Monday, July 23, 2012

ጊዜዬ ገና አልደረሰም -የዮሐንስ ወንጌል የ32ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.7፡1-9)!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  በእነዚህ ምክንያት ሞት ወደ ዓለም ገብቷልና ከቅንዐትና ከምቀኝነት የባሰ ክፉ ነገር የለም፡፡ “በዲያብሎስ ቅንዐት ሞት መጣ፤ ወደዚህ ዓለምም ገባ” ተብሎ እንደተጻፈ የሰው ልጅ በክብርና በልዕልና ቢያየው ዲያብሎስን ቅንዐት ውስጥ ከቶታል፤ እርሱን ለመመቅኘትም ዓቅሙን ሁሉ ተጠቅሟል /ጥበብ 2፡24/፡፡ ይህ ቅንዐት በሰው ልጆችም ተመሳሳይ ፍሬ ሲያፈራ እናስተውላለን፡፡ ከቅንዐት የተነሣ አቤል ተገድሏል፤ ዳዊት ለሞት ተቃርቦ ነበር፤ ሌሎች ብዙ ንጹሐን ቅዱሳንም መከራ ተቀብለውበታል፡፡ በዚሁ ቅንዐት አይሁድ ክርስቶስን ገድለውታል፡፡ ወንጌላዊው ይህን ሲያስረዳ፡- “ከዚህም በኋላ ኢየሱስ አይሁድ ሊገድሉት ይፈልጉ ስለ ነበር በይሁዳ ሊመላለስ አይወድም ነበርና በገሊላ ይመላለስ ነበር” ይላል /ቁ.1/። ይህን የሚያደርገው ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይሁንና ፈርቶ አይደለም፡፡ የሚሰቀልበት የሚሞትበት ጊዜው ስላልደረሰ እንጂ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም! ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን ለማመልከት ለማስረዳትም አንዳንድ ጊዜ በመካከላቸው ይሄዳል፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገለል ይላል፡፡ አሁንም ተናድደውበት ነበርና ገለል አለ፤ ወደ ምድረ ይሁዳም ሊሄድ አልወደደም /St. John Chrysostom, Hom 48/፡፡  

 የአይሁድም የዳስ በዓል ቀርቦ ነበር /ቁ.2/። አይሁድ ከየአሉበት ዓለም ተሰባስበው በኢየሩሳሌም ቤተመቅደስ የሚያከብርዋቸው ሦስት ታላላቅ በዓላት አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱ ይህ የዳስ በዓል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ከየቤቶቻቸው ወጥተው በቤተ መቅደሱ ዙርያ አጠገብ፣ በከተማው ዋና ዋና አደባባይ፣ በየቤታቸው… ድንኳን ይተክላሉ፡፡ ከግብጽ ወጥተው በበረሐ በድንኳን ውስጥ ያሳለፉትን መከራና ስቃይም ያስታውሱበታል /ዘሌ.23፡29-43/፡፡

 ወንድሞቹም (ደቂቀ ዮሴፍ) ይህን ይዘው (በዓል እንደቀረበ አይተው) ጌታን እንዲህ አሉት፡- “(በምድረ ይሁዳ ያሉት) ደቀ መዛሙርትህ ደግሞ የምታደርገውን ሥራ (ተአምራትህን) እንዲያዩ  አይተውም አምላክ መሆንህን እንዲያምኑብህ ከዚህ ተነሣና ወደ ይሁዳ ሂድ፡፡ ምክንያቱም ራሱን ሊገለጥ እየፈለገ፣ ሥራው እንዲታይለት ወዶ ሳለ በስውር በድብቅ የሚሠራ የለምና። አንተም ሥራህ እንዲገለጥልህ እንዲታይልህ ትወዳለህና እነዚህን አድርገህ ራስህን ለዓለም ግለጥ፤ አምላክነትህን ለሁሉ አሳይ” አሉት /ቁ.3-4፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ ገጽ 490/። እነዚህ ደቀቂ ዮሴፍ ጌታችን የሚያደርጋቸው ተአምራት ለሰው ልጆች ካለው ፍቅር የተነሣ እንደሆነ አላወቁም፤ ከማመን የዘገዩትን ሰዎች ለማቅረብ ያደረገው መሆኑን አልተረዱም፤ እንዲያው ለታይታ እንዲያው ለውዳሴ ከንቱ ያደረገው ይመሰላቸው ነበር እንጂ፤ ስለዚህ አሁን የተናገሩትን ተናገሩ፡፡ የበለጠ ይታይ ዘንድ ይህን ለገቢረ በዓል በወጣው ሕዝቡ መካከል ያደርገው ዘንድ ተናገሩት፡፡ ወንጌላዊው እንደነገረን ይህን ያሉት እነርሱ ራሳቸው ገና በጥርጥር ተይዘው ስለ ነበር ነው፡፡ የሚመጣው መሲሕ እርሱ መሆኑን ስላላመኑበት ነው፡፡ ስለዚህ በሌላ ሰው አስመስለው ይህን ተናገሩ እንጂ እናምንብህ ዘንድ ተአምራትህን አሳየን ማለታቸው ነበር /ቁ.5/፡፡

 ጌታችንስ ምን አላቸው?፡- “በገሃድ ወደ በዓል የምወጣበት ጊዜዬ፣ በይፋ መከራ መስቀል ምቀበልበት ጊዜዬ (አይሁድ ያለ ጊዘው ይገድሉት ዘንድ ይሹ ነበርና)፣ እንናንተ የምትሉት ሳይሆን እውነተኛው ክብሬ በግልጥ የሚታይበት ጊዜዬ ገና አልደረሰም፡፡ የእናንተ ጊዜ ግን የሚከለክላችሁ የለምና ለበዓለ ፋሲካውም ለበዓለ መጸለቱም ዘወትር ለመውጣት የተዘጋጀ (የተመቸ)ነው። ዓለም እናንተን ሊጠላ አይቻለውምና፡፡ እኔ ግን ሥራው ክፉ መሆኑን እመሰክርበታለሁና፤ ስለዚሁም እዘልፈዋለሁና፤ የተሰወረ ተንኰሉም እገልጥበታለሁና፤ ሌባዉን ሌባ ሲሉት አይወድምና እኔን ይጠላኛል፤ ሊገድለኝም ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ እናንተ ወደዚህ በዓል ውጡ፤ እኔ ግን በገሃድ በይፋ የምወጣበት ጊዜዬ ገና ስላልተፈጸመ አይሁድ በተናደዱበት በዚህ ጊዜ ወደዚህ በዓል ገና (ዛሬ) አልወጣም” ብሏቸው በገሊላ ቀረ /ቁ.6-9/፡፡

