Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ9ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts
Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ9ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts

Sunday, May 20, 2012

የዮሐንስ ወንጌል የ9ኛው ሳምንት ጥናት (ዮሐ.1፡44-ፍጻሜ)!!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምለካ አሜን!!
“በነገው ኢየሱስ ወደ ገሊላ ሊወጣ ወደደ፥ ፊልጶስንም አገኘና ተከተለኝ አለው” /ቁ.44/፡፡
 ጌታ በወርቃማው ስብከቱ እንዲህ ብሎ ነበር፡- “የሚፈልግ እርሱ ያገኛል” /ማቴ.7፡8/፡፡ እውነት ነው! ፊልጶስ የተዘጋጀና እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ ስለ ነበረው እነ እንድርያስ ከመጥምቁ እንደተማሩት ከማንም ሳይማር ጌታ “ተከተለኝ” ስላለው ብቻ ተከትሎታል፡፡ ቀጥለን እንደምንመለከተውም ሲያነበው የነበረው ትንቢት ሲፈጸምለት ስላየ በጣምኑ ተደስቷል፡፡ በእርግጥም ጌታ ይህንኑ ልቡን አይቶ ተከተለኝ ብሎታል /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ Homily on John 20፡1/፡፡
ይህ ፊልጶስ አስቀድመው ዮሐንስ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ” ሲል ሰምተው ከተከተሉተ ከእንድርያስና ከጴጥሮስ ከተማ ከቤተ ሳይዳ (የዓሣ ከተማ) ነበረ /ቁ.45/። ፊሊጶስ እንደ ናትናኤል ባይሆንም ከነብያትና ከሙሴ መጻሕፍት በትንሽ በትንሹ ያነብ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ናትናኤልን አግኝቶ “ሙሴ በኦሪት የጻፈለትን ነቢያትም ስለ እርሱ ትንቢት የተናገሩለትን የዮሴፍን ልጅ የናዝሬቱን ኢየሱስን አግኝተነዋል” የሚለው፡፡ እዚህ ጋር ናትናኤልም የሕግና የነብያትን መጻሕፍት ያውቅ እንደነበር እንመለከታለን፡፡ ናትናኤል ግን መልሶ “ከናዝሬት መልካም ነገር ሊወጣ ይችላልን?” ብሎታል /ቁ.47/፡፡ ለምን እንዲህ አለው? ስንልም ገሊላ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚኖር ማኅበረሰብ የሚኖርባት፣ ለሃይማኖታዊ ጉዳይ ብዙም ግድ የሌላቸው ሰዎች የሚኖሩባት አከባቢ እንደሆነች እንመለከታለን፡፡ ስለዚህም በሌሎቹ የአይሁድ ሕዝብ ዘንድ የተናቁ ነበሩ፡፡ አይሁድ ለኒቆዲሞስ “ነብይ ከገሊላ እንዳይነሣ መርምርና እይ” ማለታቸውም ይህንኑ ሐሳብ ያጠናክራል /ዮሐ.7፡52/፡፡ ፊልጶስ ናትናኤል ከሚለው ሐሳብ ተቃራኒ የሆነ ነገር ተደርጐ ስላየና ተከራክሮ ማስረዳት ባይቻለው “የእኔ ንግግር ካላሳመነህ ጌታ ራሱ ያሳምንህ ዘንድ መጥተህ እይና ተረዳ” አለው /ቴዎዶር ዘሜውፕሳስትያ Commentary on John 1:1:46/።
 ናትናኤልም አሁን የፊሊጶስን ንግግር ለማረጋገጥ መጣ፡፡ “ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ናትናኤልን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ ስለ እርሱ፡- ክዳት ተንኰል የሌለበት በእውነት እስራኤላዊ እነሆ አለ” /ቁ.48/፡፡ የሚገርም ነው! ናትናኤል “ከገሊላ መልካም ነገር ይወጣልን?” በማለቱ እንደሰው አስተሳሰብ መወቀስ ሲገባው ተመሰገነ፤ በውዳሴ ከንቱ ሳይሆን በአውነት በጌታ አንደበት ተወደሰ፡፡ እንዴትስ አልተወቀሰም ስንልም የናትናኤል ንግግር ከተንኰል የመነጨ ሳይሆን የፊሊጶስ ንግግር ከነብያቱ ትንቢት ጋር የተጋጨ መስሎት እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ ምክንያቱም ናትናኤል ከመጻሕፍት ሲያነብ ያገኘውና የተረዳው ክርስቶስ ከዳዊት ከተማ ከቤተልሔም እንጂ ከናዝሬት እንደማይመጣ ነውና /ሚክ.5፡2/፡፡ ስለዚህ ናትናኤል እንደዚያ ማለቱና ክርስቶስም “ተንኰል የሌለበት ማለቱ” ትክክል ነበር፡፡ መጻሕፍትን አንዳንዶች እንደሚያደርጉት በራሱ ፈቃድ ለመተርጐም አለመሞከሩ ደግሞ የበለጠ ቅንነቱን ያሳያል /ቅ.ኤፍሬም ሶርያዊ Commentary on Tatian’s Diatessaron 4:14/፡፡
 የናትናኤል ቅንነት የበለጠ ግልጽ የሚሆነው ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ጌታ “ተንኰል የሌለበት” ሲለው “ከወዴት ታውቀኛለህ?” ማለቱም ጭምር እንጂ። “ኢየሱስም መልሶ ፊልጶስ ሳይጠራህ፥ ከበለስ በታች ሳለህ፥ አየሁህ አለው” በማለት የበለጠ ያምን ዘንድ የነበረበትን ቦታ ብቻ ሳይሆን ጊዜውም ጭምር ነገረው /ቁ.49፣ ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡ በምሥጢራዊ አነጋገር ግን “አባትህ አዳምና እናትህ ሔዋን በወደቁበት ዕጸ በለስ ስር ወድቀህ በኃጢአት ተጐሳቁለህ ሳለህ በመለኰታዊ ባሕርዬ አውቃሃለሁ፤ አይቻሃለሁ” ማለቱ ነበር /ቅ.አምብሮስ/፡፡ በእርግጥም ክርስቶስ ከዚሁ የበለስ ግልድም አላቅቆ ጸጋውን ያለብሰን ዘንድ እኛን የጠፋነውን ለመፈለግ መጥቷል /አውግስጢኖስ/፡፡
 ከዚህ በኋላ ክርስቶስ የልቡን ስለነገረው ምንም ሳይጠራጠር እምነት ጨመረና “መምህር ሆይ፥ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤ አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ” አለ፡፡ በዚህ ሰዓት ፊልጶስ እንደነገረው ከማመን፣ ከመረዳት፣ ከመደነቅ፤ በሐሴት ከሞመላትና ለክርስቶስ እጅ ከመስጠት ውጪ ምንም አማራጭ አልነበረውም /ቁ.50/፡፡ “ኢየሱስም መልሶ ከበለስ በታች አየሁህ ስላልሁህ አመንህን? በል በዚህ ብቻ አትደነቅ! ገና ከዚህ የሚበልጥ ነገር ታያለህ /ቁ.51/። እኔ ዕሩቅ ብእሲ (ሰው ብቻ) ስላይደለሁ ገና ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት እኔን ለማገልገል ሲወጡና ሲወርዱ ታያለህ” በማለት አባቱ ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ ያየውን ራዕይ መፈጸሙን ይነግረው ነበር /ቁ.52/፡፡ በእርግጥም ክርስቶስ እንደተናገረው ናትናኤል መላእክት ክርስቶስ ፈታኙን ድል ሲያደርግ /ማቴ.4፡11/፤ ሲሰቀል፣ ከሙታን ተለይቶ ሲነሣ፣ ሲያርግ መላእክት ሲያገለግሉት አይቷል፡፡ ናትናኤል ባያይም ይህ ክስተት በቤተልሔም ግርግምም “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ስምረቱ ለሰበእ ሃሌ ሉያ” ሲሉ ተመልክተናል፡፡
አስተውላችሁ ከሆነ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ከነገረው በኋላ ናትናኤል አንዲትም ቃል መልሶ አልተነፈሰም /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒከማሁ/፡፡
አምላካችን እግዚአብሔር ላላመኑት እንደ ናትናኤል “ረቢ አማን አንተ ውእቱ ወልደ እግዚአብሔር- መምህር ሆይ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ” የሚል ቀና ልብ ይስጥልን፤ እኛንም በተዋሕዶ ያጽናን አሜን!!!!!!

FeedBurner FeedCount