Thursday, November 15, 2012

…………. ገሊላ እትዊ …………..


በልዑል ገ/እግዚአብሔር

ደመና በወርኃ ጽጌ በበረሃ ሰፈፍ
ከገሊላ ወጥቶ በምስር ላይ ሲከንፍ
ዝናም ጣለለት ለዚያ በረሃ ግለቱ
የሐዲስ ኪዳን ምስራች አማናዊነቱ!
የሄሮድስ ጦር
ስልምልም ነው ከእሳት አይዋጋም
አዛይቱን
አዛኝቱን እመ መለኮትን አይጠጋም!
ሕጻን ከሰማይ የወረደ ድንቅ ቸር አድራጊ
ባለ እልፍ ሠራዊት ጋሸኛ ከእኩያት ተዋጊ
ብርሃን ያጣ የጨለማ መሬት ብርሃን ወጣለት
በድርሳን ቀለም ተቀልሞለት መዝገብ ተጻፈለት
የስደቱ አንድምታ ውሃ አፍስሷልና ላያደርቀው
ደመና በበጋ በግብጽ ታይቷልና ተአምር ነው!

Wednesday, November 7, 2012

ተጐጂው ማን ነው?


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
                      (ጥቅምት 29/2005 ዓ.ም፣ በገ/እግዚአብሔር ኪደ)
  ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራው ስብከቱ ካስተማራቸው ትምህርቶች አንዱ “ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ የሚረግሙአችሁን መርቁ፤ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፤ ስለሚበድልዋችሁና ስለሚያሳድድዋችሁም ጸልዩ” የሚል ይገኝበታል /ማቴ.5፡43-44/፡፡
 ብዙዎቻችን ይህን ቃል ብናውቀውም ጠላቶቻችንን የምንወድበት፣ የምንመርቅበትና ስለ እነርሱ የምንጸልይበት ምክንያት ምን እንደሆነ ካለማስተዋላችን የተነሣ ይህን ለማድረግ እንቸገራለን፡፡ “ጌታ እንደዚያ እንድናደርግ ስላስተማረን ነው” በማለት እንደ ትእዛዝና ግዴታ ብቻ አድርገን የምንመለከተውም አንጠፋም፡፡
 ሆኖም ግን ከላይ የጠቀስነው የጌታችን ቃል እንዲህ የተባለበት የጠለቀ ምክንያት አለው፡፡ ይኸውም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጥያቄአዊ በሆነ አመክንዮ እንዲህ በማለት ያብራራልናል፡-

Tuesday, November 6, 2012

መቅረዝ -Mekrez: ስምህ

መቅረዝ -Mekrez: ስምህ:   “ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ! መንፈሳዊ ምስጋና ሁሉ ለአንተ ይገባል፡፡ ዋጋው የማይታወቅ ነጋዴ ገንዘቡን ሁሉ ሰጥቶ የተወዳጀው እውነተኛ ዕንቁ ደንጊያ አንተ ነህ፡፡ ይህንን ...

Sunday, November 4, 2012

ስለ አንድ የበግ ግልገል (ለሕፃናት)


           ወላጆች ይህን ትምህርት ለልጆችዎ ፕሪንት በማድረግ ወስደው ያንቡላቸው? 
 
ልጆች እንደምን ከረማችሁ? ትምህርትስ እንዴት ነው? ሰንበት ትምህርት ቤትስ ትሄዳላችሁ? ጎበዞች! ለዛሬ ደግሞ አንድ ቆንጆ ምክር ይዤላችሁ ስለመጣሁ በጽሞና ተከታተሉኝ፡፡ እሺ? ጎበዞች!
 ብዙ በጎች የነበሩት አንድ ሰው ነበረ፡፡ እህ… አላችሁ? ታድያ ይህ ሰው በጎቹን ሲጠብቅ በጣም ተጠንቅቆ ነው፡፡ የለመለመ ሳር ይመግባቸዋል፤ የጠራ ውኃ ያጠጣቸዋል፤ ወደ ተራራ ላይ ቢወጡ በጥንቃቄ ያወርዳቸዋል፤ የደከሙ ካሉ ደግሞ ይሸከማቸዋል፡፡ ወደ ማሳ ውስጥ እየገቡ ሳር ሲለቃቅሙ ደግሞ ባጠገባቸው ተቀምጦ ዋሽንት ይነፋላቸዋል፡፡ በጎቹም ዋሽንቱን እየሰሙ እጅግ ደስ ይላቸዋል፡፡

Saturday, November 3, 2012

የምንጽፍበት ሰሌዳ!


 በዲ/ን ዳንኤል ክብረት



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 ሁለት ጓደኞች ሞቃታማ በሆነው በረሃ እየሄዱ ነው። ብዙ ነገር እያነሡ ይወያያሉ። ታድያ የሆነ ጊዜ ወደ ክርክር ይገባሉ። አንዱ "እንዲህ ነው!" ሲል ሌላኛው "አይደለም" ይላል። "ነው" "አይደለም" "ነው" "አይደለም" እየተባባሉ ሲከራከሩ ፈርጠም ያለው ሌላኛውን በጥፊ አጮለው። በጥፊ የተመታው ደነገጠ። ቆይቶ ራሱን አረጋጋና ምንም ሳይናገር ቁጭ አለ። አጎንብሶም አሸዋው ላይ በጣቱ "ዛሬ በጣም የምወደው ጓደኛዬ በጥፊ መታኝ።" ብሎ ጻፈ። መቺው ቆሞ ያያል። ጓደኛውን በመምታቱና የተመታው ጓደኛውም ምንም ቃል አለመተንፈሱ ልቡን ነካው። ነገር ግን ይቅርታ እንኳ አላለውም።