ከእናንተ መካከል “ጌታችን ወደዚህ በዓል ገና አልወጣም ብሏቸው ሳለ ስለምን ቀይቶ ወደ በዓሉ ሄደ” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- ጌታችን ወደ በዓሉ ጭራሽ አልሄድም ያለ አልነበረም፡፡ ገና (አሁን) አልሄድም እንጂ፤ አሁን ከእናንተ ጋር የምሄድ አይደለሁም እንጂ፡፡ በኋላ ወደ በዓሉ የወጣውም መከራ እንዲያደርሱበት፣ እንዲሰቅሉት፣ እንዲገድሉት ሳይሆን ያስተምራቸው ዘንድ ነው /St. John Chrysostom, Ibid/፡፡

  ተወዳጆች ሆይ! ከቅንዐት ተነሣስተው ጌታን ሊገድሉት ሊወግሩት ሊሰቅሉት ከሚፈልጉት ከአይሁድ ሳይሆን ከመምህራችን ከክርስቶስ ትሕትናን፣ ጥበብን፣ ትዕግሥትን የዋህነትን የምንማር እንሁን /ማቴ.11፡29/፡፡ ብዙ ሰዎች እኛን ለመጕዳት በቁጣ ነደው ይመጣሉ፤ በትሕትና እናሸንፋቸው፡፡ ብዙ ሰዎች እኛን ለመተናኰል ይመጣሉ፤ በፍቅርና በትዕግሥት እንዲሁም በጥበብ እንጠብቃቸው፡፡ ክፉው በእኛ እንዳይሰለጥን እነዚህን የከበሩ የጠቢቡ ቃላት ደጋግመን ለራሳችን እንናገራቸው፡- “እንግዲህ ትቢያና አፈር የሚሆን በሕይወትም ሳለ ሰውነቱ የሚተላ ሰው ለምን ይታበያል /ሲራክ.10፡9/፡፡ በተቈጣ ጊዜ መከራ ይመጣበታልና ቁጡና ዐመፀኛ ሰው መጽደቅ አይችልም /ሲራክ.1፡22/፡፡ በእውነቱ ከቁጣ የባሰ ክፉ ነገር የለም /ምሳሌ.11፡25/፡፡ ስለዚህ ጊዜዋን እስክታሳልፍ ድረስ ቁጣን ታገሣት፤ ኋላም ደስ ታሰኝሃለች /ሲራክ.1፡23/፡፡”
 ይህን እንድናደርግ ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን አሜን!!

Thursday, July 19, 2012

ወደዚያ ዕረፍት ለመግባት እንትጋ- በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 በእውነት ፀዋትወ መከራ የለባትምና መንግሥተ ሰማያት ዕረፍት ናት፡፡ ብካይ፣ ልቅሶ፣ ሐዘን፣ በልብ መቆርቆር፣ መዋረድ፤ ነፍስን የሚያሳዝናት፣ የሚያስደነግጣት፣ ፍርሐት የለባትምና በእውነት መንግሥተ ሰማያት ዕረፍት ናት /ኢሳ.35፡10/፡፡ በፊትህ ወዝ መብላት መጠጣት፤ እሾህም አመኬላም የለባትምና በእውነት መንግሥተ ሰማያት ዕረፍት ናት /ዘፍ.3፡18-19/፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ “በጭንቅ ትወልጃለሽ፤ ፈቃድሽም ወደ ባልሽ ይሆናል እርሱም ገዢሽ ይሆናል” የሚል የለባትምና በእውነት መንግሥተ ሰማያት ዕረፍት ናት /ዘፍ.3፡16/፡፡ በመንግሥተ ሰማያት ዕረፍተ ሥጋ ዕረፍተ ነፍስ፣ ተድላ ሥጋ ተድላ ነፍስ፣ በጎነት፣ የዋህነት፣ ቅንነት፣ ፍቅር አለ፡፡ በመንግሥተ ሰማያት ምቀኝነትና መፎካከር የለም፡፡ በመንግሥተ ሰማይ ሕማመ ሥጋ ሕማመ ነፍስ፣ ሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ የለም፡፡ በመንግሥተ ሰማይ ብርሃን እንጂ ጨለማ፣ መዓልት እንጂ ሌሊት የለም፡፡ በመንግሥተ ሰማይ ደም ግባት ማሸብረቅ አለ፡፡ በመንግሥተ ሰማይ ለዘለዓለም የማያልፈውን በጎ በጎውን ክብር ማግኘት ነው እንጂ መሻት፣ መሰልቸት፣ መራብ፣ ቁንጣን የለም፡፡

 የመንግሥተ ሰማይን ነገር ምሳሌ መስዬ ልነግራችሁ ትወዳላችሁን? አዎን ትሉኝ እንደሆነ የሚቻለኝን ያህል መስዬ እናገራለሁ እንጂ ስለ መንግሥተ ሰማያትስ ፍጹም ምሳሌ መስሎ መናገር አይቻልም፡፡ እነሆ ሰማይን የሚጋርደው ደመና የሚሸፍነውም ጉም ሳይኖር በፀሐይ በከዋክብት አጊጦ ሲያሸበርቅ እናየዋለን፡፡ መንግሥተ ሰማይም እንዲህ ነው፡፡ የደም ግባቱን ማሸብረቅ ስንመለከት ብንዘገይ ሰማይ እንደምንመላለስባት ምድር እናደርገዋለን፡፡ ነገር ግን የመንግሥተ ሰማይ ምሳሌ በዚህ በሰማይ ምሳሌ ፀንቶ የሚኖር አይደለም፡፡ በማሸብረቅ ላይ ማሸብረቅ በደም ግባት ላይ ደም ግባት ሲጨመርለት ይኖራል እንጂ፡፡ በጭቃ በጨፈቃ ከተሠራ ቤት ይልቅ በወርቅ በዕንቁ የተሠራ ቤት እንደሚበልጥ ሁሉ ሰማይ እንደምትመላለስባት ምድር ካደረግኸው በኋላ ደግሞ ከዚያ ካየኸው ሰማይ በላይ ሌላ ሰማይ አለ፡፡ አሁንም ከዚያ በላይ ካየኸው ሰማይ በላይ ግዘፍ የሌላቸው ላኗኗራቸውም ኅልፈት የሌለባቸው መላእክት ሊቃነ መላእክት እንዲሁም ሌሎች ሕልቆ መሳፍርት ኃይላት አሉ፡፡ አሁንም ከፍ እያልክ ስትሄድ መንበረ ጸባዖትን ታገኛለህ፡፡ ዓቢይ ልዑል የሚሆን እግዚአብሔርም አለ፡፡

  ነገር ግን አስቀድመን እንደተናገርን የእኛ ቋንቋ እጅግ ደካማ ከመሆኑ የተነሣ የመንግሥተ ሰማይን ነገር ምሳሌ መስሎ መናገር አይቻልም፡፡ ይህን ለመናገር አስቀድሞ በዚያ መኖርና የተለማመዱትን ልምድ ማካፈልን ይጠይቃልና፡፡ ስለዚህ እንደሚቻለን አድርገን መንግሥተ ሰማያት የምናውቅበትን ምሳሌ መስለን መናገር ይገባናል እንጂ የመንግሥተ ሰማይን ነገር ምሳሌ መስሎ መናገር አይቻልም፡፡ እስኪ ንገሩኝ! ተድላ ደስታ ባለባት በገነት ሰባት ዓመት በነበረ ጊዜ የአዳም የደስታው ብዛት ምን ያህል ነበረ? ሰማይ ከምድር እንደሚበልጥ ሁሉ መንግሥተ ሰማይም ከዚህ (ከገነት ደስታ) ትበልጣለች፡፡

