Showing posts with label ለሕፃናት. Show all posts
Showing posts with label ለሕፃናት. Show all posts

Tuesday, December 2, 2014

ስለ እመቤታችን ልደት (ለሕፃናትና ዠማሪዎች)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ማግሰኞ ኅዳር 23 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!


ውድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዴት ሰነበታችኁ? እግዚአብሔር ይመስገን ደኅና ነን አላችኁ? አሜን፡፡ እኔም በጣም ደኅና ነኝ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡
 ልጆች! ባለፈው ጊዜ ስለምን እንደተማማርን ታስታውሳላችኁ? አቤል እና ቃየን ስለሚባሉ ኹለት ወንድማማቾች አይደል? ጐበዞች! ትክክል ናችኁ፡፡ ዛሬ ደግሞ ኹላችንም ስለምንወዳት ስለ እናታችን ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ልደት እነግራችኋለኹ፡፡ ለመስማት ዝግጁ ናችኁ አይደል? ጐበዞች፡፡ እግዚአብሔር ዕውቀቱን ይግለጥልን፡፡ አሜን!!!

Wednesday, October 29, 2014

ስለ አቤልና ቃየን (ለሕፃናት)

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጥቅምት 20፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የተዋሕዶ ፍሬዎች፣ የሃገር ተስፋዎች እንደምን ሰነበታችኁ ልጆች? “እግዚአብሔር ይመስገን ደኅና ነን” አላችችኁ? መልካም፡፡ ትምህርት እንዴት ነው? እየጐበዛችኁ ነው አይደል? ጠንከር ብላችኁ በማጥናት ከአምናው የተሻለ ውጤት ለማምጣት እንደተዘጋጃችኁ ተስፋ አደርጋለኹ፤ በርቱ እሺ?
  ዛሬ አቤል እና ቃየን ስለሚባሉ ኹለት ወንድማማቾች ታሪክ ነው ይዤላችኁ የመጣኹት፡፡ ለመስማት ዝግጁ ናችኁ አይደል? በጣም ጥሩ!!!
 አዳምና ሔዋን በገነት ይኖሩ ነበር፡፡ ሲበድሉ ግን እግዚአብሔር ከገነት አስወጣቸው፡፡ ደብር ቅዱስ ወደ ተባለ ቦታም ተሰደዱ፡፡ ከዚኽ ቦታ ኾነውም የገነት ሽታ እየሸተታቸው ይኖሩ ነበር፡፡ ወደ ገነት ግን መቅረብ አልተቻላቸውም፡፡ ሦስት ዓመት ሙሉም በጣም ያለቅሱና ያዝኑ ነበር፡፡

Sunday, October 12, 2014

ስለ አዳምና ሔዋን (ለሕፃናት)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጥቅምት 03 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
       
የእግዚአብሔር ልጆች እንደምን ሰነበታችኁ? ደኅና ናችኁ? ትምህርት እንዴት ነው? ጐበዞች፡፡

ባለፈው ጊዜ ስለ ምን እንደተማርን ታስታውሳላችኁ ልጆች? ጐበዞች፡፡ የተማማርነው ስለ ሥነ ፍጥረት ነው አይደል? እስኪ ካስታወሳችኁ አዳምና ሔዋን መቼ ተፈጠሩ ነበር ያልነው? ጐበዞች፡፡ ልክ ናችኁ፡፡ ዓርብ ነበር የተፈጠሩት፡፡ ዛሬ ደግሞ ስለ አዳምና ስለ ሔዋን ታሪክ እነግራችኋለኁ፡፡ እናንተም ለመስማት ዝግጁ ናችኁ አይደል? ጐበዞች፡፡ 

