢው ጎሳዎች የግጭት መነሃርያ ነበር፡፡ ሰላምን በአከባቢው ከመሠረትህ በቦታው በስምህ ቤተ ክርስቲያን እሠራልሃልሁ ብለው እንደተሳሉም ይነገራል፡፡

የተሳሉት በመፈጸሙ የቅዱስ ገብርኤል ታቦት የት እንዳለ ሲያፈላልጉ ቡልጋ ውስጥ ከአዠጉጉ ካህናተ ሰማይ ጋር አባ ዱባለ የተባሉ ካህን ያስቀመጡት ታቦተ ቅዱስ ገብርኤል መኖሩ ተነገራቸው፡፡ ልዑል ራስ መኰንን ለአባ ዱባለ መልእክት ስለላኩባቸው ከሐረር በተላኩ ካህናት አማካኝነት የቅዱስ ገብርኤልን ታቦት ላኩ፡፡ ልዑል ራስ መኰንንም ከነሠራዊቶቻቸው ሸንኮራ ድረስ ሄደው ታቦቱን በመቀበል የካቲት 21 ቀን 1884 ዓ.ም ታቦቱ ቁልቢ ገባ፡፡

የመቃኞው ሥራ በ1883 ዓ.ም ተጀምሮ ፍጻሜ አግኝቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረው ሐምሌ 19 ቀን 1884 ዓ.ም ነው፡፡ በዚሁ ዕለት የዋናው ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ሥራ የመሠረቱ ድንጋይ ተጥሎ ታኅሳስ 19 ቀን 1888 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ተፈጽሞ በአቡነ ማትያስ ተባረከ፡፡ ቦታውን ከባለ አባቶች የገዙት በአርባ የቁም ከብት ነው፡፡ ራስ መኰንን መጋቢት ዘጠኝ ቀን 1889 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ሲሄዱ እዚህ ቦታ ላይ በድንገት ስለታመሙ በዕለቱ ሥጋወደሙ ተቀብለውበታል፡፡ በመጀመርያ ሲተከል በገጠር ቤተ ክርስቲያን ሥሪት ሲሆን በኋላ ግን በስእለት ሰማኢነቱ በመላ ኢትዮጵያ እየታወቀ ስለ መጣ ደብር ሆኗል፡፡

የቅዱስ ገብርኤል ምልጃና በረከት አይለየን!!

(ምንጭ፡ የቤተ ክርሰቲያን መረጃዎች- በዲ/ን ዳንኤል ክብረት፤ Saints and Monastries in Ethiopia, by Kesis Kefyalew Merahi)    

FeedBurner FeedCount