   እስኪ አሁንም ሌላ ምሳሌ መስለን እንናገር፡፡ አንድ በአራቱ ማዕዘን የነገሠ ንጉሥ የሚዋጋው የሚያሳዝነው ሽፍታ ሳይኖርበት በክብር፣ በማዕረግ፣ በመፈራት፣ በመወደድ ሲኖር ያን ጊዜ በልቡ የሚወጣው የሚወርደው የደስታው መጠን ምን ያህል ይመስላችኋል? በመንግሥተ ሰማያትም እንዲህ ነው፡፡ ነገር ግን አሁንም እንደሚገባ መስዬ አልተናገርኩምና ሌላ ምሳሌ ፈልጌ መናገር ይገባኛል፡፡

  ወዳጄ ሆይ መስዬ የምናገረውን ነገር በዓይነ ልቡና አስተውል! አንድ የሚነግሥ የንጉሥ ልጅ በእናቱ ማኅፀን ሳለ ምንም እንደማያውቅና ከተወለደ በኋላ ግን እንደሚነግሥ እንደሚገዛ ሁሉ የአሁኑ ጊዜና የመንግሥተ ሰማይ ሥርዓትም እንዲህ ነው፡፡ እነሆ ታሥሮ በመከራ በኃዘን የሚኖር ሰው፣ ልዩ ልዩ የሚሆን ፅኑ መከራ የተፈራረቀበት ሰው በኋላ ከመከራ አውጥተው ከእስራት ፈትተው አንግሠዉት የነገሠ ሰው ደስ እንደሚለው የመንግሥተ ሰማይ ተድላ ደስታም እንዲህ ነው፡፡

  ሆኖም ግን እስከ አሁን ድረስ የተካከለ ምሳሌ መስዬ ማስረዳት አልተቻለኝም፡፡ አንድ ሁሉንም ነገር (ንግሥናም ቢሆን) በዚህ ዓለም ያገኘ ሰው በመጀመርያይቱ ዕለት፣ አዋጅ በነገሩለት ቀን፣ ሹመት ያዳብር ባሉት ዕለት፣ እጅ መንሻ ባገቡለት ጊዜ መጠን በመጠን ደስታው እየበዛለት ይሄዳል፡፡ ሆኖም ግን ይህም የመንግሥተ ሰማይን ነገር በሚገባ የሚያስረዳ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ይህ ሰው ያገኘው ሁሉ ኃላፊ ጠፊ ስለሆነ እየለመደው እየሰለቸው ይሄዳልና፡፡ መንግሥተ ሰማያት ግን ፍቅሯ በልቦና ፀንቶ ይኖራል እንጂ በመሰጠቷ አትፈጸምም፤ አትለወጥም፤ አትሰለችም፡፡ ኅልፈት፣ መለወጥ፣ ፍጻሜ በሌለባት በመንግሥተ ሰማያት ያለ ጣዕም፣ ተድላ፣ መዓዛ ብርሃንን ያገኘች የነፍስማ አኗኗርዋ እንደምን ይሆን? የማታልፍ፣ ሐዘን ሁሉ ፀዋትወ መከራ የሌለባት፣ ከነውር ከነቀፋ ከመቆርቆር ንጽሕት የምትሆን፣ ደስታን ፍጹም ተድላን የተመላች፣ በትሩፋት ሥራ የሚገኘውን ክብር ልዕልናን የተመላች መንግሥተ ሰማያት እየፀናች ትሄዳለች እንጂ ፍጻሜ መለወጥ የለባትም፡፡

 ከምንኖርባት ከተማ ወጣ ባልን ጊዜ የነገሥታትና የመኳንንትን ድንኳናቸው ብናይ፣ ልዩ ልዩ የሚሆን የጦር ዕቃቸውን ብናይ፣ ጋሻ ጦራቸው ሲያሸበርቅ ብንመለከት ፈጽመን እናደንቃለን፤ ደስም ይለናል፡፡ አይቻለንም እንጂ ቢቻለንና ንጉሡ በወርቅ የተሠራ የጦር ዕቃውን ይዞ በፈረስ ሆኖ በመካከላቸው ሲሄድ ብናየው የነገሥን ያህል ይሰማናል፡፡ የማታላፍ በልዕልናም ያለች የቅዱሳን ማኅደር መንግሥተ ሰማያትን ባየን ጊዜ ’ማ እንደምን እንሆን ይሆን? “በዘለዓለም ማደርያቸው ይቀበልዋችኋል” ተብሎ እንደተነገረ /ሉቃ.16፡9/ ከለበሱት ብረት ወይም ነሐስ ሳይሆን ዓይነ ሥጋ ማየት ከማይቻለው ፍጹም ክብራቸው የተነሣ የእያንዳንዳቸው የጻድቃን መልክ ከፀሐይ ብርሃን ይልቅ ሲያሸበርቅ ስናየው ‘ማ እንደምን እንሆን ይሆን? ይህ ለሰዎች የሚሰጥ ክብር ነው፡፡ የመላእክትን፣ የሊቃነ መላእክትን፣ የኪሩቤልን፣ የሱራፌልን፣ የመናብርትን፣ የአጋእዝትን፣ የሥልጣናትን፣ የኃይላትን መልካቸው ግን ከመናገር የራቀ ነው፡፡

 “ዓይን ያላየችው ጀሮም ያልሰማው በሰውም ልብ ያልታሰበው እግዚአብሔር ለሚወዱት ያዘጋጀው” ተብሎ እንደተነገረ /1ቆሮ.2፡9/ ስለ መንግሥተ ሰማያት መናገር የሚቻለው ‘ማ ማን ነው? በእውነቱ ይህችን መንግሥተ ሰማያት ከመውረስ ከተከለከሉት ሰዎች በላይ ወራዶች የሉም፤ ይህችን መንግሥተ ሰማያት ከሚወርሱ ሰዎች በላይም ንዑዳን ክቡራን የሉም፡፡ እንግዲያውስ ወንድሞች ሆይ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ንዑዳን ክቡራን ከሚሆኑ ሰዎች የምንቆጠር እንሁን፡፡ ወደዚያ ዕረፍት ለመግባት እንትጋ /ዕብ.4፡11/፡፡

  ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር የክብር ክብር፣ ጌትነት ገንዘቡ በሚሆን በፈጣርያችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰጭነት የማታልፍ መንግሥተ ሰማያትን እንወርስ ዘንድ ክቡራን ንዑዳን ከሚሆኑ ቅዱሳን ጋርም እንድንቆጠር ያድርገን አሜን፡፡   

Tuesday, July 17, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- የመጨረሻው ክፍል (ክፍል አምስት)!


