Friday, May 20, 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፬

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 12 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

አባ ዮሐንስ አፈወርቅ

ከዚህ በፊት እንደገለጽነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ወደ ገዳም እንዳይሔድ የዘገየው በእናቱ ተማጽኖ ነው፡፡ 372 .. ግን እናቱ ስላረፈች ይጓጓለት ወደነበረው ገዳም ሔደ፡፡ የገዳሙ ስም ሲልፕዮስ ይባላል፡፡ ሲልፕዮስ እጅግ ጫካ የተሞላበት የጽሞና ሥፍራ ነው፡፡
ጰላድዮስ እንደሚነግረን ቅዱስ ዮሐንስ ወደዚህ እንደ ደረሰ አንድን አባት አገኘ፤ አባ ሲሲኮስ ይባላሉ፡፡ አራት ዓመትንም ከእርሳቸው ጋር ቆየ፡፡ በዚህ አራት ዓመት ውስጥ ከእኒህ አባት በዓት አጠገብ የራሱ የኾነ በዓት ነበረው፡፡ ሌሊቱን ሙሉ እንደዚሁም ከቀኑ አብዛኛውን ሰዓት በበዓቱ ያሳልፍ ነበር፡፡ አብዝቶ ይጸልያል፤ ቅዱሳት መጻሕፍትን ያነባል፡፡ በተለይ በዚህ ገዳም የጽሞና ሕይወት በእጅጉ ይተገበር ነበር፡፡ የሚተኛው በሳር በተጎዘጎዘ መሬት ላይ ነበር፡፡ የሚለብሰው የፍየልና የግመል ቆዳ ነው፡፡ የሚበላው በቀን አንዴ ሲኾን ዳቦ በጨው ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ይህ ኹልጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር የኾነው ሕይወት፡- “አዳም ከመበደሉ በፊት የነበረው ሕይወት ነውብሎ የማቴዎስ ወንጌልን ሲተረጉም 38ኛው ድርሳኑ ላይ ገልጾታል፡፡ አባ ሲሲኮስ ብዙ አምላካዊ ራዕዮችን እያዩ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የወደፊት ታላቅነቱን ዐይተዋል፡፡

Thursday, May 19, 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፫


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 11 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከሊባንዮስ ሲማር የቆየውን የንግግር ክህሎት ትምህርት የጨረሰው 367 .. ላይ ነበር፡፡ ትምህርቱ የሚያልቅበት ወራት ራሱ ሰኔ አከባቢ ሲኾን ሐምሌ፣ ነሐሴና መስከረምም የዕረፍት ጊዜ ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት 18 ዓመቱ ነበር፡፡ ዜና ሕይወቱን የጻፈው ጳላዲዮስ እንደተናገረው ቅዱስ ዮሐንስ ከጓደኞቹ ይልቅ እጅግ በጣም ከፍ ያለ ዕውቀት ያለው ነበር፡፡ በትምህርቱ ብቻ ሳይኾን ወጣትነቱም ለብዙ ሰዎች አርአያ ነበር፡፡ 
ትምህርቱን ቢጨርስም ከእናቱ ጋር ነበር፡፡ ብዙ ጓደኞች ቢኖሩትም እንደ ባስልዮስ ግን የሚቀርበው አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እድገታቸው በአንድ ሰፈር ነው፤ የተማሩት በአንድ ትምህርት ቤት ነው፤ ምግባራቸው የቀና ለብዙ ወጣቶችም አርአያ በመኾን የተመሰገኑ ናቸው፡፡ 
በኋላ ላይ ግን ከባስልዮስ ጋር ለጥቂት ጊዜያት ተለያዩ፡፡ የመለያየታቸው ምክንያትም ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ፍርድ ቤቶች እየሔደ እዚያ የሚሰጡትን ፍርዶች መስማት ያስደስተው ስለ ነበር ነው፤ የንግግር ክህሎት ከሊባንዮስ መማሩ ይህን እንዲወድ አድርጎታል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ልክ እንደ አብዛኛው የአንጾኪያ ሕዝብ ቲያትርን ይወድ ነበር፡፡ ጓደኛው ባስልዮስ ግን በእንደዚህ ዓይነት ነገር ብዙም ግድ አይሰጠውም ነበር፡፡ ባስልዮስ ይወደው የነበረው መጻሕፍትን ማንበብ ነው፡፡
ታሪክ ጸሐፊዎቹ ሶቅራጠስና ሶዞሜን እንደጻፉት፥ ቅዱስ ዮሐንስ በዚህ ጊዜ ወደ ፍርድ ቤቶች መሔዱ በኋላ የሕግ ጠበቃ ለመኾን በር ከፍቶለታል ይላሉ፡፡ በጥቂት ጊዜ ውስጥም በሚያደርጋቸው ንግግሮች በሊባንዮስና በማኅበረሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን አገኘ፡፡ የከፍተኛ ባለሥልጣናት አማካሪ፣ ሕግ አውጪ፣ አባቱ ሲያገለግልበት ከነበረው ከከፍተኛው ወታደራዊ ማዕርግ በላይ ወደ መኾን የሚያሸጋግረው ኾነ፡፡

Wednesday, May 18, 2016

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ - ክፍል ፪


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 10 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ተወዳጆች ሆይ! በክፍል አንድ ትምህርታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ ተወለደባት ከተማ ስለ አንጾኪያ ጥቂት ተነጋግረናል፡፡ እነሆ አሁን ደግሞ ወደ ሊቁ ልደትና እድገት እንቀጥል፤ መልካም ንባብ!
ከአንደበተ ርቱዕነቱ የተነሣ አፈወርቅ የተባለው ይህ ቅዱስ የተወለደው 347 .. ነው፡፡ 50 ዓመት የሚኾን ዕድሜውን የሚያሳልፈውም በዚህች በአንጾኪያ ከተማ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዕድሜ 330 .. ገደማ ከተወለዱት ከቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያና ከቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ እንደዚሁም 335 .. ከተወለደው ከቅዱስ ባስልዮስ ታናሽ ወንድም ከቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በዕድሜ ያንሳል፡፡ ከአባ ሆሮኒመስ ደግሞ ተቀራራቢ ዕድሜ አላቸው፡፡ በኋላ ከመንበሩ እንዲጋዝ ከሚያደርገው ከአሌክሳንድርያው ፓትሪያርክ ከቴዎፍሎስም ጋር ልደታቸው ተቀራራቢ ነው፤ ፓትሪያርክ ቴዎፍሎስ የሚወለደው 345 .. ላይ ነውና፡፡

FeedBurner FeedCount