Thursday, August 17, 2017

“እስክመጣ ድረስ በማንበብ ተጠንቀቅ” (1ኛ ጢሞ.4፡13)፡፡



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ 11 ቀን 2009 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
እንደ መንደርደሪያ
ኃይለ ቃሉን የተናገረው በመንፈሳዊው ትምህርት ከሕግ መምህሩ ከገማልያል፣ በዚህ ዓለም ትምህርት ደግሞ በዘመኑ እጅግ ታዋቂ ከነበረው የተርሴስ ዩኒቨርሲቲ በእጅግ ከፍተኛ ማዕረግ የተመረቀው ንዑድ ክቡር የሚኾን ጳውሎስ ነው፡፡ የተናገረው ደግሞ በመንፈስ ለወለደው ልጁ ለሊቀ ጳጳሱ ለቅዱስ ጢሞቴዎስ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለቅዱስ ጢሞቴዎስ፡- “እስክመጣ ድረስ በማንበብ ተጠንቀቅ፤ በማንበብ ተወስነህ ኑር” በማለት መንፈሳውያን መጻሕፍትን እንዲያነብ ሲመክረውም ምክንያቱን ነግሮታል፤ እንዲህ ሲል፡- “ይህን ብታደርግ ራስህንም የሚሰሙህንም ታድናለህ” (1ኛ ጢሞ.4፡16)፡፡
ስለዚህ መንፈሳዊ ንባብ ማለት ራሳችንንም የሚሰሙንንም ለማዳን - አስተውሉ! ለማዳን - መጽሐፍ ቅዱስን ጨምሮ የአበው ድርሳናትን፣ ትርጓሜያትን፣ ምክሮችን፣ ገድሎችን፣ ታሪኮችን ማንበብ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የማንበብ ግቡ እኛ ራሳችን እግዚአብሔርን ወደ መምሰል እንድናድግ ሌሎችንም ወደዚህ ምንድግና እንዲመጡ ማድረግ ነው ማለት ነው፡፡ ንባብ ብቻ ሳይኾን የማንኛውም መንፈሳዊ ግብር ዓላማም ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትና አንድነት መፍጠር ነው፡፡
ከላይ ባነሣነው የቅዱስ ጳውሎስ ቃል እንደምንመለከተው አንድ ኦርቶዶክሳዊ ኹልጊዜ በመደበኛነት ሊያነብ እንደሚገባው ያስረዳል፡፡ ጢሞቴዎስ ጳጳስ ነው፡፡ ቢኾንም ግን ማንበብ - ያውም ኹልጊዜ - መጻሕፍትን መመልከት እንዳለበት ተመከረ! ቅዱስ ጢሞቴዎስ ከሴት አያቱና ከእናቱ ከልጅነቱ አንሥቶ ቅዱሳት መጻሕፍትን ሲያነብ ያደገ ነው (2ኛ ጢሞ.3፡14-15)፡፡ አሁንም ቅዱስ ጳውሎስ ተቀብሎ ይበቃሃል ሳይኾን “በማንበብ ተጠንቀቅ” አለው፡፡

Monday, August 7, 2017

መቅረዝ ዘተዋሕዶ : የሰኞ ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ

መቅረዝ ዘተዋሕዶ : የሰኞ ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ: ገ/እግዚአብሔር ኪደ (መቅረዝ ዘተዋሕዶ ነሐሴ ፭ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም.)፡- ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም እመቤታችን ከባረከችው በኋላ ምስጋናውን የጀመረው “ፈቀደ እግዚእ…” ብሎ ነው፡፡ ፩. በ መቅድመ ወንጌል “ ወ አልቦቱ ...

Friday, August 4, 2017

ዓላማውን ያልሳተ ሕይወት

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
አንድ እኁ (ወንድም) ወደ አባ ሄላርዮን መጣና፡- “አንድ ሰው ሌሎች እርሱን የሚመስሉ አኀው ወደ ዓለም ተመልሰው ሲወድቁ አይቶ እንደ እነርሱ ላለመውደቅ ምን ማድረግ አለበት?” ሲል ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም እንዲህ አሉት፡- “አንድ ታሪክ ልንገርህ፡፡ ጥንቸሎችን ለማደ’ን የሚሮጡ ውሾችን አስብ፡፡ ከእነዚህ ውሾች መካከል አንዱ በሩቅ ያለችን ጥንቸል ተመለከታት፡፡ ወዲያውም እርሷን ለመያዝ ሩጫውን ጀመረ፡፡ አብረዉት የነበሩ ውሾችም አንዱ ሲሮጥ አይተው ጥንቸሊቱን ሳያዩዋት ተከትለውት ሮጡ፡፡ ለጊዜው አብረዉት ሮጡ፡፡ ሲደክማቸው ግን ሩጫውን አቆሙ፡፡ ማቆም ብቻ ሳይኾን እያዘገሙ ቅድም ወደ ነበሩበት ስፍራ ተመለሱ፡፡ ያ አንዱ ውሻ ግን ሩጫውን ቀጠለ፡፡

Wednesday, July 26, 2017

ሥራህን ሥራ፤ ሌሎችን እርዳ፤ የሚጠቅም ሰውም ኹን!

በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 20 ቀን 2009 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ሌሎች ሰዎችን ከማያድን ክርስቲያን በላይ የከፋ ምንም የለም፡፡ አንተ ሰው! ድኻ ነኝ የምትለኝ ለምንድን ነው? ኹለት ዲናር የጣለችዋ ሴት ትፋረድባሃለች፡፡ ከምናምንቴ ቤተ ሰብ እንደ ተወለድክ የምትነግረኝስ ለምንድን ነው? ሐዋርያትም ምናምንቴዎች ነበሩ፤ ነገር ግን ታላላቅ መኾን ተችሏቸዋል፡፡ አለመማርህን ሰበብ አድርገህ አትንገረኝ፤ ሐዋርያትም ያልተማሩ ነበሩና፡፡
ባሪያ ብትኾንም እንኳ፣ ስደተኛ ብትኾንም እንኳ ሥራህን መሥራት ይቻልሃል፤ ሌሎችን መርዳት ይቻልሃል፤ ሰዎችን ማዳን ይቻልሃል፥ አናሲሞስም እንደ አንተ ዓይነት ሰው ነበርና (ፊልሞ.1፡10-11)፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ምን ወዳለ ማዕረግ ከፍ እንዳደረገውና ምን ብሎ እንደ ጠራው አድምጥ፡- “በእስራቴ ስለ ወለድሁት፡፡”

FeedBurner FeedCount