      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  ተወዳጆች ሆይ! እንደ እግዚአብሔር ሐሳብ ለመማማር የጀመርነው ርእስ የሚያልቅ ስላልሆነ እናንተ በይበልጥ ከሊቃውንት ከመጻሕፍት እንድታዳብሩት እየጋበዝኩኝ እኛ ዛሬ እንጨርሳለን፡፡ መልካም ንባብ፡፡
1. ደሙ ከሞተ ሥራ ሕሊናን የሚያነጻ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት መሥዋዕቶች የጊደሮች፣ የኮርማዎች፣ የፍየሎች የሆነ ደመ እንስሳ ነበር፤ የዘመነ ሐዲስ ግን በደመ ክርስቶስ የተደረገ ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ መሥዋዕቶች ያለ ፈቃዳቸው ያለ ውዴታቸው የሚሞቱ እንስሳት ነበሩ፤ የዛሬው ግን ሞት ይሁንብኝ ይደረግብኝ ብሎ ያለ ኃጢአቱ እንደ ኃጢአተኛ ተቈጥሮ በፈቃዱ እስከ ሞት ድረስ የታዘዘ የእግዚአብሔር በግ ነው፡፡ የእነዚያ መሥዋዕት ነውርና ነቀፋ ባለባቸው አገልጋዮች የሚቀርብ ነበር፤ የሐዲስ ኪዳን መሥዋዕት ግን ነውርና ነቀፋ በሌለበት በንጹሑ ኢየሱስ የተከናወነ ነው፡፡ የእነዚያ መሥዋዕት ሞት በሚይዛቸው በእንስሳት ደም የሚከናወን አገልግሎት ነበር፤ የሐዲስ ኪዳኑ መሥዋዕት ግን ትንሣኤና ሕይወት በሆነው በክርስቶስ የተከናወነ አገልግሎት ነው፡፡ የመጀመርያው ኪዳን ለጊዜው የሆነ ንጽሕናን የሚሰጥ ነበር፤ የሊቀ ካህናችን የኢየሱስ ክርስቶስ አገልግሎት ግን ከጊዜና ከቦታ ቀመር ውጪ (Beyond Time) የሆነ ዘለዓለማዊ ንጽሕናን የሚሰጥ አገልግሎት ነው፡፡ የቀደመው ኪዳን በምሳሌና በጥላ በሆነ በደመ እንስሳ የሚከናወን ነበር፤ የዛሬው ግን አማናዊ በሚሆን በንጹሑ በደመ ክርስቶስ ተደርጓል፡፡ የቀደመው መሥዋዕት እሳት አንድዶ እንጨት ማግዶ የሚሠዋ ነበር፤ የዛሬው ግን በመንፈስ ቅዱስ እሳትነት የተደረገ ነው፡፡ እንዲህም ስለ ሆነ የእነዚያ መሥዋዕት ደመ ነፍስን (ሥጋን) ብቻ የሚቀድስ ነበር፤ የዛሬው ግን… ደመ ክርስቶስ ግን ሕያው መሥዋዕት ስለሆነ ሁለንተናን ሕያውና ቅዱስ የሚያደርግ ነው፤ ሕሊናን ከሞተ ሥራ የሚያነጻ ልዩ መሥዋዕት ነው፡፡ ሐዋርያው እንዲህ ይላል፡- “ደመ ላህም ደመ ጠሊ የጊደርም አመድ ሥጋዊ ኃጢአትን የሚያነጻ ከሆነ፣ በኃጢአት ያደፉትን የሚያከብራቸው ከሆነ በመንፈስ ቅዱስ እሳትነት ራሱን ለእግዚአብሔር ነውር ነቀፋ የሌለበት የዘለዓለም መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ የኢየሱስ ክርስቶስ ደምማ ከኦሪት፣ ከኃጢአት፣ ከፍዳ፣ ከፍቅረ ንዋይ ልቡናችንን እንደምን ያህል ያነጻ ይኾን?” /የዕብ.9፡13-14 ትርጓሜው፣ገጽ.441/፡፡  ስለዚህ ደሙ ከሞተ ሥራ ሕሊናን የሚያነጻ ሊቀ ካህናት አለን፡፡
2. የሐዲስ ኪዳን መካከለኛ (ምርጥ) ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያው “ስለዚህም የፊተኛው ኪዳን ሲጸና ሕግን የተላለፉትን የሚቤዥ ሞት ስለ ሆነ፥ የተጠሩት የዘላለምን ርስት የተስፋ ቃል እንዲቀበሉ እርሱ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ ነው ይላል /ዕብ.9፡15/፡፡ እውነት ነው! ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለወንጌል መምህር ለመንግሥተ ሰማያትም አስታራቂ የሐዲስ ኪዳን ብቸኛው መካከለኛ ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን ክፍል በተረጐመበት አንቀጽ ምን ማለት እንደሆነ እንዲህ ያብራራልናል፡- “መካከለኛ ማለት ምን ማለት ነው? መካከለኛ መካከለኛ ለሆነለት ነገር ባለቤት (ተጠቃሚ) አይደለም፡፡ ለምሳሌ አማጭ (መካከለኛ) ለሚያገባ ሰው ሚስት ለማግባት አጋዥ ይሆነዋል እንጂ እርሱ የሚያገባ ሙሽራ አይደለም፡፡ በጌታም ዘንድ እንዲህ ነው (የተሠዋው እጠቀም ብሎ አይደለም)፡፡ ወልድ ዋሕድ ጌታ በአባቱና በእኛ መካከል አስታራቂ ሆነ፡፡ አብ በሠራነው ኃጢአት ፈርዶብን መንግሥቱን ሊያወርሰን አልወደደም ነበርና ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው የባሕርይ ልጁ በእርሱና በእኛ መካከል አስታራቂ ሆነ፡፡ እርሱንም ደስ አሰኘው፡፡ ከዚያም እኛን ወደ ልጅነት ልጅነትንም ወደ እኛ ጠራ፤ በሞቱ ከአብ ዘንድ መንግሥተ ሰማያትን አስገኘልን፡፡ ሕጉን በማፍረስ በነበርን ጊዜ ሞት ተገባን፤ እርሱ ግን ስለ እኛ በሞተ ጊዜ ሳይገባን ለመንግሥተ ሰማያት የበቃን አደረገን፡፡ አባት ለልጁ እንደሚሰጥ ቀድሞ ልጅነትን ሳንጥር ሳንግር እንዲያው ሰጠን”  /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.16፡33-48/፡፡ አዎ! በበደልነው ጊዜ ሕጉ (ኦሪት) እንደ ፍርድ ሆነብን (የሚያስፈርድብን ሆነ)፡፡ ለማዳን የሚሞት አንድ ስንኳ ጠፋ፡፡ ሊቀ ካህናችን ግን ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከራሱና ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያስታርቀን ዘንድ የባርያውን መልክ ይዞ (የእኛን ባሕርይ ነሥቶ) ትምክህታችን ከምትሆን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ሰው ሆነ፤ አምላክ የሆነ ሰው ሰውም የሆነ አምላክ (መካከለኛ) ሆነ፤ በተዋሕዶ አንድ አካል አንድ ባሕርይ የሆነ ሥግው ቃል (Incarnated Word)፣ አምላክ ወሰብእ (መካከለኛ) ሆነ፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው በሥግው ቃልነቱ ስለ እኛ ባይሞት ኖሮ ኦሪት ደካማ ከመሆኗ የተነሣ ባልዳንን ነበር፡፡ ስለዚህ እንደ ሰውነቱ ዘመዳችን እንደ መለኰትነቱ ፈጣርያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዲስ ሕግ ለወንጌል መምህር ለመንግሥተ ሰማይ አስታራቂ ሆነ፤ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ያለ ብቸኛ መካከለኛ ሆነ፡፡
3. ራሱን በመሠዋት ኃጢአትን የሻረ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ደጋግመን እንደተናገርነው የቀደመው ሊቀ ካህናት ብዙ ጊዜ ብዙ መሥዋዕት ሠዋ፤ ሊቀ ካህናችን ግን አንድ ጊዜ ራሱን ሠዋ፡፡ የቀደመው ሊቀ ካህናት ገንዘቡ ባይደለ በሌላ ደም አገለገለ፤ የዛሬው ግን እውነት ገንዘቡ በሚሆን በራሱ ደም አስታረቀ፡፡ ምሥዋዑ እርሱ ነውና፤ የሠዋው እርሱ ነውና፤ የተሠዋውም እርሱ ነውና በራሱ ደም አገለገለ፡፡ ፈቃዱን እንደ ካህን ሥጋው እንደ መንበር አድርጎ ነፍሱን አንድ ጊዜ ሠዋ፡፡ አሁን ግን በዓለም ፍጻሜ (ኑሮ ኑሮ አምስት ሺ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም) ራሱን በመሠዋት ኃጢአትን ሊሽር (ያጠፋት ዘንድ) አንድ ጊዜ ተገልጦአል” /ዕብ.9፡26/ ተብሎ እንደተጻፈ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ኃጢአት ያስወገደው ራሱን በመሠዋት እንጂ የጊደርና የኮርማ ደም በማፍሰስ አይደለም፡፡
4. ያዳናቸውን ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመውሰድ ሁለተኛ የሚገለጥ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያው እንዲህ ይላል፡- “ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው፥ እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፥ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል” /ዕብ.9፡27-28/፡፡ ምን ማለት ነው? ውሎ ውሎ ከቤት ኑሮ ኑሮ ከመሬት እንዲሉ ለሰው ኑሮ ኑሮ ሞት እንዲቆየው ኋላም መቃብር እንዲከተለው ሁላችንም ከፊት የሚጠብቀን አንድ ጊዜ “መሞት” አለ፡፡ ሆኖም ግን ይህ “ሞት” ክርስቲያኖች ለምንሆን ለእኛ ከድካማችን ዕረፍት እንጂ እውነተኛ ሞት አይደለም፤ ሞት የሚሠለጥንብን አይደለም፡፡ ሞትስ ሰው የኃጢአቱን ትብትብ ተሸክሞ ሳለ ሥርየተ ኃጢአትን ሳያገኝ መንግሥተ ሰማያትን ሲያጣ ነውና፡፡ ስለዚህ ከድካም ካረፍን በኋላ የዘለዓለም ሕይወት አለን፡፡ ክርስቶስም የብዙዎችን ሰዎች ኃጢአት ያስተሠርይ ዘንድ ኑሮ ኑሮ አምስት ሺ አምስት ዘመን ሲፈጸም አንድ ጊዜ ራሱን ሠዋ፡፡ አዎ! በአዳም ምክንያት የመጣው ሞት ሁሉን ለማጥፋት መጣ፡፡ ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይሁንና ጌታችንም ኃጢአት ሳይኖርበት ስለ እኛ ኃጥእ አሰኘ፡፡ እርሱ ንጹሕ ሲሆን “ከኃጥአን ጋር ተቈጠረ” /ኢሳ.53፡12/፤ የእኛን ኃጢአት የራሱ እንደ ሆነ ቈጥሮ ወደ መስቀል ወጣ /2ቆሮ.5፡21/፡፡ ማመንን ደኅንነትን ለወደዱም አዳናቸው፡፡ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ብሎ /ሉቃ.23፡34/ ሥርየተ ኃጢአትን ሰጣቸው፤ ይቅር አላቸው፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ግን የሰውን ኃጢአት ለመሸከም ሳይሆን ያዳናቸውን ወደ አዘጋጀላቸው ርስት ወደ ሀገራቸው ለመውሰድ ይመጣል፡፡ የዘይት ማሰሮአቸውን ሞልተው ተስፋ ለሚያደርጉት፣ ለሚጠባበቁት ለሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል፤ ይመጣላቸዋል፡፡ ዓለምን ለማሳለፍ፣ ጻድቃንን ለማወደስ፣ ኃጥአንን ለመውቀስ፣ ሞትንና ዲያብሎስን ወደ ጥልቁ በመጣል ለመደምሰስ፣ መንግሥቱንም ለምእመናን ለማውረስ ይመጣል፡፡ ወንድሜ!... እኅቴ!... የኢየሱስን መምጣት ትጠባበቃለህን/ ትጠባበቂያለሽን? እንግዲያው ከወንጌላዊው ጋር፡- “ይህን የሚመሰክር አዎን በቶሎ እመጣለሁ ይላል፤ አሜን ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና” እንበል /ራዕ.22፡20/፡፡

