Showing posts with label የጥበብ ትሩፋት. Show all posts
Showing posts with label የጥበብ ትሩፋት. Show all posts

Thursday, April 28, 2016

ደም ለበሰች

ያቺ ውብ ጨረቃ በጣም የደመቀች
                ውቢቷ ጨረቃ፤
ደም ለበሰች አሉኝ
             በኃይል ተጨንቃ፡፡
እርቃኑን ሲያስቀሩት የዓለም ፈጣሪ
    ከላይ ተመልክታ ከልቧ አዘነች፤
ይህን አላደርግም ድምቀቴ በሱ ነው
                ብላ ራሷን ጣለች፡፡
ደሙ ሲፈስ አይታ፤
ህመም ግርፋቱን እሷም ተመልክታ፤
ጌታ ሲንገላታ፤
አይ አይሆንም አለች
          አይኖቿን ጨፈነች፤
የጭንቀቷ ብዛት
         እሷም ደም ለበሰች፡፡

Saturday, September 26, 2015

መስቀል ኃይል

በልዑል ገብረ እግዚአብሔር
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 15 ቀን 2008 ዓ.ም.)፦ በስመ አብ ወወልድ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

የአዳም ነገር……
በቀራኒዮ መሐል ቀጠሮ ተይዞለታል
የገመጣት ፍሬ መዘዝ ወልዳ
ከሰገነት……...ቁልቁል ሰድዳ
ብርሃን ልብሱ ተገፎበት
ልበ ምቱ……..ቀንሶበት
ክብሩን ሊመልስለት
…….የማይሻረው ቃልን ሰጥቶታል!

የእሳት አጥር ጉድጓድ ጨለማ ቤት ሰፍፎ
ለዚህ አልነበረም…….ተፈጥሮው
በሲኦል ከተማ መጋኛ ሊመታው
ያ የሰው በኩር የፊጥኝ ታስሮ
በዲያቢሎስ ቀንበር ተቀንብሮ
እሳቱን ሲያሳርሰው በጅራፍ ጀርፎ
ባርነትን ተፈራርመው
………………..ፀጋ ልብሱን ገፍፎ ገፍፎ!

ዋይ! ዋይ! ዋይ!
የሲቃ ድምፀት ምህረት የለሹ እኩይ ግዛት
አዳም እንጂ የተጎዳ…
እበላለው ብሎ የተበላ
…………..እወጣለው ብሎ የወረደ
በፍቃዱ …….
ከግዛቱ ወደ ግዞት ተሰደደ ተዋረደ

Sunday, July 26, 2015

....... ሰላም ገብርኤል.......



በልዑል ገ/እግዚአብሔር
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 19 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!


ሰላምታየሰላማዊ አካል ስጦታ
................
በጎነት አክብሮት ምሣሌው
የታላቅነት ትርጓሜ የሰሪውን ማንነት
...........
አንድ የመሆን ምስጢር ሲለው

ሰላም...!
ነገረ ፈጅ የእስራኤል ባለጠጋ
.........
መመረቅ መርገም ቢችልበት
ባላቅ ደስ ሊለው...
የፀጋውን ስጦታ ቅዱሱን ሊረግምበት
..............
አህያውን ይዞ ተጓዘበት

Monday, May 18, 2015

ይድረስ ለሯጩ ወንድሜ

በአሃ ገብርኤል
ከዓምደ ሃይማኖት /ሰ/ት/ቤት
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ግንቦት 11 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
        ይድረስ ለወንድሜ ተስፋ እግዚአብሔር! እንደምን ሰንብተኻል? እኔ ቸሩ እግዚአብሔር ይመስገን ደኅና ነኝ፡፡ “በተመረቅኩት ሥራ ብዙ ዓመታት መሥራቴን ታውቃለኅ፡፡ አኹን ግን ትቼው አትሌት ኾኛለኁ፡፡ ለመኾኑ ሯጭነት ኃጢአት ነውን?” ብለኽ የጻፍክልኝ ደብዳቤ ደርሶኛል፡፡
        ውድ ወንድሜ! ሩጫችን ይለያያል እንጂ ኹላችንም ሯጮች ነን፡፡ በርግጥ የሚገባና የማይገባ ሩጫ እንዳለ ልትዘነጋ አይገባም፡፡ ጥያቄኽ የኹላችንም ጥያቄ በመኾኑ የጥያቄአችን መልስ የሚኾነን ደግሞ ቃለ እግዚአብሔር ነው፡፡ ታስታውስ እንደኾነ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ከኾንን በኋላ በጕባኤ “ታገኙ ዘንድ ሩጡ” /1ኛ ቆሮ.9፡24/ በሚል ርእስ ተምረን ነበር፡፡ ዛሬ አንተ ሯጭ ኾነህ በምሳሌ የተማርነውን በተግባር እያስታወስከው እንድትማርበት ዕድሉን በማግኘትህ ደስ ልትሰኝ ይገባኻል፡፡

