Thursday, May 19, 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፫


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 11 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከሊባንዮስ ሲማር የቆየውን የንግግር ክህሎት ትምህርት የጨረሰው 367 .. ላይ ነበር፡፡ ትምህርቱ የሚያልቅበት ወራት ራሱ ሰኔ አከባቢ ሲኾን ሐምሌ፣ ነሐሴና መስከረምም የዕረፍት ጊዜ ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት 18 ዓመቱ ነበር፡፡ ዜና ሕይወቱን የጻፈው ጳላዲዮስ እንደተናገረው ቅዱስ ዮሐንስ ከጓደኞቹ ይልቅ እጅግ በጣም ከፍ ያለ ዕውቀት ያለው ነበር፡፡ በትምህርቱ ብቻ ሳይኾን ወጣትነቱም ለብዙ ሰዎች አርአያ ነበር፡፡ 
ትምህርቱን ቢጨርስም ከእናቱ ጋር ነበር፡፡ ብዙ ጓደኞች ቢኖሩትም እንደ ባስልዮስ ግን የሚቀርበው አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እድገታቸው በአንድ ሰፈር ነው፤ የተማሩት በአንድ ትምህርት ቤት ነው፤ ምግባራቸው የቀና ለብዙ ወጣቶችም አርአያ በመኾን የተመሰገኑ ናቸው፡፡ 
በኋላ ላይ ግን ከባስልዮስ ጋር ለጥቂት ጊዜያት ተለያዩ፡፡ የመለያየታቸው ምክንያትም ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ፍርድ ቤቶች እየሔደ እዚያ የሚሰጡትን ፍርዶች መስማት ያስደስተው ስለ ነበር ነው፤ የንግግር ክህሎት ከሊባንዮስ መማሩ ይህን እንዲወድ አድርጎታል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ልክ እንደ አብዛኛው የአንጾኪያ ሕዝብ ቲያትርን ይወድ ነበር፡፡ ጓደኛው ባስልዮስ ግን በእንደዚህ ዓይነት ነገር ብዙም ግድ አይሰጠውም ነበር፡፡ ባስልዮስ ይወደው የነበረው መጻሕፍትን ማንበብ ነው፡፡
ታሪክ ጸሐፊዎቹ ሶቅራጠስና ሶዞሜን እንደጻፉት፥ ቅዱስ ዮሐንስ በዚህ ጊዜ ወደ ፍርድ ቤቶች መሔዱ በኋላ የሕግ ጠበቃ ለመኾን በር ከፍቶለታል ይላሉ፡፡ በጥቂት ጊዜ ውስጥም በሚያደርጋቸው ንግግሮች በሊባንዮስና በማኅበረሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን አገኘ፡፡ የከፍተኛ ባለሥልጣናት አማካሪ፣ ሕግ አውጪ፣ አባቱ ሲያገለግልበት ከነበረው ከከፍተኛው ወታደራዊ ማዕርግ በላይ ወደ መኾን የሚያሸጋግረው ኾነ፡፡

Wednesday, May 18, 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፪


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 10 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ተወዳጆች ሆይ! በክፍል አንድ ትምህርታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ ተወለደባት ከተማ ስለ አንጾኪያ ጥቂት ተነጋግረናል፡፡ እነሆ አሁን ደግሞ ወደ ሊቁ ልደትና እድገት እንቀጥል፤ መልካም ንባብ!
ከአንደበተ ርቱዕነቱ የተነሣ አፈወርቅ የተባለው ይህ ቅዱስ የተወለደው 347 .. ነው፡፡ 50 ዓመት የሚኾን ዕድሜውን የሚያሳልፈውም በዚህች በአንጾኪያ ከተማ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዕድሜ 330 .. ገደማ ከተወለዱት ከቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያና ከቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ እንደዚሁም 335 .. ከተወለደው ከቅዱስ ባስልዮስ ታናሽ ወንድም ከቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በዕድሜ ያንሳል፡፡ ከአባ ሆሮኒመስ ደግሞ ተቀራራቢ ዕድሜ አላቸው፡፡ በኋላ ከመንበሩ እንዲጋዝ ከሚያደርገው ከአሌክሳንድርያው ፓትሪያርክ ከቴዎፍሎስም ጋር ልደታቸው ተቀራራቢ ነው፤ ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ የሚወለደው 345 .. ላይ ነውና፡፡

Tuesday, May 17, 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፩

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 9 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ተወዳጆች ሆይ! ግንቦት 12 የተወዳጁ አባታችን የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዓመታዊ በዓለ ዕረፍት እንደ መኾኑ ስለ ሊቁ ከዚህ በፊት ከምናውቀው በተጨማሪ አንዳንድ ነገሮችን እንድንነጋገር ወድጃለሁ፡፡ በዚሁ የመጀመሪያ ክፍልም ስለ ተወለደባትና ስላደገባት ከተማ ስለ አንጾኪያ የተወሰኑ ነጥቦችን እንነጋገራለን፡፡ መልካም ንባብ!
በአራተኛ ... አጋማሽ ላይ በሮማ ክፍለ ግዛት እጅግ በጣም ከሚታወቁት ከተሞች አንዷ አንጾኪያ ነች፡፡ በተለይ ደግሞ በአሁኑ ሰዓት አንጣክያ ተብላ በምትታወቀው የደቡብ ቱርክ ውስጥ የምትገኝ የሶሪያ ልሳነ ምድር ነች፡፡
ይህቺ ከተማ 300 ... የታላቁ እስክንድር ጀኔሮችሎች አንዱ በሚኾን በሴሉከስ ቀዳማዊ ኒካቶር በደቡብ አቅጣጫ ወደሚገኝ ባሕሩ በሚፈስ ኦሮንቶስ በተባለ ወንዝ ዳር የተመሠረተች ናት፡፡ አጥሯ ግንብ ሲኾን 10 ኪሎ ሜትር ያህል ይረዝማል፡፡ በደቡብ ምሥራቅ አቅጣጫ 508 ሜትር ከፍታ ያለውና በደን የተሸፈነ ተራራ አላት፡፡ ዋናው መንገዷ በእብነ በረድ የተነጠፈ፣ በኹለቱም አቅጣጫ ኹለት ፎቅ ባላቸው ሕንፃዎች የደመቀ፣ ሌሊት ሌሊት በዘይት በሚሠሩ መብራቶች ያሸበረቀ ነው፡፡ ከተማይቱ እጅግ አስደናቂ በኾኑ ሕንፃዎች የተዋበች፣ በቂ የሚባል የውኃ ተደራሽነት ያላት፣ 18 የሚኾኑ የመዋኛ ሥፍራዎችና ቲአትር ቤቶች እንዲሁም የሰረገላ እሽቅድድም ቦታዎች የሚገኙባት ናት፡፡ ከከተማይቱ ደቡብ ምዕራብ አቅጣጫ 8 ኪሎ ሜትር ላይ ነፋሻማ ቦታ ላይ የተሠሩ ቪላ ቤቶች፣ አሁንም በጥቅም ላይ ያሉ ፏፏቴዎች፣ አፖሎ የተባለ ጣዖት ቤትና የኦሎምፒክ ውድድር በየጊዜው የሚካሔድበት ሥፍራ የሚገኙባት ከተማ ነች፡፡

FeedBurner FeedCount