Showing posts with label ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ በ‹‹ያ! ትውልድ›› መካከል … ‹‹ሞትህ ደጅ አደረ››! ክፍል ሁለት…!. Show all posts
Showing posts with label ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ በ‹‹ያ! ትውልድ›› መካከል … ‹‹ሞትህ ደጅ አደረ››! ክፍል ሁለት…!. Show all posts

Saturday, July 23, 2016

ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ በ‹‹ያ! ትውልድ›› መካከል … ‹‹ሞትህ ደጅ አደረ››! ክፍል ሁለት…!

በአማን ነጸረ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 16 ቀን 2008 ዓ.ም.):- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

3. ሰቆቃወ ቴዎፍሎስ… ቅድመ-ሞት፣ ጊዜ-ሞት፣ ድኅረ-ሞት...ሞትህ ደጅ አደረ!
ከሞመቱ በፊት ስብዕናውን ለመግደል ተሞከረ፡፡ ሲሞት የፓትርርክነት ወግና ሥርዓቱ ቀርቶ ሞቱን ለሙት በሚገባ ክብር ሳያደርጉለት ቀሩ፡፡ ድኅረ-ሞት ታሪኩን ለማስተሀቀር ተሽቀዳደሙ፡፡ ሞቱን፣ እረፍቱን ከለከሉት፤ ሞቱን ደጅ አሳደሩበት፡፡ ሰቆቃውን አበዙበት፡፡ ስለሰቆቃው መዛግብት ካኖሩልን ልናወጋ ጀምረናል፡፡
3.1. ቅድመ-ሞት…የተሐድሶ ጉባኤ (የኮ/ል አጥናፉ የቤተ ክርስቲያን ኮሚቴ)!
3.1.1. የ1966 ዓ.ም አብዮት እየጋመ፣ እየፋመ፣ እየተቀጣጠለ የንጉሡን ዙፋን በይፋ ለመገልበጥ 25 ቀናት ሲቀሩት ነሐሴ 11 ቀን 1966 ዓ.ም ተጠሪነቱ ለኮ/ል አጥናፉ የሆነ ‹‹ጠቅላይ ቤተ ክሕነት እስከ አሁን በምትሠራበት ደንብና ሥርዓት ሥራዋን ስትቀጥል…ከጎን ሆኖ የሚሠራ›› በሚል ሽፋን ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጥኝ ጊዜያዊ ጉባኤ›› ተቋቋመ(ድምጸ ተዋሕዶ ጋዜጣ፣ ሐምሌና ነሐሴ 1983 ዓ.ም፡ገ.7)፡፡ ይሕ ጉባኤ በቤተ ክህነት አካባቢ ‹‹የተሐድሶ ጉባኤ›› በሚል ሲታወቅ የጉባኤው አባል የነበሩት ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ ደግሞ ‹‹የኮ/ል አጥናፉ የቤተ ክርስቲያን ኮሚቴ›› ይሉታል፡፡ በወቅቱ ሸዋ ክፍለ ሀገርን ወክለው የደርግ ሸንጎ(መማክርት ጉባኤ) አባል የነበሩት ፕ/ር ጌታቸው እንዴት የኮ/ል አጥናፉ ኮሚቴ አባል እንደሆኑና የኮሚቴውን አባላት ዝርዝር ሲገልጹ ‹‹…ኮ/ል አጥናፉ አባተ ጠርቶኝ ‹ቤተ ክርስቲያን ከመንግሥት የገንዘብ ድጋፍ ወጥታ ራሷን የምትችለበትን መንገድ የሚፈልግ ኮሚቴ ልናቋቋም ነውና በአባልነት እንዲያገለግሉ እፈልጋለሁ› አለኝ፡፡ ንቡረ ዕድ ድሜጥሮስ ገብረማርያም፣ አለቃ አያሌው ታምሩ፣ ቄስ ዳኛቸው ካሳሁን፣ ዶክተር ክንፈርግብ ዘለቀ፣ አቶ ፍቅረድንግል በየነ፣ አቶ መርስዔኀዘን አበበ፣ አቶ አእምሮ ወንድማገኘሁ፣ አቶ(በኋላ ሊቀ ማዕምራን) አበባው ይግዛው የኮሚቴው አባላት እንደነበሩ አስታውሳለሁ፡፡ ኮሚቴው ሊቀ መንበር ሲመርጥ…ዶ/ር ክነፈርግብ ዘለቀ ተመረጠ›› ይላሉ(ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ፣ አንዳፍታ ላውጋችሁ፡ገ.202)፡፡ የኮሚቴው አባላት 9 ሰዎች ነበሩ ማለት ነው፡፡

FeedBurner FeedCount