Showing posts with label ውሉደ ብርሃን ትሆኑ ዘንድ በብርሃን እመኑ - የዮሐንስ ወንጌል የ፵፯ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.፲፪፡፴፬-፶). Show all posts
Showing posts with label ውሉደ ብርሃን ትሆኑ ዘንድ በብርሃን እመኑ - የዮሐንስ ወንጌል የ፵፯ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.፲፪፡፴፬-፶). Show all posts

Wednesday, July 17, 2013

ውሉደ ብርሃን ትሆኑ ዘንድ በብርሃን እመኑ - የዮሐንስ ወንጌል የ፵፯ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.፲፪፡፴፬-፶)

በገ/እግዚአብሔር ኪደ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ ሐምሌ ፲ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም)፡- ውሸት በእልፍ የሚያማምሩ ሕብረ ቀለማት ብትቀባም ውሸትነቷ ከመታወቅ አታመልጥም፡፡ ያረጀና ያፈጀ ግድግዳም ምንም ያህል በሚያምር ቀለም ቢቀባም አዲስ መሆን አይችልም፡፡ የሚዋሽ ሰውም እንደዚሁ ነው፡፡ ምንም ያህል ውሸቱን እውነት በሚመስሉ ውብ ቃላት ቢያሽሞነሙነውም ውሸታም መሆኑ በቀላሉ ይታወቃል፡፡ በአይሁድ ሕዝብ ዘንድ የምናስተውለውም ይኸንኑ ነው፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደሆነ ሁሉን (በአሚን) ወደ እኔ እስባለሁ” ሲላቸው /ቁ.፴፪/ እነርሱ ግን መልሰው፡-እኛስክርስቶስ (በመሲሑ) ሞት እንደሌለበት፣ ለዘለዓለምም እንደሚኖር በኦሪት ሰምተናል /መዝ.፻፱፡፬፣ ኢሳ.፬፡፮፣ ሕዝ.፴፯፡፳፮፣ ዳን.፯፡፲፫-፲፬/፤ አንተስ የሰው ልጅ ክርስቶስ ይሰቀል ዘንድ አለው እንደምን ትላላህ? ይህ የሰው ልጅ ክርስቶስስ ማን ነው?” ይሉታልና /ቁ.፴፬/። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን አንቀጽ በተረጐመበት ድርሳኑ እንዲህ ይላል፡- “ምንም እንኳን እነዚህ ሰዎች መሲሑ (ክርስቶስ) ለመዘኑ ኅልፈት ለመንግሥቱም ሽረት የሌለበት ዘለዓለማዊ መሆኑን ከተለያዩ መጻሕፍተ ብሉያት ቢያነቡም፣ እዚያው ዘለዓለማዊነቱን ባነበቡበት ቦታ ላይም ለሰው ልጆች ሲል ስለሚደርስበት መከራ መስቀልና ስለ ትንሣኤው ጨምረው አንብበዋል፡፡ ‘ተጨነቀ ተሣቀየም አፉንም አልከፈተም፤ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፥ በሸላቶቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም’ /ኢሳ.፶፫፡፯/፤ ‘ይሁዳ የአንበሳ ደቦል ነው፤ ልጄ ሆይ፥ ከመሰማርያህ ወጣህ፤ እንደ አንበሳ ተኛህ እንደ ሴት አንበሳም አንቀላፋህ እንደ አንበሳ ደቦልም የሚቀሰቅስህ የለም’ /ዘፍ.፵፱፡፱/ እና የመሳሰሉት ቃላት ደጋግመው አንብበዋቸዋል፡፡ ነገር ግን ጌታችን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ (መሲሑ) አይደለም ለማለት ስለፈለጉ ብቻ ‘እኛስ በመሲሑ ሞት እንደሌለበት፣ ለዘለዓለምም እንደሚኖር በኦሪት ሰምተናል’ ይላሉ፡፡ የመሲሑ ሞት ዘለዓለማዊነቱን የሚጻረር አስመስለው ለማቅረብ ይሞክራሉ፡፡ አንዱን ጫፍ ብቻ በመያዝም ወደ ስሕተት ይነጉዳሉ፡፡ ‘ከፍ ከፍ ያልሁ እንደሆነ’ ሲላቸው ‘እሞታለሁ እሰቀላለሁ’ ማለቱ እንደሆነ ስለገባቸው ‘አቤቱ ሆይ! ስለመሲሑ የምናውቀው አሁን እንደነገርንህ ነው፡፡ ስለዚህ አሁን ይሞታል ይሰቀላል የምትለው መሲሕ ፈጽመን አናውቀውም (አንተን አናውቅህም) ይሉታል” ይላል /St. John Chrysostom, Homily LXVIII/፡፡ ዓምደ ሃይማኖት የተባለው ቅዱስ ቄርሎስም “ከመጻሕፍት ጥቅስ በመጥቀስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረው ትምህርት ሐሰት ነው ለማለት ይጥሩ ነበር” ይላል /St. Cyril of Alexandria, Commentary on The Gospel of John, Book 8/፡፡

FeedBurner FeedCount