Monday, December 28, 2015

ስለ በርለዓም ሰማዕት



በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ 18 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
    በርለዓም ሰማዕት በዲዮቅልጥያኖስ ጊዜ በአንጾኪያ የነበረ እጅግ ጥቡዕ ክርስቲያን ነው፡፡ መምለክያነ ጣዖት ለጣዖት ይሠዋ ዘንድ ባስገደዱት ጊዜ ያሳየው ጽናት እስከ ምን ድረስ እንደ ኾነ፣ የዲያብሎስ የማታለል ሥራ እንዴት በየጊዜው እንደሚቀያየር፣ ሊቁ ያስተምራቸው የነበሩት ምእመናንም ከዚህ ሰማዕት ምን ሊማሩ እንደሚገባቸው ሰማዕቱ ወዳረፈበት መቃብር ወስዶ ያስተማራቸው ነው፡፡ መታሰቢያዉም እ.ኤ.አ. ሕዳር 19 ነው፡፡
† † †

     (1) ዛሬ ንዑድ ክቡር የሚኾን በርለዓም ወደ ቅዱስ በዓሉ ጠርቶናል፡፡ ነገር ግን እንድናመሰግነው አይደለም፤ እንድንመስለው ነው እንጂ፡፡ ሲያመሰግን እንድንሰማውም አይደለም፤ የደረሰበትን ቅድስና ዐይተን እርሱን መስለን እዚያ የቅድስና ማዕርግ ላይ እንድንደርስ ነው እንጂ፡፡ የዚህ ዓለም ሰዎች ወደ ሥልጣን ሲወጡ ሌሎች ሰዎች ልክ እንደ እነርሱ ታላላቅ ኾነው ማየትን በፍጹም አይወዱም፤ ቅንአት ውስጣቸውን ይተናነቃቸዋል፡፡ በመንፈሳዊ ነገሮች ላይ ግን እንደዚህ አይደለም፤ ፍጹም ተቃራኒ ነው እንጂ፡፡ ቅዱሳን ሰማዕታት ክብራቸውን ከምንም በላይ ከፍ ብሎ የሚያዩት ደቀ መዛሙርቶቻቸው እነርሱን አብነት አድርገው ከእነርሱ በላይ የተሻሉ ኾነው ሲመለከቱአቸው ነው፡፡ በመኾኑም አንድ ሰው ሰማዕታትን ማመስገን ቢፈልግ እነርሱን ሊመስል ይገቧል፡፡ አንድ ሰው የእምነት አትሌቶችን ማሞገስ ቢፈልግ እነርሱን መስሎ ምግባር ትሩፋትን ሊሠራ ይገቧል፡፡ ይህ ነገርም እነርሱ ካገኙት ሹመት ሽልማት በላይ ሰማዕታቱን ደስ ያሰኛቸዋል፡፡ በእርግጥም ያገኙትን ሹመት ሽልማት ከምንም በላይ የሚያጣጥሙትና የተሰጣቸው ክብር ምን ያህል ታላቅ እንደ ኾነ የሚገነዘቡት እኛ እነርሱን መስለን የሔድን እንደ ኾነ ነው፡፡ ይህንንም በማስመልከት ንዑድ ክቡር የሚኾን ጳውሎስ የተናገረውን አድምጡ፤ እንዲህ ያለውን፡- “እናንተ በጌታችን ጸንታችሁ ብትቆሙ አሁን እኛ በሕይወት እንኖራለን” /1ኛ ተሰ.3፥8/፡፡ ከዚህ በፊትም ብፁዕ ሙሴ እንዲህ ብሏል፡- “አሁንም ይህን ኃጢአታቸውን ይቅር ትላቸው እንደ ኾነ ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍኸው መጽሐፍ ደምስሰኝ” /ዘጸ.32፥32/፡፡ እንዲህ ማለቱ ነበር፡- “እነርሱ ከተጎዱ የእኔ ክብር ምንም አይደለም፤ የምእመናን ሙላት ማለት የአካል መገናኘትም ነውና፡፡ ታዲያ ራስ የሕይወት አክሊልን አግኝቶ እግር ቢቀጣ ምን ጥቅም አለው?”

Thursday, December 17, 2015

ቅዱስ አግናጥዮስ ምጥው ለአንበሳ (2)


በሥርጉተ ሥላሴ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ 07 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ሰማዕትነቱ