      ስናጠቃልለው ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ እንዲደርሱ የሚወድ ደግሞም  የምናመልከው እግዚአብሔር አንድ ነው፡፡ እንዲያድነንና ወደ እውነት (ወደ ራሱ) ሊመራን ቤዛም ሊሆነን በተለየ አካሉ ትምክሕታችን ከምትሆን ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሥጋንና ፍጹም ነፍስን ተዋሕዶ የመጣም አንዱ እውነት እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እንዲህ ስለሆነም መካከለኛ መባልን ተገባው፡፡ “እግዚአብሔር አባቴ ነው”፤ “በአባቴ ስም መጣሁ”፤ “እኔና አብ አንድ ነን” ብሎ የመሰከረውን ምሥክርነት ያልተቀበሉት ባይቀበሉትም በገዛ ዘመኑ (በመዋዕለ ሥጋዌው) ምስክርነቱ ነበረ /1ጢሞ.2፡4-6/፡፡ እኛም ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ሆነን ይህን እውነት እንናገራለን፤ አንዋሽም፡፡ ብዙዎች ሌላ መካከለኛ እንዳለን አድርገው ቢከሱንም “ከአንዱ ሊቀ ካህናችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ውጪ ሌላ መካከለኛ የለንም” ብለን እንመሰክራለን፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የታረቅንበት የመንግሥተ ሰማያትን መንገድ በደሙ የመረቀልን ሊቀ ካህናችን አንድ ነው፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ይባላል ብለን እንመሰክራለን፡፡ የቅዱሳንን ምልጃ ከኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህንነት ጋር ፈጽሞ የማይገናኝ ነውና “ሌላ መካከለኛ” የለንም ብለን እንመሰክራለን፡፡
አኰቴት ወክብር ለሊቀ ካህንነ ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስለ አቡሁ ወምስለ መንፈሲሁ እስከ ለዓለም አሜን!! 

