Showing posts with label የቁልቢ ገብርኤል አመሠራረት. Show all posts
Showing posts with label የቁልቢ ገብርኤል አመሠራረት. Show all posts

Tuesday, July 24, 2012

የቁልቢ ገብርኤል አመሠራረት- በዲ/ን ዳንኤል ክብረትና ቀሲስ ከፍያለው መራሒ!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

 ከአዲስ አበባ በስተምሥራቅ 461 ኪ/ሜ. ርቀት ላይ በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጋራ ሙለታ የሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ የዚህን ደብር አመሠራረት በተመለከተ በብዙ ሊቃውንት የሚተረከው የሚከተለው ነው፡፡

በዘጠነኛው መ/ክ/ዘ. ዮዲት ጉዲት ተነሥታ አብያተ ክርስቲያናትን ስትመዘብር፣ ክርስቲያኖችን ስትገድልና መጻሕፍትን ስትቆነጻጽል ንጉሥ አንበሣ ውድም በአኩስምና በአከባቢዋ የነበሩ ታቦታትንና ንዋያተ ቅዱሳትን በመያዝ ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ ወደ ዝዋይ መጣ፡፡

ከ40 ዓመታት ስደት በኋላ አንበሣ ውድም ወደ አኵሱም ሲመለስና የንዋያተ ቅዱሳት ቆጠራ ሲደረግ ታቦተ ቅዱስ ገብርኤል በዝዋይ መቅረቱ ታወቀ፡፡ ከኤርትራ ደብረ ሲና ማርያም የመጡና አባ ሌዊ የተባሉ አባት ታቦቱን ለማምጣት ከንጉሡ አስፈቅደው ወደ ዝዋይ መጡ፡፡

አባ ሌዊ ከሰባት ቀን ሱባኤ በኋላ ታቦተ ቅዱስ ገብርኤልን ይዘው ወደ አኵሱም ሲጓዙ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጦ “እኔ ወደማሳይህ ቦታ ታቦቱን ይዘህ ሂድ” አላቸው፡፡ አባ ሌዊም ታቦቱን ይዘው ተከተሉት፡፡ በመጨረሻም ቁልቢ ደረሱ፡፡ ለአባ ሌዊም የተፈቀደላቸው ቦታ ይሄ መሆኑን ታቦቱም በኋላ ዘመን ለሕዝቡ ድንቅ ሥራ እንደሚሠራ ቅዱስ ገብርኤል ነግሯቸው ተሠወረ፡፡ አባ ሌዊ በቦታው ለ130 ዓመታት ያህል አገልግለው በንጉሥ ግርማ ሥዩም ዘመነ መንግሥተ ታኅሳስ 14 ቀን ዐርፈዋል፡፡

ግራኝ አሕመድ ኢትዮጵያን ሲወርር ብዙ ካህናት ከሰሜን ኢትዮጵያ ታቦታትንና ንዋያተ ቅዱሳትን ይዘው ሲጓዙ ቁልቢ ደረሱ፡፡ መልአከ ገነት መብረቁ፣ መምህር የማነ አብ፣ አባ ተከስተ ሥሉስ የተባሉ ካህናት ከተነጠፈ ድንጋይ ላይ የተጻፈ ነገር ያገኛሉ፡፡ ጽሑፉም ታቦተ ቅዱስ ገብርኤል በሥዉር መቀመጡን፣ ልዩ ልዩ ተአምራት እንደሚፈጸምበት፣ ወደ ፊትም ታላቅ ቤተ መቅደስ እንደሚሠራበት፣ እንዴት አባ ሌዊ ታቦቱን ወደዚህ ቦታ እንዳመጡት የሚገልጽ ነበር፡፡ እነርሱም ይህን ታሪክ ይዘውት በነበረው መጽሐፈ ቀሌሜንጦስ ሕዳግ ላይ ጻፉት፡፡ ወደ ዝዋይ ደሴት ሲደርሱም መጽሐፉን በዚያ አኖሩት፡፡

ልዑል ራስ መኰነን ከዝዋይ ደሴት መጽሐፈ ቀሌሜንጦስን አስመጥተው ሲያነቡ የቁልቢ ገብርኤልን ታሪክ በማግኘታቸው የቅዱስ ገብርኤልን ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ተነሡ፡፡ ልዑል ራስ መኰንን በአከባቢው የአየር ንብረት ተማርከው በሥፍራው ቤት ሠርተው ነበር፡፡ ልዑል ራስ መኰንን ቁልቢ ገብርኤልን ከመትከላቸው በፊት ቦታው የአከባቢው ጎሳዎች የግጭት መነሃርያ ነበር፡፡ ሰላምን በአከባቢው ከመሠረትህ በቦታው በስምህ ቤተ ክርስቲያን እሠራልሃልሁ ብለው እንደተሳሉም ይነገራል፡፡

የተሳሉት በመፈጸሙ የቅዱስ ገብርኤል ታቦት የት እንዳለ ሲያፈላልጉ ቡልጋ ውስጥ ከአዠጉጉ ካህናተ ሰማይ ጋር አባ ዱባለ የተባሉ ካህን ያስቀመጡት ታቦተ ቅዱስ ገብርኤል መኖሩ ተነገራቸው፡፡ ልዑል ራስ መኰንን ለአባ ዱባለ መልእክት ስለላኩባቸው ከሐረር በተላኩ ካህናት አማካኝነት የቅዱስ ገብርኤልን ታቦት ላኩ፡፡ ልዑል ራስ መኰንንም ከነሠራዊቶቻቸው ሸንኮራ ድረስ ሄደው ታቦቱን በመቀበል የካቲት 21 ቀን 1884 ዓ.ም ታቦቱ ቁልቢ ገባ፡፡

የመቃኞው ሥራ በ1883 ዓ.ም ተጀምሮ ፍጻሜ አግኝቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረው ሐምሌ 19 ቀን 1884 ዓ.ም ነው፡፡ በዚሁ ዕለት የዋናው ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ሥራ የመሠረቱ ድንጋይ ተጥሎ ታኅሳስ 19 ቀን 1888 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ተፈጽሞ በአቡነ ማትያስ ተባረከ፡፡ ቦታውን ከባለ አባቶች የገዙት በአርባ የቁም ከብት ነው፡፡ ራስ መኰንን መጋቢት ዘጠኝ ቀን 1889 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ሲሄዱ እዚህ ቦታ ላይ በድንገት ስለታመሙ በዕለቱ ሥጋወደሙ ተቀብለውበታል፡፡ በመጀመርያ ሲተከል በገጠር ቤተ ክርስቲያን ሥሪት ሲሆን በኋላ ግን በስእለት ሰማኢነቱ በመላ ኢትዮጵያ እየታወቀ ስለ መጣ ደብር ሆኗል፡፡

የቅዱስ ገብርኤል ምልጃና በረከት አይለየን!!

(ምንጭ፡ የቤተ ክርሰቲያን መረጃዎች- በዲ/ን ዳንኤል ክብረት፤ Saints and Monastries in Ethiopia, by Kesis Kefyalew Merahi)    

FeedBurner FeedCount