Saturday, November 15, 2014

አብሬሽ ልመለስ



በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ቅዳሜ ኅዳር 6 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ከክብር ማረፊያው ከገሊላው ቤትሽ
ሰማሁ መፍለስሽን ወደ ግብጽ ወደ ኩሽ
ፀሐይ ሲያከትራት ያቺን የበረሃ ዖፍ
ጼዋዌን ስትናፍቅ ላንዲት ቅጽበት ሳታርፍ
ሰማሁኝ ስደቷን መጠጊያ ሳታገኝ በልቤ ላይ ስታልፍ

Thursday, October 2, 2014

ሰላም ተዋሕዶ

በብጹዕ አቡነ ጐርጐርዮስ ካልዕ የሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩ


ሰላም ተዋሕዶ ሰላም ኦርቶዶክስ
የአትናቴዎስ ሐውልት የዲዮስቆሮስ፡፡
  የአዳም መመኪያ የሔዋን ሀገር
  አንቺ አይደለሽም ወይ የቅዱሳን ክብር?
በከንቱ የሞተው የአቤል መሥዋዕት
የኄኖክ ሃይማኖት የአዳንሽው ከሞት
አንቺ የኖኅ መርከብ የሴም በረከት፡፡
  በአብርሃም ድንኳን ተወልደሽ ያደግሽ
  የይስሐቅ መዓዛ ወደር የሌለሽ
  ያዕቆብ በሕልሙ በቤቴል ያየሽ
  የዮሴፍ አጽናኙ ተዋሕዶ አንቺ ነሽ፡፡

Friday, September 19, 2014

"እርግና"



በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 9 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

የእድሜ ጅራፍ ግርፋቱ = ከግንባሬ
የክብር ሸማ ሽበቱ = ከጠጉሬ
የአዝማናት ፍኖት ንቃቃት = ተረከዜ
የምድር ሩጫ ሥጦታ = "ደም- ወዜ"
ለቁጥር መሳፍርት = ብልጥግና
ዳግም ለንሰሃ ............ ዳግም ለምስጋና
ጊዜ ለእርጋታ..... ጊዜ ለጥሙና
ፍፃሜ መዋዕል ......... ድህረ ውርዝውና

Tuesday, September 9, 2014

ዘመኔን አድሰው


በወርቅነሽ ቱፋ
ይኸው
ሩቅ ያልኩት ቀረበ፥ ነገ ዛሬ ሊኾን፥ መጣ እየበረረ፤
በለስ ሕይወቴም ሲፈተሸ፥ ምንም አላፈራ፥ አላዘረዘረ፡፡

Thursday, November 15, 2012

…………. ገሊላ እትዊ …………..


በልዑል ገ/እግዚአብሔር

ደመና በወርኃ ጽጌ በበረሃ ሰፈፍ
ከገሊላ ወጥቶ በምስር ላይ ሲከንፍ
ዝናም ጣለለት ለዚያ በረሃ ግለቱ
የሐዲስ ኪዳን ምስራች አማናዊነቱ!
የሄሮድስ ጦር
ስልምልም ነው ከእሳት አይዋጋም
አዛይቱን
አዛኝቱን እመ መለኮትን አይጠጋም!
ሕጻን ከሰማይ የወረደ ድንቅ ቸር አድራጊ
ባለ እልፍ ሠራዊት ጋሸኛ ከእኩያት ተዋጊ
ብርሃን ያጣ የጨለማ መሬት ብርሃን ወጣለት
በድርሳን ቀለም ተቀልሞለት መዝገብ ተጻፈለት
የስደቱ አንድምታ ውሃ አፍስሷልና ላያደርቀው
ደመና በበጋ በግብጽ ታይቷልና ተአምር ነው!

Thursday, July 12, 2012

.......ብርሃናተ ዓለም......





ማነው በሁለት እግሩ ዓለምን የዞረ
ጽፎ ተናግሮ ዘክሮ ወንጌል የነገረ?
ይህች አለት ናት የቤቴ መሠረት
በሷ ቤቴን ሰራሁ ኮኩሐ ሐይማኖት

አባቴ ዼጥሮስ ...
እስኪንገረኝ...
የቱ ይበልጣል?
መረብ በባህሩ መወርወር
ወንጌል ለዓለሙ መናገር ?
ዓሣን ....ማደን
ሕዝብን ማዳን?
የቱ ይበልጣል አባቴ ...?
በጀልባ መዋሉ
ጌታን ማገልገሉ?