Monday, September 29, 2014

ሥነ ፍጥረት (ለሕፃናት)- ክፍል ኹለት



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 19 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 እንደምን ናችኁ ልጆች? ትምህርት በደምብ ዠመራችኁ? እንዴት ነው ታድያ ትምህርት? በጉጉት እየተከታተላችኁ ነው አይደል? ጐበዞች፡፡ አኹን የምትማሩት ትምህርት ለወደፊት ኑሮአችኁ መሠረት በመኾኑ ተግታችኁ ተማሩ፤ እሺ?! እግዚአብሔር ብርታትን እንዲሰጣችኁ፣ የእናንተንና የቤተ ሰቦቻችኁ ጤንነት እንዲጠብቅላችኁም ዘወትር ጸልዩ፡፡ እግዚአብሔር ጸሎታችኁን እንዲሰማችኁም ለወላጆቻችኁና ለታላላቆቻችኁ በቅንነት ታዘዙ፡፡ ይኽን ካደረጋችኁ፥ ዕቅዳችኁና ምኞታችኁ ይሳካላችኋል፡፡
 ልጆች! ባለፈው ሳምንት የተማርነውን ታስታውሳላችኁ? እስኪ ምን ምን ተማርን? ጐበዞች!!! ጥያቄውንስ ሠራችኁት? ስንት አመጣችኁ? እናንተ ጐበዞች ስለኾናችሁ ደፍናችኁታል አይደል? በጣም ጐበዞች፡፡ ለዛሬ ደግሞ እግዚአብሔር ረቡዕ፣ ሐሙስ እና ዓርብ ምን ምን እንደፈጠረ እንማራለን፡፡ እግዚአብሔር ልቡናችንን ይክፈትልን፡፡ አሜን!!!

Monday, September 22, 2014

ሥነ ፍጥረት (ለሕፃናት)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 12 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ልጆች እንደምን ከረማችኁ? የዕረፍት ጊዜአችኁ እንዴት አለፈ? መልካም ልጆች፡፡ እንግዲኽ ዘመነ ማርቆስ አልፎ አኹን ዘመነ ሉቃስ ገብተናል፡፡ ለአዲሱ ዓመት ያደረሰንን አምላክ እያመሰገንን በዚኽ ዓመት ደግሞ ጊዜያችንን በአግባቡ ተጠቅመን፣ በትምህርታችንም በርትተን ለጥሩ ውጤት መብቃት አለብን እሺ፡፡ ምክንያቱም ጊዜውን በአግባቡ የማይጠቀም ልጅ መጨረሻው አያምርም እሺ ልጆች፡፡ ስለዚኽ ጊዜአችንን በአግባቡ መጠቀም አለብን፡፡ ለዚኽም እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

Sunday, November 4, 2012

ስለ አንድ የበግ ግልገል (ለሕፃናት)


           ወላጆች ይህን ትምህርት ለልጆችዎ ፕሪንት በማድረግ ወስደው ያንቡላቸው? 
 
ልጆች እንደምን ከረማችሁ? ትምህርትስ እንዴት ነው? ሰንበት ትምህርት ቤትስ ትሄዳላችሁ? ጎበዞች! ለዛሬ ደግሞ አንድ ቆንጆ ምክር ይዤላችሁ ስለመጣሁ በጽሞና ተከታተሉኝ፡፡ እሺ? ጎበዞች!
 ብዙ በጎች የነበሩት አንድ ሰው ነበረ፡፡ እህ… አላችሁ? ታድያ ይህ ሰው በጎቹን ሲጠብቅ በጣም ተጠንቅቆ ነው፡፡ የለመለመ ሳር ይመግባቸዋል፤ የጠራ ውኃ ያጠጣቸዋል፤ ወደ ተራራ ላይ ቢወጡ በጥንቃቄ ያወርዳቸዋል፤ የደከሙ ካሉ ደግሞ ይሸከማቸዋል፡፡ ወደ ማሳ ውስጥ እየገቡ ሳር ሲለቃቅሙ ደግሞ ባጠገባቸው ተቀምጦ ዋሽንት ይነፋላቸዋል፡፡ በጎቹም ዋሽንቱን እየሰሙ እጅግ ደስ ይላቸዋል፡፡

Wednesday, August 22, 2012

በአዲሲቷ ቆሮንቶስ መኖር(ለሕፃናት)!