ቅዱስ አግናጥዮስ የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ በነበረበት ወቅት ቤተ ክርስቲያን ከዓላውያን የሮማ ነገሥታት ከፍተኛ መከራና ስቃይ ይደርስባት ነበር:: በድምጥያኖስ ዘመነ መንግሥት ከነበረው የመከራ ማዕበል በጾም እና በጸሎት፣ በብዙ መንፈሳዊ ተጋድሎ፥ በተለይም ምእመናን መከራውን ተሰቅቀው ከሃይማኖት እንዳይወጡ ተግቶ በማስተማር እንደ መልካም ካፒቴን ሆኖ ቤተ ክርስቲያንን መርቶ አሻግሯል:: ቅዱስ አግናጥዮስ ከትሕትናው የተነሣ ስለ ራሱ ሕይወት እውነተኛ የክርስቶስ ፍቅር ላይ ገና አልደረስኩም፤ እውነተኛ የደቀ መዝሙርነት ፍጽምና ላይ አልደረስኩም እያለ ያዝን ነበር:: በመሆኑም ሰማዕትነት የበለጠ ወደ እግዚአብሔር እንደሚያቀርብ በማመን ለሰማዕትነት ክብር እንዲበቃ በእጅጉ ይመኝ ነበር::

Friday, December 11, 2015

አዲስ መጽሐፍ በቅርብ ቀን


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ 2 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ውድ የመቅረዝ ዘተዋሕዶ አንባቢያን! እንደ ምን ሰነበታችሁ? ላለፉት አምስት ሳምንታት ገደማ በመቅረዝ ላይ አዲስ ጽሑፍ ሳልለጥፍ በመቆየቴ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡ እንዲህ የኾንኩበት ዋና ምክንያት ግን ላለፉት ስድስት ወራት ስተረጉመው የቆየሁትንና ከቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አያሌ መጻሕፍት አንዱ የኾነው የኦሪት ዘፍጥረት የመጀመሪያ ቅጽ መጽሐፍን የመጨረሻዉን ቅርጽ ለማስያዝ ብሎም ወደ ኅትመት ለማስገባት በነበረብኝ ጫና ምክንያት ነው፡፡ እንደ እግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ በእኔ ዓቅም በብዙ ድካም የተተረጎመው ይህ አዲስ መጽሐፍ በቅርብ ጊዜ ወደ እናንተ ይደርሳል፡፡ ለማቆያ ያህልም ከመጽሐፉ መቅድም ከዚህ በታች አቅርቤላችኋለሁ፡-

Wednesday, November 4, 2015

የዓርብ ፍጥረታት



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጥቅምት 25 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ትምህርተ ሃይማኖት - ክፍል 18
ዓርብ ዐረበ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲኾን ተካተተ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ዓርብ ማለት መካተቻ መደምደሚያ ማለት ነው። ምዕራብ ስንል መግቢያ፣ መጥለቂያ (ለምሳሌ የፀሐይ መግቢያን ምዕራብ እንደምንለው) ማለት ሲኾን ዐረብ ሲባልም ተመሳሳይ ነው - ከኢየሩሳሌም ምዕራባዊ አቅጣጫ ያሉ ሀገራት የዐረብ ምድር ይባላሉና። ዐርብ የተባለበት ምክንያት በዕለተ እሑድ መፈጠር የጀመሩት ፍጥረታት ተፈጥረው ያበቁበት፣ የተካተቱበት ቀን ስለ ኾነ ነው፡፡
በዚህ ቀን እግዚአብሔር “ምድር ሕያዋን ፍጥረታትን እንደ ወገኑ እንስሳትን ተንቀሳቃሾችን የምድር አራዊትንም እንደ ወገኑ ታውጣ” ብሎ አዘዘ /ዘፍ.1፥24/፡፡ በዚሁም መሠረት ልክ እንደ ሐሙስ ፍጥረታት በእግራቸው የሚሔዱ፣ በልባቸው የሚሳቡና በክንፋቸው የሚበሩ ፍጥረታት ናቸው፡፡ የሐሙስና የዓርብ መኾናቸውን የምንለየውም በአኗኗራቸውና በግብራቸው ሲኾን የሐሙስ ፍጥረታት በባሕር፣ የዓርብ ፍጥረታትም በየብስ ይኖራሉ፡፡ በዚህ ቀን በአራተኛ አዳምን ፈጥሯል። ይህንን በኋላ እንመለስበታለን፡፡
በሳይንሳዊ መንገድ ሔደን ምድር እነዚህን ፍጥረታት እንዴት ልታስገኛቸው ቻለች ብለን ብንጠይቅ መልስ የለውም፡፡ የተገኙት እግዚአብሔር ስላዘዘ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሔር ምድሪቱን አዘዛት፤ እርሷም አረገዘች፤ ወለደቻቸውም፡፡ ዛሬም ይህ እውነት እንደ ኾነ የምናይበት ኹናቴ አለ፡፡ ዝናብ ወደ ሰኔ አከባቢ መዝነብ ሲጀምር አስቀድመን ያላየናቸው ፍጥረታት ከምድር ወጥተው ሲበሩ፣ እንዲሁም እንደ እንቁራሪት ያሉ ፍጥረታት ወደ መኖር ሲመጡ እናያቸዋለን፡፡ አስቀድሞ ባልተጣለ ዕንቁላል የተለያዩ ዓይነት ትላትሎች ከጭቃ ውስጥ ሲፈጠሩ እናያቸዋለን፡፡ እንግዲህ የእግዚአብሔርን ጥበብ ታያላችሁን?

FeedBurner FeedCount