Thursday, January 12, 2017

ይቅርታ



በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጥር 4 ቀን፣ 2009 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱአምላክ አሜን!
… ከሠራተኞችህ አንዱ ከአንተ መቶ ቅንጣት ወርቆችን ተበደረ እንበል፡፡ ሌላ ሰው ደግሞ ከዚህ ሠራተኛህ የተበደረው ጥቂት ብር ነበረው፡፡ ከዚህ ሠራተኛህ የተበደረው ያ ሰውም ወደ አንተ መጥቶ ቸርነትን እንድታደርግለት ለመነህ፡፡ አንተም ሠራተኛህን ጠርተህ፡- “የዚህን ሰው ዕዳ ተውለት፤ ከእኔ ከተበደርከው ዕዳህም እቀንስልሃለሁ” ብትለውና ይህ ሠራተኛህ ከዚያ በኋላ በዚያ ሰው ላይ ቢጨክንና ቢከፋ ይህን ሠራተኛ ከእጅህ ሊያድነው የሚችል ሰው አለን? እጅግ እንደ ነቀፈህ አድርገህ ቈጥረህ ብዙ ግርፋትን አትገርፈውምን? [እንዲህ ብታደርግ] እጅግ ፍትሐዊ ነው፡፡ እግዚአብሔርም የሚያደርገው እንደዚህ ነው፤ በዚያች ዕለተ ምጽአት ላይ እንዲህ ይልሃልና፡- “አንተ ክፉና ተንኰለኛ ባሪያ ያንን ሰው ይቅር ብትለው ይቅርታው የአንተ ነበርን? ለእርሱ እንድታደርግለት የታዘዝከው ከእኔ የተበደርከውን ነበር፡፡ ያልኩህ ‘ዕዳዉን ብትተውለት እኔም እተውልሃለሁ’ ነው፡፡ በእውነት እንዲህ ይህን ኹኔታ ጨምሬ ባልነግርህም እንኳን ስለ እግዚአብሔር ብለህ ዕዳዉን ትተውለት ዘንድ በተገባህ ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ ወዳጅ ኾኜ ውለታን ጠየቅሁህ እንጂ እንደ ጌታ አላዘዝኩህም፡፡ የጠየቅሁህ የእኔ ከኾነው ነው፤ ይህን ካደረግህም እጅግ በረከተ ሥጋን በረከተ ነፍስን እንደምሰጥህ ቃል ገብቼልህ ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም ልትሻሻል አልቻልክም፡፡”

ህየንተ “ወልታ ጽድቅ” - እንተ ይእቲ ሐዳስ መጽሐፍ!



በአማን ነጸረ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ 3 ቀን፣ 2009 ..)- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ባለመወድሱኩሉ ይሤኒ ለእመ አሠንይኮ – (አንተ) ለበጎ ካደረግኸው ሁሉም ለበጎ ይሆናልእንዲል ማኅበራዊ ሚዲያን (እስከ ተቻለን) ስለ ኦርቶዶክሳዊ ትውፊትም ሆነ ስለ ተቀረው አገራዊ ጉዳይ ለበጎ ዓላማ ለማዋል ሳንታትር የቀረን አይመስለኝም፡፡  ከታተርንባቸው አርእስተ ጉዳዮች ደቂቀ እስጢፋኖስንና ጥንተ አብሶን የተመለከቱ በእመቤታችን ዙሪያ እያጠነጠኑ ታሪክና ዶግማ የሚያጣቅሱ ረዘም ያሉ መጣጥፎ ይጠቀሳሉ፡፡ መረጥናቸው፡፡ አየናቸው፡፡ ከለስናቸው፡፡ በክለሳው የፍቁራን ወንድሞቼ ብርሃኑ አድማስ፣ የኄኖክ ኃይሌና የገብረ እግዚአብሔር ኪደ በቀና ልቡና የታጀበ ጥልቅ አስተያየት ታከለበት፤ ከእነርሱ በመጣ ጥቆማ መነሻነት መጣጥፎቹን በተጨማሪ ማጣቀሻ አዳበርናቸው፡፡ ዳበሩ፡፡ ተገጣጠሙ፡፡ ከግጥምጥሙወልታ ጽድቅየምትሰኝ ደንቧላ መጽሐፍ በሽልም ወጣች፤ ተወለደች! መወለዷ ጥሩ! ዜና ልደቷን ተሻግረን እስኪ የጽንሰቷን ነገር እንስማው

Saturday, July 23, 2016

ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ በ‹‹ያ! ትውልድ›› መካከል … ‹‹ሞትህ ደጅ አደረ››! ክፍል ሁለት…!