  እንደምን አላችሁ ልጆች? ጾመ ፍልሰታ እንዴት አለፈ? ጾማችኋል አይደል? ጐበዞች!
ለዛሬ አንድ በጣም ጣፋጭ ታሪክ ይዤላችሁ ቀርቤአለሁ፡፡ ለመስማት ዝግጁ ናችሁ አይደል? ጐበዞች!
   ከዕለታት በአንዲቱ ቀን ማርቆስ ሁል ጊዜ ከሚያጠናባት ክፍል ተቀመጠና መጽሐፍ ቅዱስን አንሥቶ የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች ምዕራፍ 13 ላይ ስለ ፍቅር ማንበብ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ደጋግሞ ቢያነበውም ፍቅር ምን ማለት እንደሆነና እንዴት ተግባራዊ እንደሚደረግ አልገባ አለው፡፡ እያሰላሰለ ሳለም በተቀመጠበት ወንበር እንቅልፍ ወሰደውና ደስ የሚል ሕልም አየ፡፡ ከነቃ በኋላም ያየውን ሕልም በወረቀት እንዲህ ብሎ ጻፈው፡-
“የሆነ አንድ ፌርማታ ላይ የአውቶብሳችንን መምጣት እየጠበቅኩ የነበርኩ ይመስለኛል፡፡ ከጎኔም አንድ ሰውዬ እንደኔ አውቶብስ ሲጠብቅ ቆሞ አየሁኝ፡፡ ሰውዬውም፡- እኔ ጋር ና አለኝ፡፡ እኔም ሄድኩና አንድ ላይ ተሳፈርን፡፡ ፊት ለፊትም እየተያየን ተቀመጥን፡፡ አውቶብሳችን መንቀሳቀስ ጀመረች፡፡ ከተወሰኑ ደቂቃዎች በኋላም አውቶብሳችን የመጀመርያው ፌርማታ በምትሆን “አዲሲቷ ቆሮንቶስ” በምትባል ስፍራ ደረስን፡፡ ሁለታችንም ወረድን፡፡ አንድ ላይ በእግር እየተንሸራሸርን ሳለ (Walk እያረግን ሳለ) ሰውዬውን ቀና አልኩና ትኩር ብዬ ተመለከትኩት፡፡ እርሱም ፈገግ ብሎ አየኝ፡፡ በፊቱ የሆነ የሐሴትና የደስታ ነገር ይነበባል፡፡ እኔም በውስጤ ደስ የሚል ስሜት ተሰማኝ፡፡ በዚያ አከባቢ እንደኛ ሲንሸራሸሩ የማያቸው ሰዎች ሁሉም በእርጋታ ቀስ ብለው ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ሳስተውላቸው አንድ ሰው ስንኳ ፊቱ የተቋጠረ የለም፡፡ እኛም ከትንሽ ደቂቃዎች በኋላ የፍቅር አደባባይ ወደተባለ አደባባይ ደረስን፡፡ በአደባባዩ መኻከል ላይ አንድ ትልቅ የውኃ ፏፏቴ (ፋውንቴን) ይታያል፡፡ አደባባዩ ዙርያው በትልልቅ ሥዕሎች (ቢል ቦርዶች) ተሞልቷል፡፡ ሰውዬም በጣቱ ወደ አንድ ሥዕል እየጠቆመ፡- “እዛ ጋር ያለው ትልቁን መስቀል አየኸው? ይህ ሥዕል የክርስቶስን ነገረ ስቅለት የሚያሳይ ሥዕል ነው” አለኝ፡፡ እኔም ክርስቶስ የተሰቀለበትን ሥዕል ለማየት ቀና ስል ወዲያው እንዲህ የሚል ጽሑፍ ከስሩ አነበብኩኝ፡- “ነፍሱን ስለ ወዳጆቹ ከመስጠት ይልቅ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም” /ዮሐ.15፡13/፡፡ ከአጠገቡ ወደ ነበረው ሌላ ሥዕል ስመለከት