Monday, July 16, 2012

ጌታ ሆይ ከአንተ ወደ ማን እንሄዳለን?-የዮሐንስ ወንጌል የ31ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.6፡53-ፍጻሜ)!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
   ስለ ሰማያዊ ነገር፣ ስለ መንፈሳዊ ቃል በምንናገርበት ጊዜ አፍአዊ ምድራዊ የሆኑ አስተሳሰቦችን ሁሉ ከእኛ ዘንድ የራቁ መሆን ይገባል፡፡ ወደ አንድ ምድራዊ ንጉሥ በቀረብን ጊዜ ሐሳባችን ልባችን ሁሉ በምንም ነገር እንደማይባክን መንፈስ ቅዱስ ሲናገረንም ከዚሁ በበለጠ በአርምሞና በአንቃዕዶ ሆነን ልንቀርብ ልናደምጥ ይገባናል፡፡ ዛሬ የምንማማረው ትምህርትም ይህን የመሰለ ልብ የሚጠይቅ የሚፈልግ ነው፡፡ የአይሁድ ሰዎች አቀራረባቸው ሁሉ እንዲህ አፍአዊ፣ ሥጋዊና ደማዊ ስለ ነበረ ጌታችን በሚነግራቸው የሕይወት ቃል ግራ ሲጋቡ፣ ሲጨቃጨቁ፣ ሲያንጐራጕሩ እንመለከታቸዋለን፡፡ “ይህ ሰው ሥጋዉን እንበላ ዘንድ እንደምን ሊሰጠን ይችላል? አንዳንድ ጉርሻስ እንኳ ይደርሰናልን? ደግሞስ ዕሩቅ ብእሲ ሥጋዉን ቢበሉት ደሙንም ቢጠጡት ደዌ ይሆናል እንጂ ሕይወት ይሆናልን?” እያሉ ሲታወኩበት፣ ሲከራከሩበት እናስተውላቸዋለን /ቁ.52/፡፡ ጌታችን ግን “የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ” በማለት  ሥጋዉን ሊበሉት ደሙንም ሊጠጡት መስጠት የሚቻል ብቻ ሳይሆን ይኸን ሰማያዊ መብል ይኸን ሰማያዊ መጠጥ አለመብላት አለመጠጣትም ዘለዓለማዊ ሕይወትን የሚያሳጣ እንደሆነ ይነግራቸው ያስረዳቸው ነበር /ቁ.53/። ንግግሩንም በዚህ ያበቃ አይደለም፤ ጨምሮም፡-ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው፤ ከገቡ መውጣት ካገኙ ማጣት የሌላት የማታልፍ መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳል፥ እኔም በመጨረሻው ቀን በዕለተ ምጽአት በክብር አስነሣዋለሁ፤ አድነዋለሁ” አላቸው እንጂ /ቁ.54፣ St. John Chrysostom, Hom.47./ 

   ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ገና ወንጌሉን ሲጀምርልን “ቃልም ሥጋ ነሣ” በማለት ነገሩን ያቆመ አይደለም፡፡ ፍጹም ተዋሕዶአቸውን ለማሳየት “ቃልም ሥጋ ሆነ” አለን እንጂ /ዮሐ.1፡14/፡፡ ይህን ሲልም ከእግዚአብሔር ዘንድ የነበረው ቀዳማዊ ቃል ባሕርይውን ለውጦ ሥጋ ሆነ ማለቱ አይደለም፡፡ ሥጋም ወደ መለኰትነት ተለወጠ አላለንም፡፡ ቃል የቃልነት ባሕርይውን ሥጋም የሥጋ ባሕርይውን ይዞ በፍጹም ተዋሐደ እንጂ፡፡ ሕይወትን ላጡ ፍጥረታት ሕይወትን የሚሰጥ ቀዳማዊ ቃል የሰው ልጆች ሊረዱት ሊመረምሩት ከሚችሉት በላይ በሆነ በተዋሕዶ ምሥጢር የፈጠረውን ሥጋ ተዋሐደ፡፡ ለሥጋም የመለኰትን ባሕርይ ሰጠው፡፡ ሥጋም የመለኰትን ባሕርይ ገንዘብ አደረገ፡፡ በእኛ ተፈጥሮ ውስጥ የነበረውን ሞት በእርሱ ባሕርይ አጠፋልን፤ ሥጋ በባሕርዩ ሕይወት የሆነ ቃልን ተዋሕዷልና የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን የሚበላ ክቡር ደሙን የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው፡፡ እንዲህም ስለሆነ ጌታችን “በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ” በማለት ተናገረ፡፡ ሆኖም ግን “ሥጋዬ ያስነሣዋል” አላለም፤ “ሥጋዬን የበላውን ደሜንም የጠጣውን ሰው አስነሣዋለሁ” እንጂ፡፡ ከተዋሕዶ በኋላ ምንታዌ የለምና፡፡… ስለዚህ ምንም እንኳን ሞት የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሳ አንበሳ በዙርያችን ቢዞርም ሥጋችንንም ልናስወግደው ወደማንችለው መበስበስ ሊቀይረው ቢሞክርም ክርስቶስ በእኛ እኛም በክርስቶስ ከሆንን ግን በእርግጠኝነት (ለክብር ለሕይወት) እንነሣለን፡፡ ሥጋው እስራኤል ዘሥጋ ጊዜአዊ የሥጋን ረሀብ እንዳስታገሰላቸው መና ያይደለ ዘላለማዊ ሕይወትን የሚያድል እውነተኛ መብል ነውና፤ ደሙም እስራኤል ዘሥጋ በገዳም ጊዜአዊ የሥጋ ጥማቸውን እንዳረካላቸው ውኃ ያይደለ እውነተኛ መጠጥ ነውና /ቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ፣ በዲ/ን ታደለ ፈንታው ገጽ 154/፡፡ 

