Showing posts with label ወቅታዊ. Show all posts
Showing posts with label ወቅታዊ. Show all posts

Monday, September 9, 2019

የእነ ቀሲስ በላይ ጥያቄ ታሪካዊ ባለቤቱ ማን ነው?


በመምህር ብርሃኑ አድማስ
(ከመጽሓፈ ገጹ የተወሰደ)
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጳጉሜን 04 / 2011 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
አቤቱ እውነትና መንገድ ሕይወትም የሆንከው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ስለእውነትና ስለ ጽድቅ ስለሰላምና ስለአንድነት፤ ስለመግባባትና በስምህ አንድ ስለመሆን ብቻ እመሰክር ዘንድ አንተ በምታውቃቸው በጽኑ ወዳጆችህና ስምህን ተሸክመው ዐለምን በዞሩ በቅዱሳንህ ስም እማጸንሃለሁ፡፡ ልዩነት፣ ሥጋዊ ጥቅም፣ ዝናና የበላይነት ስሜት ወደ ማንኛችንም ልጆችህ እንዳይመጣ ትጠበቀንም ዘንድ ኃጢአተኛው ባሪያህ በእውነት አለምንሃለሁ፡፡ አቤቱ በዙሪያችን የከበበውን ጨለማ አርቅ፤ ብርሃንህንም ግለጽልን፤ ስለእውነትና በእውነት ብቻ እንድናገርም ርዳን፡፡ አቤቱ በጠላታችን በዲያብሎስ አንናቅ፤ ይልቁንም ስለ ስምህ አንድ መሆንንና እርሱን መርገጥን ስጠን፤ በቅዱሳን ሁሉ ጸሎትና ከሁሉም በላይ በምትሆን በባሕርያችን መመኪያ በእናትህ በቅድስት ድንግል ማርያም ጽኑ አማላጅነት፤ አሜን፡፡

የአንድ ፓስተር ኑዛዜ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት በሀገሪቱ የነበረው ሽኩቻና ውጥረት እንዲሁም የሕዝቡ ጭንቀት ያሳሰባቸው ኢትዮጵያውያን ብዙ ነበሩ፡፡ ብዙዎች መፍትሔ የመሰላቸውን ከማድረግ ወደ ኋላ እንዳላሉ የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ በወቅቱ ለመፍትሔ ይሯሯጡ ከነበሩት አካላት አንድ የሽማግሌዎች ቡድን ለመመሥረትና ባለሥልጣናትን በማናገር ወደ መግባባትና ሰላም ለማምጣት ሕብረ ብሔርና ሕብረ ሃይማትን ታሳቢ ያደረገ የሀገር ሽማግሌዎች ቡድን ማሰባሰብ ይጀመራል፡፡ በዚህ ሒደት ውስጥ ከኮሚቴዎቹ ሁለቱ እገዛ እንዳደርግ ሲያወያዩኝ የነገሩኝ ሽማግሌዎችን ሲያናግሩ ከገጠማቸውና ካስገረማቸው ታሪክ አንዱ የሚከተለው ነበር፡፡

Wednesday, September 4, 2019

ከገጠመን ችግር ለመውጣት በፍጥነት ልናደርገው የሚገባን ምንድን ነው?

በመምህር ብርሃኑ አድማስ
(ከመጽሐፈ ገጹ የተወሰደ)
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ 29 ቀን 2011 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡

ባለፉት ስምንት ዐመታት (ከቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ እና ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዕረፍት) ወዲህ ኢትዮጵያ ባልተቋረጠ የለውጥ፣ የውዝግብና የነውጥ ሂደት ውስጥ ትገኛለች፡፡ ሁለቱም ታላላቅ መሪዎች ያረፉት በዘመነ ዮሐንስ ማጠቃለያ ወር ላይ ነበር፡፡ የእነርሱን ዕረፍት ተከትሎ እንዳሁኑ ጎልቶ ባይነገርላቸውም ብዙ ለውጦችም ነውጦችም በተከታዮች ዐመታት ውስጥ ነበሩ፡፡ ከዐራት ዐመታት በኋላ ልክ በዘመነ ዮሐንስ ደግሞ አሁን ላለንበት ለውጥም እንበለው ምስቅልቅል የዳረገን አብዮት ተቀሰቀሰ፡፡ አሁን ባለቤቱ እኔ ነኝ እኔ ነኝ የሚባልለት ሕዝባዊ ጫናን መሣሪያ ያደረገ (ከየት እንደሆነ ግን ከግምት በቀር ብዙዎቻችን በትክክል የማናውቀው) ለውጥ ተፈጠረ፡፡ አራቱን ዐመታትም የማንጠበቃቸውና ሊተነበዩ የማይችሉ ተከታታይ ለውጦች ከጥፋቶችና ምስቅልቅሎች ጋር በሀገራችን ተከሰቱ፡፡ ሁኔታዎቹም ለከፊሉ ደስታ ለከፊሉም ሐዘን የሆኑበት ብዙም ሳይቆይ ደግሞ ደስታና ሐዘን በፍጥነት የተፈራረቁበት ሆነ፡፡ እንዲህ ያሉ ክስተቶች ሳያቋርጡ ያለፉበት የዐራት ዐመታት አንድ የለውጥ ወቅት ሊፈጸም ሳምንታት ብቻ ቀርተውታል፡፡