ተወው ዼጥሮስ ...
ለካ እኔ ሞኙ
ያልገባኝ ምስጢሩ
የበለጠውን በተግባር ነግረኸኝ
ዓለምን ተፍተህ ሞተህ አሳየኸኝ

ወዮ!......ወዮ!...
ወዮልሽ ሮም!
የኒሮን ዓለም
የቄሳሮች ሃገር
የግፍ ድንበር
የደም ባህር

ወዮልሽ ሮም ...
የዼጥሮስ ስቅለት ክስ ይሁንብሽ
የቅዱሱ ችንካር ምስክር ይጥራብሽ
በእጇ ያለ ወርቅ
............ሮም አልደመቀችበት

Wednesday, June 27, 2012

መርከቤ- በልዑል ገ/እግዚአብሔር!


የሰማይ መስኮት ተከፈተ
የፀሐይ ውበት ተከተተ
ነጎድጓድ ተደባለቀ
መብረቅ ተባረቀ
የምድር ፍልቅልቂት ፈሰሱ
የውሃ ቆሬዎች ተቸለሱ

እንዴ...
መሬት ከውሃ ነው
..........................
የተሰራች ?
መሠረቷ ግድግዳዋ
......................
ማይ የሆነች!

ግራ ቀኙ ጎርፍ
ላይ ታቹ ዝናመ ዶፍ
አለ ጣይ በረዶው ተኮሰ
ዝርጉ ባህር ተን ተነፈሰ
እምቡቅ እምቡቅ
ማየ አይህ መረቅ

ክምችት የውቅያኖስ ሙላት
ነፈረ ተንተከተከ ምድርን አጋላት

እንጃልኝ....
ከሥጋ ከእፁ ከፍጥረቱ
አንዱም ላይተርፍ ከጥፋቱ

አቤት ቁጣ...
ለምን ሰማይ ጎረፈ
ሙላቱ እስተላይ ሰፈፈ?
ክህደቱ:-
የጠፈሩን ቧንቧ ከፈተው
የእልቂቱን ዝናም አዘነመው
ሀጥያቱ:-
የምድርን ምድጃ ለኮሰው
የረጋውን ውሃውን አጋለው

እንግዲህ...
ክህደት ከሀጥያት ከተራመደ
ጎርፍ ከንፍር ተዛመደ

አይኔ እያየ...
ፍጥረት በውሃ ሲወሰድ
በሞቀባት መሬት ሲነድ

እኔ ግን...
የማትሰጥመውን ተመለከትኩ
የማትበገረውን ተከተልኩ
ጎፈር እንጨት በዙሪያዋ
አልቦ ሽንቁር መለያዋ
በጉርጆች የተሰራች
በለምለሞች የተዋበች

ውብ መርከብ መዳኛ
ስርግው ልሂቅ ተአምረኛ
ጣራ ክዳኗን ዶፍ አልበሳው
ግድግዳዋን ግለት አልበገረው
ነፋስ አውሎው አልቀየሳት
ሞገድ ማዕበል አልሰበራት

ተገረምኩ...
እኔስ:-
አይኔን አላሸሁ
ኋላዬን አላየሁ
ስራዬማ...
አካሌ ዋና አይችልም
ሰውነቴ ንፍር አያልፍም

ተፈሳህኩ ርኢክዋ
ለሐመር የዋህ

ገባሁ...
በታላቋ መርከብ ተከለልኩ
ከስጥመት ከንፍረት ተሰወርኩ

ገረምክኒ...
በጣራዋ ታቅፌ
በአጥሯ ተደግፌ
ወገኔ...
ከውስጥ ሲገቡባት
በክዳኗ ሲጠለሏት
ለካ...
ሐሴት
ድህነት
እናት ናት::

ተደሰትኩ...
ሳይ:-
ከውስጥ ወደ ደጅ
ፍጥረት ሲሰጥም ሲፈጅ

ምስኪን...
'
ዋና እችላለሁ' ያለ
...................
ሲሰጥም አየሁት
'
ንፍር አይበግረኝ' ያለ
...................
ሲቀቀል አየሁት

መርከቢቷ ተንሳፈፈች ቀዘፈች
ውስጧ አይሞላ ለሁሉ ነች::

እኔስ...
በመርከቤ አለሁ
ከጥፋቱ እድናለሁ::
..........=//=.........


(
ሰኔ21/2004..)


FeedBurner FeedCount