    ስለዚህም ነው በሰዋዊ አመክንዮ ሲታወኩ ለነበሩ አይሁድ፡- ሥጋዬ እውነተኛ (የማያልፍ፣ የማይሻር፣ የማይለወጥ )መብል ነው፤ ደሜም እውነተኛ (የማያልፍ፣ የማይሻር የማይለወጥ) መጠጥ ነው፡፡ የዚህ ዓለም መብል እውነተኛ አይደለም፡፡ ማታ ተበልቶ ጧት ይርባልና፤ ጧት ተበልቶ ማታ ያስፈልጋልና፡፡ ኃላፊ ጠፊ ስለሆነም በቀን ብዙ ጊዜ ይበላል፡፡ እኔ የምስጣችሁ መብል፣ እኔ የምሰጣችሁ መጠጥ ግን በኃጢአት ካላሳደፉት በቀር ቀዋሚ ዘላለማዊ ነው፡፡ በአሚን በንጽሕ ሆኖ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ ግን በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ (በልግስና በጸጋ) ተዋሕጄው እኖራለሁ” የሚላቸው /ቁ.55-56/። አዎ! ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ብቻ ሳይሆን ከውጪ ያሉትንም በክርስቶስ አምነውና በስሙ ተጠምቀው ወደዚሁ ቅዱስ ምሥጢር እንዲቀርቡ እንዲቀበሉትም የምታበረታታቸው ስለዚሁ ነው፡፡ መዝሙረኛው እንደተናገረ፡- “ደሙ የሰውን ነፍስ ደስ የሚያሰኝ መጠጥ፣ ሥጋዉም ኃይለ ነፍስን የሚያፀና መብል ነውና” /መዝ.104፡15 ትርጓሜው፣ Saint Ambrose, On the Mysteries 9:55, 58. /፡፡

  ጌታችን አሁንም ከማር የጣፈጠ ሕይወትም የሆነ ቃሉን ይቀጥልና እንዲህ ይላቸዋል፡- “ሕያው አብ (ለተዋሕዶ) እንደ ላከኝ እኔም ከአብ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ ስለተወለድኩ ሕያው ነኝ፥ እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ (በጸጋ ስለምዋሐደው) ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል። አባቶቻችሁ መናውን በገዳም በልተው እንደ ሞቱ ያይደለ ከሰማይ የወረደ ኅብስት ይህ ነውና (ሥጋዬ ነውና)፡፡ ይህን እንጀራ የሚበላም ለዘላለም ሕያው ሆኖ ሞተ ነፍስ (ትንሣኤ ዘለሐሳር) ሳይኖርበት በተድላ በደስታ በሕይወት ይኖራል”/ቁ.57-58፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታው ገጽ 488/፡፡

  ነቢዩ ሚልክያስ እንደተናገረው ይህ የአይሁድ ዓይነት ቁርባን ያይደለ ንጹሕ የዘለዓለምንም ሕይወት የሚሰጥ ቁርባን ነው /ሚል.1፡10-11,St. Irenaeus Adv. Haer. 4:17:5, 6./፡፡

    በነቢዩ ኢሳይያስ “በስውር ወይም በጨለማ ምድር ስፍራ አልተናገርሁም” /ኢሳ.45፡19/ እንዳለ በቅፍርናሆም ባለ በምኵራብ ሲያስተምራቸው ይኸን (በምሳሌ ሳይሆን በግልጥ እውነተኛ ሥጋዬ ነው፤ እውነተኛ ደሜ ነው እያለ ስለ ሥጋወደሙ) ነገራቸው፤ አስተማራቸው” /ቁ.59/ ተወዳጆች ሆይ! ሥጋዉንና ደሙን ምሳሌ አለማለቱን እናስተውል፡፡ አምሳል አምሳል እንጂ እውነተኛ አይደለምና፡፡ አንድ ሰው መታሰብያን ብቻ ተቀብሎ ለዘለዓለም በሕይወት ከእግዚአብሔር ጋር መኖር አይችልምና፡፡ ለአማናዊው የክርስቶስ ጥምቀት ምሳሌ የነበረችው የኦሪት የውኃ መታጠብ የዘለዓለም ድኅነት መስጠት የማትችል ይልቁንም ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ የምታስቀር እንደሆነች ሁሉ “ሥጋውና ደሙ እውነተኛ መብል አይደለም፤ ምሳሌ መታሰብያ እንጂ” የሚሉም የዘለዓለም ሕይወት የሌላቸው ይልቁንም ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ የቀሩ የወጡ ናቸው፡፡

  ጌታችን ስለ ሁለት ምክንያት በምኵራብ አስተማራቸው፡፡ አንደኛ ብዙ ሕዝብ ባለበት ቦታ በማስተማሩ ምክንያት ብዙዎች በእርሱ ያምናሉና፡፡ ሁለተኛ እርሱ ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ጋር ፍጹም ተቃርኖ እንደሌለው እነርሱም (አይሁድም) እንደሚያስቡት እርሱ የእግዚአብሔር ተቃዋሚ እንዳልሆነ ያስረዳቸው ዘንድ በምኵራብ አስተማራቸው /St.John Chrysostom, Ibid/፡፡

   ከደቀ መዛሙርቱም ብዙዎች ይኸን (የምሥጢረ ቁርባኑን ትምህርት) በሰሙ ጊዜ ረቀቀባቸው ራቀባቸውና፡-ይህ የሚያስጨንቅ ንግግር ነው፤ ማን ሊሰማው ማንስ ልብ ሊለው ይችላል? የሰው ሥጋስ እንደምን ሕይወትን ሊሰጥ ይችላል?አሉ /ቁ.60, St. Augustine,On the Gospel of St. John, tractate 27:1./። ልብ ያመላለሰውን ኩላሊት ያጤሰውን የሚያውቅ /ዕብ.4፡12/ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ደቀ መዛሙርቱ በዚህ ምክንያት እንደታወኩ በልቡ አውቆ፡-ይህ ያሰናክላችኋልን? እንግዲህ ወልደ እጓለ እመሕያው (የሰው ልጅ- ክርስቶስ) ቀድሞ ወደ ነበረበት (ያስተውሉ! እንዲህ ማለቱ ሥጋ ከጥንት ነበረ ከሰማይም ይዞት ወረደ ማለት ሳይሆን ቀዳማዊ ከሆነው ቃል ጋር በተዋሕዶ አንድ ባሕርይ አንድ አካል መሆኑን መግለጽ ነው!)ሲያርግ ብታዩ እንደምን ደንቃችሁ ይሆን?  ሥጋዬ ሕይወትን እንደሚሰጥ በነገርኳችሁ ጊዜ ልባችሁ ከታወከ ሳርግ ብታዩኝ ‘ማ ምን ልትሉ ነው? ዕሩቅ ብእሲ ሲሆን እንደምን እንደ ወፍ ወደ ላይ ሊበር ሊወጣ ቻለ ልትሉ ነውን? ይህ ግን ለዕሩቅ ብእሲ የማይቻል ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህን አፈር የነበረው ሥጋ እንዲህ በተዋሕዶ አክብሬ የባሕርይ አምላክ እንዳደረግኩት ሁሉ ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ያደረኩትም እኔ ነኝ፡፡ የእኔን ሰው የመሆን ምሥጢር (ምሥጢረ ተዋሕዶን) በመረመራችሁ ባስተዋላችሁ ጊዜ ሰው የሆንኩት እኔ የሚያድን መለኰት እንደሆንኩ፤ ዕሩቅ ብእሲ ግን አንዳች እንደማይጠቅም (ሕይወትን እንደማይሰጥ) ትገነዘባላችሁ፡፡ ስለዚህ እኔ የነገርኋችሁ ቃልም መንፈስ (ረቂቅ) ነው፤ ሕይወትም ነውና በግዙፍ አእምሮ (እኔን ወልደ ዮሴፍ በሚል ልቡና) ሳይሆን በውስጣችሁ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ተረዱት፤ በእምነትም ተቀበሉት። ይህ ሥጋ አስቀድሜ እንደነገርኳችሁ ሕይወት የሆንኩትን እኔን (ዮሐ.1፡5) ተዋሐዷልና ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው፡፡ ነገር ግን ከእናንተ ይህን የማያምኑ አሉ” አላቸው /ቁ.61-63፣ St.Cyril Of Alexandria, Ibid/።