Saturday, April 2, 2016

ዕለተ ምጽአት



ምንጭ፡- ቅዳሴ አትናቴዎስ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መጋቢት 24 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ይህቺ ዕለት (ቅድስት ሰንበተ ክርስቲያን) በምትሠለጥንበት ጊዜ አዲስ ሥራ አዲስ ነገርም ይኾናል፡፡ ያን ጊዜ የፀሐይና የጨረቃ የከዋክብትም ብርሃን ወይም ፀዳል ወይም በጋ የለም፡፡
በውስጥዋ በነፍስ ሕያው ኾኖ የሚንቀሳቀስ ፍጥረት ሳይኖርባት ምድር ሰባት ቀን ታርፋለች፡፡ እንደ ረቂቅ ፉጨት ያለ ቃል ይላካል፡፡ በዚያችም ቃል የሰማያት ጽንዕ ይወገዳል፤ የምድር ግዘፍ ይነዋወጻል፡፡
ያን ጊዜ መቃብራት ይከፈታሉ፡፡ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የፈረሱ ሙታን ፈጥነው እንደ ዓይን ቅጽበት ይነሣሉ፡፡ አብ መንግሥቱንና ፍርዱን ለልጁ ይሰጣል፡፡ ግሩም የኾነ የነጐድጓድም ቃል ይሰማል፡፡ ከመጀመሪያው (ከጥንት) ጀምሮ ጆሮ ያልሰማው ዓይንም ያላየው!
የእሳት ክንፎች ያሏቸው ግሩማን መላእክት በፊቱ ይቆማሉ፡፡ ስም የሌላቸው፣ እገሌና እገሌ የማይሏቸው በአብ መጋረጃ ውስጥ የሚኖሩ ባለሟሎች መላእክት ናቸው፡፡ የሊህም ክንፍ ከክንፍ ጋር ይሳበቃል፤ ይሰማሉ፤ ያንጐደጕዳሉ፤ ሰይፋቸውንም ይመዛሉ፤ ጽናታቸውንም ያሳዩ ዘንድ ይበራሉ፡፡

Sunday, October 4, 2015

የዘመናችን አጥማቂ ነን ባዮች፡- የሐሳዊው መሲሕ መንገድ ጠራጊዎች

በዲ/ን ዳንኤል ክብረት
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 23 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ክፍል ሁለት
1.   ተአምራት ማድረግ የምን ውጤት ነው? ተአምራት ማድረግ ከሁለት ነገሮች ሊመጣ ይችላል፡፡ ከመንፈሳዊ ብቃትና ከሰይጣን አሠራር፡፡ በክርስትና ሕይወቱ የበረታ ሰው መንፈሳዊ ብቃቱ በሕይወቱ በሚገለጡ ተአምራት ሊታወቅ ይችላል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የምናገኛቸው ቅዱሳን በገድል ተቀጥቅጠው፣ ሰማዕትነት ከፍለው፣ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው በሚገባ ተጉዘው ዲያብሎስን ድል ሲነሡት በሕይወታቸው ውስጥ ተአምራት ይገለጣሉ፡፡ ይህም ማለት ተአምራት የመንፈሳዊ ብቃት መገለጫ ነው ማለት ነው፡፡ የተአምራት ስጦታ እንዲሁ በድንገት አይገለጥም፡፡ በዚያ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ እያደገ፣ እየተገለጠና እየተመሰከረለት በሚመጣ መንፈሳዊ ዕድገት ምክንያት እንጂ፡፡ ለዚህ ሁለት ምሳሌዎች እናንሣ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስና አቡነ ተክለ ሃይማኖት፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ በሐዋርያት ሥራ ውስጥ አራት ምዕራፍ ያለው መንፈሳዊ ዕድገቱ በየዘመናቱ ተገልጦልናል፡፡ በፍኖተ ደማስቆ መመለሱ(የሐዋ8) በአንጾኪያ በሱባኤ መኖሩ(የሐዋ13) ለአገልግሎት ተጠርቶ ከበርናባስ ጋር መውጣቱ እና ከአረማውያን፣ ከአይሁድና ከመናፍቃን ጋር ባደረገው ተጋድሎ የምናገኘው በትምህርትና በተአምራት የተገለጠ ሕይወቱ ናቸው፡፡ የቅዱስ ጳውሎስ ሕይወት ቀስ በቀስ እያደገ (ወየሐውር እም ኃይል ውስተ ኃይል እንዲል) የመጣ ነው፡፡

FeedBurner FeedCount