በአማን ነጸረ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 16 ቀን 2008 ዓ.ም.):- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

3. ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ… ቅድመ-ሞት፣ ጊዜ-ሞት፣ ድኅረ-ሞት...ሞትህ ደጅ አደረ!
ከሞመቱ በፊት ስብዕናውን ለመግደል ተሞከረ፡፡ ሲሞት የፓትርርክነት ወግና ሥርዓቱ ቀርቶ ሞቱን ለሙት በሚገባ ክብር ሳያደርጉለት ቀሩ፡፡ ድኅረ-ሞት ታሪኩን ለማስተሀቀር ተሽቀዳደሙ፡፡ ሞቱን፣ እረፍቱን ከለከሉት፤ ሞቱን ደጅ አሳደሩበት፡፡ ሰቆቃውን አበዙበት፡፡ ስለሰቆቃው መዛግብት ካኖሩልን ልናወጋ ጀምረናል፡፡
3.1. ቅድመ-ሞት…የተሐድሶ ጉባኤ (የኮ/ል አጥናፉ የቤተ ክርስቲያን ኮሚቴ)!
3.1.1. የ1966 ዓ.ም አብዮት እየጋመ፣ እየፋመ፣ እየተቀጣጠለ የንጉሡን ዙፋን በይፋ ለመገልበጥ 25 ቀናት ሲቀሩት ነሐሴ 11 ቀን 1966 ዓ.ም ተጠሪነቱ ለኮ/ል አጥናፉ የሆነ ‹‹ጠቅላይ ቤተ ክሕነት እስከ አሁን በምትሠራበት ደንብና ሥርዓት ሥራዋን ስትቀጥል…ከጎን ሆኖ የሚሠራ›› በሚል ሽፋን ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጥኝ ጊዜያዊ ጉባኤ›› ተቋቋመ(ድምጸ ተዋሕዶ ጋዜጣ፣ ሐምሌና ነሐሴ 1983 ዓ.ም፡ገ.7)፡፡ ይሕ ጉባኤ በቤተ ክህነት አካባቢ ‹‹የተሐድሶ ጉባኤ›› በሚል ሲታወቅ የጉባኤው አባል የነበሩት ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ ደግሞ ‹‹የኮ/ል አጥናፉ የቤተ ክርስቲያን ኮሚቴ›› ይሉታል፡፡ በወቅቱ ሸዋ ክፍለ ሀገርን ወክለው የደርግ ሸንጎ(መማክርት ጉባኤ) አባል የነበሩት ፕ/ር ጌታቸው እንዴት የኮ/ል አጥናፉ ኮሚቴ አባል እንደሆኑና የኮሚቴውን አባላት ዝርዝር ሲገልጹ ‹‹…ኮ/ል አጥናፉ አባተ ጠርቶኝ ‹ቤተ ክርስቲያን ከመንግሥት የገንዘብ ድጋፍ ወጥታ ራሷን የምትችለበትን መንገድ የሚፈልግ ኮሚቴ ልናቋቋም ነውና በአባልነት እንዲያገለግሉ እፈልጋለሁ› አለኝ፡፡ ንቡረ ዕድ ድሜጥሮስ ገብረማርያም፣ አለቃ አያሌው ታምሩ፣ ቄስ ዳኛቸው ካሳሁን፣ ዶክተር ክንፈርግብ ዘለቀ፣ አቶ ፍቅረድንግል በየነ፣ አቶ መርስዔኀዘን አበበ፣ አቶ አእምሮ ወንድማገኘሁ፣ አቶ(በኋላ ሊቀ ማዕምራን) አበባው ይግዛው የኮሚቴው አባላት እንደነበሩ አስታውሳለሁ፡፡ ኮሚቴው ሊቀ መንበር ሲመርጥ…ዶ/ር ክነፈርግብ ዘለቀ ተመረጠ›› ይላሉ(ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ፣ አንዳፍታ ላውጋችሁ፡ገ.202)፡፡ የኮሚቴው አባላት 9 ሰዎች ነበሩ ማለት ነው፡፡