  ጌታችን የማያምኑት እነማን እንደ ሆኑ (አይሁድ ፈሪሳውያን እንደሆኑ) አሳልፎ የሚሰጠውም ማን እንደ ሆነ (ይሁዳ እንደሆነ) ከጥንት ጀምሮ ያውቅ ነበርና እንዲህ አላቸው /ቁ.64፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ፣ ገጽ 489/።

  አሁንም ጨምሮ እንዲህ አላቸው፡- እስራኤል ዘሥጋ ባለማመናቸው ምክንያት ዕረፍተ ፍልስጥኤምን ሳይወርሱ እንደቀሩ ሁሉ አንድ ሰው በልቡ ፈቅዶ ወዶ ከዚያምዕውቀቱ ከአባቴ (ረድኤተ እግዚአብሔር) የተሰጠው ካልሆነ በቀር ወደ እኔ ሊመጣ በእኔም ማመን የሚቻለው የለም፤ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያትን መውረስን አይቻለውም ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ”። እንዲህ ስላላቸውም ከሕዝቡ ወገን ብዙዎች ወደ ኋላ ተመለሱ፤ ወደ ፊትም ከእርሱ ጋር አልሄዱም። በጌታ ማመን ምርጫቸው አልነበረምና “ጽድቅ በዕድል ከሆነስ እንግዲያ ምን ያደክመናል?” በማለት የራሳቸውን አመክንዮ በመስጠት ጌታን ከመከተ ቀሩ /ቁ.65-66/፡፡ ማየት የተሳናቸው ሰዎች ከብርሃን ይለቅ በጨለማ መቀመጥን ይወዳሉ፤ ዓይነ ልቡናቸው ከማመን የታወሩ ሰዎችም ከፀሐይ ከክርስቶስ ርቀው በጨለማ መኖርን ይመርጣሉ /ቅ.ቄርሎስ ዘእስክንድርያ፣ ዝኒ ከማሁ/፡፡

   ጌታችንም ሰዎቹ በፍቃዳቸው ወደ ኋላ እንደተመለሱ አይቶ ለአሥራ ሁለቱ ደቀመዛሙርቱ (ያለፈቃዳቸው ይነዳሉ የሚል ነገር እንዳይኖርና ወደው ፈቅደው ሊከተሉት እንደሚገባ ሲያስረዳቸው)፡-እናንተም ልትሄዱ ትወዳላችሁን?” አላቸው /ቁ.67፣ Cyprian the Martyr Letter 59 to Cornellius: 7./። ስምዖን ጴጥሮስ ግን፡-ጌታ ሆይ! የዘላለም ደኅንነት የሚሰጥ ትምህርት ከአንተ ዘንድ እያለ ወደ ማን እንሄዳለን? ከሕይወትስ ወጥተን ወዴት እንሄዳለን?  እኛስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጁ ክርስቶስ እንደ ሆንህ አምነንብሃል፤ የዘላለምን ሕይወትም በቅዱስ ሥጋህና በክቡር ደምህ ልትሰጠን እንደመጣህ አውቀናል ተረድተናልም” ብሎ መለሰለት /ቁ.68-69፣ Saint Augustine,27:9/። ጌታችንም፡-እናንተ እንድታውቁት ብዬ እንጂ አሥራ ሁለታችሁንማ እኔስ ከፍጹም ፍቅሬ የተነሣ የመረጥኋችሁ አይደለምን? ነገር ግን ከእናንተ አንዱ የእኔን ፍቅር ያላስተዋለ ሰይጣን (መስተቃርን መስተጻርር) ነው” ብሎ መለሰላቸው /ቁ.70/።

 ይህን ነገር (እስከሚያሲዘው ድረስ በግልጽ ሳይሆን በምሥጢር) የተናገረ ስለ ስምዖን ልጅ ስለ አስቆሮቱ ይሁዳ ነው፤ ከአሥራ ሁለቱ አንዱ የሆነ እርሱ አሳልፎ ይሰጠው ዘንድ አለውና /ቁ.71/፡፡ ጌታችን እንዲህ ስላለም ከሁሉም ይልቅ ጴጥሮስ በእጅጉ ታውኮ ነበር /ዮሐ.13፡24/፡፡ ይህም የሆነው ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ አስቀድሞ ጌታን “ጌታ ሆይ! መከራ መስቀል ከቶ አይሁንብህ” ሲለው “ወደኋላዬ ሂድ አንተ ሰይጣን” ብሎት ስለነበር አሁንም ከእናንተ አንዱ ሰይጣን ነው ሲል “እኔ እሆንን?” በማለት ነበር /St.John Chrysostom, Ibid/።

   ወዬ አባት ሆይ! በሲና በረሐ ምድራዊ መብልን በልተው ምድራዊ መጠጥንም ጠጥተው እንደሞቱ እንደነዚያ እንዳንሞት ሰማያዊ መብል ሰማያዊ መጠጥ ሆነህ መጥተህ ሳይገባን ስለ ሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ ከመጀመርያው አዳም ጋር እንዳንሞት ይልቁንም ከሁለተኛው አዳም (ከአንተ ጋር) የዘለዓለም ሕይወት እንዲኖረን ራስህን መብልና መጠጥ አድርገህ ስለሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ እንግዲያውስ አባት ሆይ! ከምድራዊ መብል ጋር ስንታገል ካዘጋጀህልን ሰማያዊ ማዕድ (ከቅዱስ ሥጋህና ከክቡር ደምህ) የራቅን እንዳንሆን ይልቁንም በፍርሐትና በረዐድ ሆነን እንድንቀርብ እንድንቀበል እርዳን፡፡ ይህን ሥጋህን በልተን ይህንንም ደምህን ጠጥተን አንተ በእኛ እኛም በአንተ እንድንኖር እንድትዋሐደን እርዳን፡፡ አባት ሆይ! ሕይወት የሆነውን፣ ደኅንነትም የሚገኝበትን ቃልህን ሰምተናል፡፡ መድኃኒታችን ሆይ! ታድያ ከአንተ ወዴት እንሄዳለን? ፍቅር ከሆንከው ከአንተ ርቀንስ ምን ሕይወት አለን? ቅዱስ አባት ሆይ የቸርነትህን ሥራ ሥራልን አሜን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!


FeedBurner FeedCount