Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ7ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts
Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ7ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts

Saturday, May 19, 2012

የእግዚአብሔር በግ (የዮሐንስ ወንጌል የ7ኛው ሳምንት ጥናት)!!

“በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ። እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ።” ዮሐ.1፡29
 የሚገርም ምስክርነት ነው፡፡ ጌታስ “በሰው ፊት የሚያምንብኝን ሁሉ እኔም በእግዚአብሔር መላእክት ፊት አምነዋለሁ” አይደል ያለው /ሉቃ.12፡8/፡፡ መጥምቁ ምስክርነቱን ለአይሁድ ሁሉ ላንቃው እስኪሰነጠቅ ድረስ “ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘያአትት ወያሴስል ኃጢአተ ዓለም- የሰውን ኃጢአት የሚያስተሰርይ የእግዚአብሔር መሥዋዕቱ እነሆ!” ይላቸው ነበር /John Chrysostom, Homily on the Gospel of John, 17/፡፡ አዎ! ዮሐንስ ከእንግዲህ ወዲህ ዝግጅቱን ጨርሷል፡፡ ያ ለስድስት ወራት ሲያዘጋጀው የነበረና ለዓለም ሁሉ የሚሠዋው ንጹሑ በግ መጥቷልና /2ቆሮ.5፡14፣ ቅ.ቄርሎስ ዘአሌክሳንድርያ Commentary on the Gospel of John 2:1/፡፡ ይህ ንጹሕ በግ እንደ ብሉይ ኪዳኑ ዓይነት በግ አይደለም፤ ይህ በግ ነብዩ “እኔም ለመታረድ እንደሚነዳ እንደ የዋህ በግ ጠቦት ሆንሁ” ያለው ነው /ኤር.11፡29፣ አርጌንስ Commentary on the Gospel of John 6/፡፡ ይህ በግ ኢሳይያስ “በሸላቾቹ ፊት ዝም አለ” ያለለት በግ ነው /ኢሳ.53፡7፣ አውሳብዮስ ዘቂሳርያ Proof of the Gospels 1:10/፡፡ ይህ በግ በዕጸ ሳቤቅ (በእመቤታችን) ተይዞ የተገኘውና በይስሐቅ ፈንታ የተሠዋው በግ ነው /ዘፍ.22፡13፣ አውግስጢኖስ Sermon 19:3/፡፡ ይህ በግ በምድረ ግብጽ ሞተ በኩር በመጣ ጊዜ በእስራኤላውያን በኩራት ፈንታ የተሠዋው በግ ነው /ዘጸ.12፡21-30/፤ ይህ በግ አቤል ለእግዚአብሔር ያቀረበው ንጹሑ በግ ነው /ዘፍ.4፡4፣ አምብሮስ/፡፡
 መጥምቁ በዚያ ለነበሩ አይሁድ ይህን ሁሉ የሚመሰክርላቸው በመጻሕፍቶቻቸው የተነገረውን ትንቢት ሁሉ መፈጸሙን አውቀው በክርስቶስ እንዲያምኑ ነው /ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡
 የሚደንቅ ነው! ይስሐቅ ከርብቃ ጋር /ዘፍ.24/፣ ያዕቆብ ከራሄል ጋር /ዘፍ.29/፣ ሙሴም ከሲፓራ ጋር ለመጋባት በውኃ ጉድጓድ እንደተገናኙ ሁሉ /ዘጸ.2፡15-21/ ክርስቶስም ከሙሽራው ከቤተ ክርስቲያን ጋር በዮርዳኖስ ወንዝ ተጋብቷል /ኤፌ.5፡32፣ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ Commentary on Tatians Diatessaron 3:17/፡፡
 መጥምቁ ምስክርነቱን ይቀጥልና “አንድ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል፥ ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል ብዬ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነው።” ይላቸዋል /ቁ.30/፡፡ እንዲህ ማለቱ ነበር፡- “የዓለምን ኃጢአት ያስወግዳል ያልኳችሁ በግ፣ በመንፈስ ቅዱስ በእሳትም ያጠምቃችኋል ያልኳችሁ ሰው እርሱ ነው፡፡ እርሱ አወጣጡ ከዘላለም የሆነ አምላክ ነው፤ እኔ ግን አይደለሁም፡፡” አሁንም ይቀጥልና “እኔም አላውቀውም ነበር” ይላል/ቁ.31/፡፡ “ታድያ ካለወቅከው እንዴት ትመሰክራለህ? ካላችሁኝም ‘አላውቀውም ነበር’ አልኳችሁ እንጂ ‘አላውቀውም’ አላልኩም ብዬ እመልስላችኋለሁ፡፡ ‘አወጣጡ ከዘላለም ከሆነ ታድያ አሁን ካንተ ዘንድ ለመጠመቅ ምን አተጋው?’ ካላችሁኝም እንዲህ እላችኋለሁ ‘ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ’ ብዬ እመሰክራችኋለሁ፡፡ እርሱስ እንደ እኔና እንደናንተ ጥምቀት የሚያስፈልገው አይደለም፡፡ ‘ቅድም አላውቀውም ነበር ብለኸን ነበር፡፡ አሁን እንዴት አወቅከው?’ ካላችሁኝ ‘መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ፤ በእርሱ ላይም ኖረ። እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን በውኃ አጠምቅ ዘንድ የላከኝ እርሱ፡- መንፈስ ሲወርድበትና ሲኖርበት የምታየው፥ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው አለኝ’ እላችኋለሁ” /ቁ.32-33/፡፡  መጥምቁ እየደጋገመ “አላውቀውም ነበር” የሚለን ስለ ክርስቶስ የሚሰብከው ሁሉ “ተዛምዶተ ሥጋ ኑሮት ነው፤ ማማለጃ ተቀብሎ ነው፤ አብሮ አደግ ሁኖ ነው” ብሎ ማንም እንዳያስብ ነው፡፡ በበረሀ የማደጉ አንዱ ምሥጢርም ይኸው ነበር /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡
 የመንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል መውረድ ሌላ የሚያስገነዝበን ምሥጢር አለው፡፡ ይኸውም እንዲህ ነው፡- መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ሰው በእግዚአብሔር መልክ እና ምሳሌ  ተፈጥሯል፡፡ እግዚአብሔር ሰውን ከአፈር ካበጃጀው በኋላ እፍ ሲልበት መልኩን ሥሎበታል፡፡ ሲበድል ግን ይህ መልኩ ተበላሽቷል፤ የጸጋ ልብሱ ቆሽሾአል፡፡ የተሰጠው መንፈስ ቅዱስ እየራቀው ሄደ፡፡ ፈጣሪውንም እየረሳ ሄደ፡፡ መፍቀሬ ሰብእ እግዚአብሔር ግን የተበተነውን መንጋ መሰብሰብ ወደደ፡፡ የሰው ልጅ በመጀመርያው አዳም ያጣውን ጽድቅም በሁለተኛው አዳም መታዘዝ የእግዚአብሔር ቤተ ሰብእ አደረገው /2ቆሮ.5፡21/፡፡ መንፈስን የሚያድል ክርስቶስም ከእኛ ርቆ የነበረውን ቅዱስ መንፈስ በእኛ ተገብቶ ተቀበለው፡፡ በኃጢአታችን ምክንያት የራቀው መንፈስ ቅዱስ በክርስቶስ ንጽሕና ወደ እኛ ተመለሰ /ቅ.ቄርሎስ ዘአሌክሳንድርያ፣ ዝኒ ከማሁ/፡፡ በኖኅ ጊዜ እንደተደረገውም ያ መንፈስ ቅዱስ ለቤተ ክርስቲያን ሰላም ሲያውጅ ተመልክተናል /ቅ.ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም፣ Catechetical Lecture 17:9/፡፡
 ከእናንተ መካከል “አይሁድ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ሲወርድ እየተመለከቱ እንዴት በክርስቶስ አላመኑም?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ እኔም እንዲህ ብዬ እመልስለታለሁ፡- “ነገረ እግዚአብሔር በዓይነ ሥጋ ብቻ በማየት አይገባም፤ ይልቁንም በዓይነ ልቡና አይቶ ማስተዋልን ይጠይቃል እንጂ” /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡
መጥምቁ ንግግሩን እንዲህ ብሎ ይጨርሳል፡- “እኔም አይቻለሁ-  ከመ ዝንቱ ውእቱ ወልዱ ለእግዚአብሔር- እርሱ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ” /ቁ.34/፡፡
እውነት ነው!! ሁላችንም ክርስቶስ እርሱ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ እንደሆነ፤ በአንድነት በሦስትነት የሚመሰገን አምላክ እንደሆነ፤ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዳለው፤ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቁጣ በእርሱ ላይ እንደሆነች ልንመሰክር ያስፈልጋል፡፡ ይህን ሁሉ በአፍም በመጣፍም እንዲሁም በምግባር እንገልጠው ዘንድ ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን አሜን!!!

FeedBurner FeedCount