Tuesday, October 30, 2012

ጌታ ሆይ አምናለሁ -የዮሐንስ ወንጌል የ40ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.9)


       በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  በምዕራፍ 8 እንደተመለከትን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚነግራቸውን ነገር ከማመን ይልቅ አይሁድ “ጋኔን አለብህ” /8፡48/ ብለው በድንጋይ ሊወግሩት ሽተው ነበርና አንድም “አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ” /8፡58/ ብሏቸው ነበርና ቁጣቸውን አብርዶ ቀዳማዊነቱን በገቢር (በሥራ) ያስረዳቸው ዘንድ ወደደ /መዝ.51፡4/፡፡ ስለዚህም ሲያልፍ ከመወለዱ ጀምሮ ዕውር የሆነውን ሰው (ሲለምን) አየ /ቁ.1/። ይህ ዐይነ ሰውር ሰው የዓይን ምልክት እንኳን አልነበረውም፡፡ እንዲሁ ልሙጥ ግንባር ነበረው እንጂ፡፡ ስለዚህ ሰውዬው ሳይሆን ክርስቶስ አየው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ክርስቶስ ዕዉሩን በልዩ እይታ (በፍቅርና በሐዘኔታ) እንዳየው አስተዋሉ፤ ደነቃቸውም፡፡ አስቀድሞ መጻጉዑን ሲፈውሰው፡- “ዳግመኛ እንዳትበድል” ብሎት ስለነበረ /5፡14/ “ይህ ዕዉር ሆኖ የተወለደውም ዕዉርነቱ ከበደል የተነሣ ነው ማለት ነው” ብለው አሰቡ፡፡ አሳባቸው ግን ግራ አጋባቸው፡፡ ስለዚህም፡-  መምህር ሆይ፥ ይህ ሰው ዕውር ሆኖ እንዲወለድ ኃጢአት የሠራ ማን ነው? እርሱ ነው ወይስ ወላጆቹ?” ብለው ጌታን ጠየቁት /ቁ.2/። ጌታችንም፡-እርሱ ወይም ወላጆቹ ኃጢአት አልሠሩም፡፡ ምክንያቱም እያንዳንዱ ሰው በራሱ ኃጢአት ይቀጣል እንጂ አባት ስለ ልጅ ልጅም ስለ አባት አይቀጣምና /ዘዳ.24፡16/፡፡ ታድያ እርሱ ነውን? ብትሉም አይደለም እላችኋለሁ፡፡ እንግዲያ ስለምን ዓይነ ስውር ሆነ? ብትሉም የእግዚአብሔር ሥራ (አስቀድሞ አዳምን ከምድር አፈር የፈጠርኩት ቀዳማዊ የምሆን እኔ መሆኔን) በእርሱ እንዲገለጥ ነው እላችኋለሁ /St. Ephrem the Syrian, Commentary on Tatation’s Diatessaron, 28 /፡፡

Sunday, October 28, 2012

ምክረ አበው ቁጥር አራት


ልጆቼ! ሓኪሞች ብትሆኑ፣ መሀንዲሶች ብትሆኑ፣ የሽመና ሠራተኞች ብትሆኑ፣ መርከበኞችም ብትሆኑ መልካም ነው፡፡ ይህን ጥበብ መማራችሁም ጥሩ ነው፡፡ እኔ ግን ከዚህ የበለጠ ጥበብ አሳያችኋለሁ፡፡ በዚህ (በተማራችሁት ምድራዊ) ጥበባችሁም ሌላ ጥበብ ትማሩበት ዘንድ እማልዳችኋለሁ፡፡ ሰማያዊን ጥበብ! ከላይ በገልጽኩላችሁና እናንተ በተማራችሁት ጥበብ ተጠቅማችሁ ገንዘብ ማግኘታችሁ አይቀርም፡፡ በዚህ ገንዘባችሁ ግን ድሆችን መርዳት ልመዱበት፡፡ ይህ የምነግራችሁን ጥበብ እንደ ቀላል የምታዩት አትሁኑ፡፡ መሀንዲሶች ብትሆኑ በምህንድስና ጥበባችሁና እውቀታችሁ በዚህ ምድር የሚያማምሩ ቪላ ቤቶችን ልትሠሩ ትችላላችሁ፡፡ በምነግራችሁ ጥበብ ግን
በመንግሥተ ሰማያት ውስጥ የዘላለም ቤታችሁን ትሠራላችሁ፡፡ በዚህ ምድር ለምትሠሩት ቤታችሁ በጣም ብዙ ወጪ ብዙም ድካም ይጠይቃችኋል፡፡ በምነግራችሁ ጥበብ ግን ብዙ ልፋት የለውም፡፡ ወጪአችሁ መልካምና ፈቃደኛ መሆን ብቻ ነው፡፡ በዚህ ምድር ለምትሠሩት ቤት የተለያዩ ዓይነት ብረቶችና ማቅለጫዎች እንዲሁም የከበሩ ድንጋዮችን ትጠቀማላችሁ፡፡ በምነግራችሁ ጥበብ ግን ይህ ሁሉ አያስፈልጋችሁም፡፡ የሚያስፈልጋችሁ ብሎን ወይንም ብረት ወይንም የከበረ ድንጋይ ሳይሆን መልካም ምግባራችሁና በጎ ፈቃዳችሁ ብቻ ነው፡፡

FeedBurner FeedCount