Thursday, July 21, 2016

ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ በ‹‹ያ! ትውልድ›› መካከል … ‹‹ሞትህ ደጅ አደረ››! ክፍል አንድ…!

በአማን ነጸረ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 14 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የአቡነ ቴዎፍሎስ ዝክረ-ሥምዕ በቤተ ክህነቱም በአዲሱ ትውልድም ዘንድ እየተዘነጋ ሄደ፡፡እኛ ስንዘነጋው ታሪካቸው በቆናጽላን (ተሐድሶዎች) እንዳልሆነ-እንዳልሆነ ተተረከ፡፡የአቡነ ቴዎፍሎስን በመሥዋዕትነት የከበረ ታሪክ የቤ/ ታሪክ አድርጎ ለማየት ፍላጎት ጠፋ፤ሰቆቃቸው የሚዲያ ሽፋን ተነፈገ፡፡እንዲያ ተሰማኝ!ይሕን ሁሉ ችለን ሕመማችንን እንዳናስታምም ወዲህ ከቤተ ክህነት፣ወዲያ ከአብዮታውያን ወገን ያሉ ትሩፋን አበው ጭራሽ አጽመ-ቴዎፍሎስን በግፍ በወደቀበት እንበለ-ርኅራኄ አነወሩ፡፡ሲሻቸው ለቀ.. ተቆርቋሪ መስለው፣ሲሻቸው የሲሶ ግዛትን ተረክ ከለላ በማድረግ 2 ወገን በሚወረወር የብዕር ፍላጻ መቃብሩን እየፈለሱ በወደቀበት አለሳርፍ አሉት፡፡መንበሩን በግፍ ከለቀቀ 40 ዓመት የደፈነው ግፉዕ እረፍት አጣ፡፡ አላስተኛ አሉት፡፡ዘለግ ያለችውና መቼቷ 1953-1971 . የሆነው የዚህች ክታብምክንያተ-ጽሕፈትይኸው ነው--ሕማሙ፡፡የሚከተሉት አርእስት ለነዚህ ዐፅመ-ቴዎፍሎስን እንቅልፍ ለሚነሱ ልብ ሰባሪ ከሳሾች ‹‹እናንት የዛሬ ሕያዋን!ስለ ጉልበታችሁ አምላክ፤ሟች ሞቱን ይሙትበት፤ዐፅሙን ሰላም አትንሱ!›› ለማለት ያህል ከማስረጃ ጋር ተከረተሱ፡-
1.  የሲሶ ግዛት ተረክ …‹‹ሲሶ ግዛት›› ወይስ ‹‹የቶፋ ሥርዓት››?! 
2.  አብዮታዊ -አማኒነትና የአቡነ ቴዎፍሎስ ምዕዳን!
3.  ሰቆቃወ ቴዎፍሎስቅድመ-ሞት፣ጊዜ-ሞት፣ድኅረ-ሞት...ሞትህ ደጅ አደረ! 
4.  ዝክረ-ቴዎፍሎስ በአፈ-ጳጳሳት ወሊቃውንት!
የሚሉ አርእስትን መራኅያን አድርጌ በተቻለኝ መጠን ስሜቴን ገትቼ (እንዲያው መግታቱ ከሆነልኝ) የመዛግብቱን ሀቅ ለማሳየት እሞክራለሁ፤ለዚህም የአምላከ ግፉዐን ረድኤትና ጥበቃ እንደማይለየኝ አምናለሁ፡፡

FeedBurner FeedCount