ቀዳሜ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ በጉልበቱ ተንበርክኮ ሲጸልይ አየሁት፡፡ ሲጸልይ የተናገራቸው ቃላትም ከሥዕሉ ግርጌ እንዲህ ተጽፈዋል፡- “ጌታ ሆይ ይህን ኃጢአት አትቁጠርባቸው” /ሐዋ.7፡60/፡፡ ዐይኔን ወደ ሌላኛው ማዕዘን ሳሻግረው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልጇ ወዳጇን ታቅፋ አየኋት፡፡ እመቤታችን ያቀረበችው የምስጋና መዝሙርም እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፡- “ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች፡፡ መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደረጋለች፡፡ የባርያይቱን ውርደት ተመልክቷልና፡፡… ብርቱ የሆነ እርሱ በእኔ ታላቅ ሥራን አድርጓልና ስሙም ቅዱስ ነው” /ሉቃ.1፡46-49/፡፡ ወደ ሌላኘው ማዕዘን ዐይኔን ሳማትር የጠፋው ልጁን ለመቀበል ሐሴት የሚያደርገውን አባት ተመለከትኩት፡፡ በዚያም እንዲህ የሚል ጽሑፍ ነበረ፡- “እንብላ ደስም ይበለን፤ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኗል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቷልም” /ሉቃ.15፡23-24/፡፡
  ከዚያ በኋላ የሆነ መቀመጫ አገኘንና አንድ ላይ ተቀመጥን፡፡ ሰውዬውን “አደባባዩን በጣም ወደድኩት” አልኩት፡፡ ሰውየውም ሐሳቤን በአወንታ ተቀብሎ ራሱን ነቀነቀና እንዲህ አለኝ፡- “አየህ ልጄ! በዚህ አደባባይ ቂም በቀል የሚባል ነገር አይታወቅም፡፡ አንዱ በአንዱ አይቀናም፡፡ ሰላም ሲባባሉ ራሳቸውን ጐንበስ አድርገው በትሕትና ነው፡፡ ፍቅራቸው በጣም ልዩ ነው፡፡ ጌታ እንዳስተማረው እዚህ የምታየው ሰው ሁሉ ባደረገው ነገር “እኔ እኮ እንዲህ አደረግኩ” ብሎ አይመካም፡፡ ሁሉም ተራ በተራ ይደማመጣሉ እንጂ አንድ ሰው ስንኳ ድምጹን ከፍ አድርጎ አይናገርም፡፡ አንድ ስንኳ ተቈጥቶ የሚናገር የለም፡፡ እንደ አንተ ዓይነት ሕፃን በዚህ ቦታ ወይም በመማርያ ክፍል ከጓደኞቹ ጋር ከተቀመጠና እየተናገረ ከሆነ ሁሉም በጽሞና ያደምጡታል፡፡ እርሱም ሌሎች ሕፃናት ሲናገሩ በጽሞና ያደምጣቸዋል፡፡ ከጓደኛቸው አንዱ ምናልባት የተለየ ሐሳብ እንኳን ቢኖረው ያሳምናቸዋል እንጂ የእኔ ብቻ ነው ትክክል አይላቸውም፡፡ አሁንም ሌላ ሕፃን ምናልባት… ምናልባት ተሳስቶ ልክ ያልሆነ ነገር ቢናገር ቀስ አድርገው ልክ የሆነውን ይነግሩታል እንጂ ማንም ስለተሳሳተ አይስቅበትም፡፡ በቃ! እንዲህ እያደረጉ እከሌስ ጥሩ ልጅ አይደለም ተብሎ ሰው ሲያወራለት የነበረው ልጅ በአንዴ ይለውጡታል፡፡ እርሱም ጐበዝ ልጅ ይሆናል፡፡ ተራ በተራ ሁሉም ከተናገሩ በኋላ በአንድ ሐሳብ ተስማምተው ይጨርሳሉ፡፡ ሲጨርሱም ሁሉም ተቃቅፈው እየተጫወቱ ይሄዳሉ፡፡ ሲጫወቱ ደግሞ ሐቅ ሐቁን ብቻ ይነጋገራሉ እንጂ አይወሻሹም፡፡ የሚደባበቁት ምንም ነገር የላቸውም፡፡ አንዱ በሚናገረው ነገርም ሌላው ያምኗል፡፡ እናም በቃ ሁሉም ነገር የሚያደርጉት በፍጹም ፍቅር ነው፡፡ ወደየቤታቸው ሲገቡም ተጨባብጠው ደኅና እደሩ ተባብለው ይለያያሉ፡፡”
 ከዚህ በኋላ ሰውዬውን፡-“ወይኔ! ሁል ጊዜ እዚህ በሆንኩኝ? ከእነዚህ ልጆች ጋር መጫወት እፈልጋለሁ?” አልኩት፡፡ ሰውዬውም ልብ ውስጥ በሚዘልቅ ፈገግታ ራሴን እየዳበሰ እንዲህ አለኝ፡- “ይህን በሕይወትህ ማድረግ እኮ በጣም ቀላል ነው፡፡ ሁሉም ነገር የምትወስነው አንተ ነህ፡፡ ልብህ በእነዚህ ልጆች እንዳየኸው አድርገህ ሁሉም ሰው እኵል የምታፈቅር ከሆነ በጣም ቀላል ነው፡፡ እንዲህ የምታደርግ ከሆነ እዚህ ያየሃቸው ሁሉም በአንተ ሕይወት ይከናወናሉ፡፡ እንዲህ ስታደርግ ሁሉም ነገር በፍቅር ማየት ትጀምራለህ፡፡ ሊደርሱብህ የሚችሉ ችግሮች እንኳን በጣም ጠቃቅንና በቀላሉ የምትፈታቸው ይሆናሉ” አለኝ፡፡ እኔም ንግግሩን አቋረጥኩትና፡- “የሆነ የሰፈራችን ልጅ ዝም ብሎ የሚሰድበኝ ከሆነ ምንም ነገር ሳልመልስለት እንዴት እችላለሁ? እንዲህ ዓይነቱን ልጅስ እንዴት ልወደው እችላለሁ?” ብዬ ጠየቅኩት፡፡ ሰውዬውም እንዲህ ሲል መለሰልኝ፡- “አየህ! ፍቅር ከሁሉም ይበልጣል የተባለው ለዚህ ነው፡፡ አንተ በአዲሲቷ ቆሮንቶስ ከእነዚህ ልጆች ጋር መኖር ከፈለግክ ሁል ጊዜ ፍቅርን በተግባር በመግለጥ መለማመድ አለብህ፡፡ አንተ በምትኖርባት መንደር ሆነህ በልብህና በሐሳብህ እዚች ከተማ መኖር ትችላለህ፡፡ ፍቅር ከስጦታዎች ሁሉ እንደምትበልጥና የመልካም ምግባር ሁሉ እናት እንደሆነች ታውቃለህ?” ሲለኝ ከእንቅልፌ ብንን ብዬ ነቃሁ፡፡ ዓይኔን አሻሽቼ ዙርያዬን ስመለከት ሰው የለም፡፡ ባየሁት ሕልም ግን በጣም ተደሰትኩኝ፡፡ መጽሐፍ ቅዱሴንም ሳዬው 1ኛ ቆሮንቶስ ምዕራፍ 13 ላይ እንደተገለጠ ነበር፡፡ 

 ልጆች! ታሪኩን ወደዳችሁት አይደል? ጐበዞች! “እኛም እንደ አዲሰቱ ቆሮንቶስ ልጆች እንሆናለን” እንደምትሉ እርግጠኛ ነኝ፡፡ በሉ ሌላ ጊዜ ሌላ ታሪክ ይዤላችሁ እስክመጣ ድረስ ደኅና ሰንብቱ! እወዳችኋለሁ እሺ?!
(ምንጭ፡-The Coptic Orthodox Diocese of the Southern USA, Sunday school Curriculum, Grade 8)
   

FeedBurner FeedCount