Tuesday, August 13, 2013

የረቡዕ ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ

ገ/እግዚአብሔር ኪደ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ ነሐሴ ፰ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም.)፡-  ለምስጋና ሦስተኛ፣ ለፍጥረት አራተኛ ቀን በሚኾን በዚህ ዕለት ከወትሮ ይልቅ መላእክትን አስከትላ እመቤታችን ትመጣለች፤ የብርሃን ድባብ ይዘረጋል፤ የብርሃን ምንጻፍ ይነጸፋል፡፡ ከዚያ ላይ ኾናም፡- “ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ኤፍሬም” ትለዋለች፡፡ እሱም ታጥቆ እጅ ነሥቶ ይቆማል፡፡ ከባረከችው በኋላም ምስጋናዋን “ኵሉ ሠራዊተ ሰማያት ይብሉ ብፅዕት አንቲ…” ብሎ ይጀምራል፡፡

፩. ኵሉ ሠራዊተ ሰማያት ይብሉ ብፅዕት አንቲ ሰማይ ዳግሚት ዲበ ምድር - ከምድር በላይ ያለሽ ኹለተኛ ሰማይ ሆይ! በሦስቱ ሰማያት (በኢዮር፣ በራማ፣ በኤረር) ያሉ መላእክት ንዕድ ነሽ፤ ክብርት ነሽ ይላሉ፡፡ ማርያም የምሥራቅ ደጅ ናት፤ ከእርሷ የጽድቅ ፀሐይ ክርስቶስ ተኝቷልና፡፡ ማርያም ሙሽራዋ ንጹሕ የሚኾን ንጽሕት የሠርግ ቤት ናት፡፡ በሠርግ ቤት የመርዓዊና የመርዓት (የሙሽራና የሙሽሪት) ተዋሕዶ ይደረግበታል፡፡ በእመቤታችንም እንደ መርዓዊና እንደ መርዓት ተዋሕዶ፤ ትስብእትና መለኮት አንድ ኹነዋልና፡፡ በሠርግ አዝማደ መርዓዊና አዝማደ መርዓት አንድ እንዲኾኑባት በእመቤታችንም ምክንያት ሰውና መላእክት፣ ሰውና እግዚአብሔር፣ ነፍስና ሥጋ፣ ሕዝብና አሕዛብ አንድ ኹነዋልና እመቤታችን ንጽሕት የሠርግ ቤት ናት /ኤፌ.፪፡፲፭/፡፡ አባ ሕርያቆስ “አስተንፈሰ ወአጼነወ ወኢረከበ ዘከማኪ፤ ወሠምረ መዓዛ ዚኣኪ ወአፍቀረ ሥነኪ ወፈነወ ኀቤኪ ወልዶ ዘያፈቅር” እንዲል /ቅዳ.ማር.ቁ.፳፬/ አብ ከሰማይ ኾኖ አየ፤ ነገር ግን እንዳንች ያለ ባያገኝ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለውን ልጁን ሰዶ ካንቺ ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነሥቶ ሰው ኾነ፡፡ ተቀዳሚ ተከታይ ከሌለው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት (ክብርት) በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
  እዚህ ጋር አንዳንድ ወገኖች የሚያነሡትን ጥያቄ መልሰን እንለፍ፡፡ “ልመናስ ከዚያ በኋላ ስንኳን በሷ (ከበቁ በኋላ) በሌሎችም የለባቸውም፡፡ በቀደመ ልመናዋ የምታስምር ስለ ኾነ እንዲህ አለ እንጂ” ስለተባለ ምሥጢሩን ሳይረዱ “ቅዱሳን በአጸደ ነፍስ አያማልዱም” ለማለት የሚጠቅሱት ወገኖች አሉ፡፡ የዚህ ኃይለ ቃል ትርጓሜ ግን ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዕብራውያንን መልእክት በተረጐመበት በ፲፫ኛው ድርሳኑ ላይ፡- “ጻድቃን ይረክቡ ኵሎ በአሐቲ ተምኔቶሙ በአሐቲ ስእለት - ጻድቃን አንድ ጊዜ በለመኑት ልመና የሚሹትን ኹሉ ያገኛሉ” እንዳለው /ቁ.፻፶፱/ ቅዱሳኑ በአጸደ ሥጋ ሳሉ እግዚአብሔር አንድ ጊዜ “በስምሽ/ህ ለታረዙ ያለበሰ፣ ሕሙማንን የጐበኘ፣ ዝክርሽ/ህን የዘከረ…” እያለ በገባላቸው ቃል ኪዳን መሠረት በስማቸው የዘከረ፣ በስማቸው ሕሙማንን የጐበኘ፣ የመጸወተ እንደሚምርላቸው የሚያስረዳ ነው፡፡ ለምሳሌ፡- እግዚአብሔር፣ ዓለምን ዳግም በንፍር ውሃ የማያጠፋትና በየዕለቱ ቀስተ ደመናን የምንመለከተው ፡- “ቃል ኪዳኔንም ለእናንተ አቆማለሁ፤ ሥጋ ያለውም ኹሉ ዳግመኛ በጥፋት ውኃ አይጠፋም፤ ምድርንም ለማጥፋት ዳግመኛ የጥፋት ውኃ አይኾንም” ብሎ /ዘፍ.፱፡፲፩/ ለኖኅ አንድ ጊዜ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት እንጂ ኖኅ በየዕለቱ እንዲህ ስለሚለምን አይደለም፡፡ “አይለምንም” ሲባል ግን ክብሩን፣ ልዕልናውን፣ መንፈሳዊ ብቃቱን የሚያስረዳ እንጂ ማማለድ አይችልም ለማለት አይደለም፡፡ እንደውም ይህ ኃይለ ቃል ከማማለድ በላይ የኾነ ክብር እንደተሰጣቸው የሚያመለክት ነው፡፡ ምክንያቱም አንድ ጊዜ ለምኖ በየጊዜው የሚሹትን ማግኘት፤ ዕለት ዕለት እየለመኑ የሚሹትን ከማግኘት በላይ ልዕልናን፣ ክብርን፣ መንፈሳዊ ብቃትን ያሳያልና፡፡ አሁን ቅዱሳንን አማልዱን ስንላቸው አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ደጋግሞ እንደገለጸው ቃል ኪዳናችሁን አሳስቡልን ስንል ነው /ቅዳ.ማር. ቁ.፻፷፬-፻፸፩ ይመልከቱ/፡፡
፪. ንግባእኬ ኀበ ጥንተ ነገር - ወደ ቀደመው ነገር እንመለስ፡፡ አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ! አንቺን ብቻሽን ትውልደ ሴም፣ ትውልደ ካም፣ ትውልደ ያፌት (ትውልድ ኹሉ) ያመሰግኑሻል /ሉቃ.፩፡፵፰/፡፡ ፱ ወር ከ፭ ቀን ማኅፀንሽን ዓለም አድርጐ የኖረብሽ ሀገረ እግዚአብሔር፣ መንግሥተ ሰማያት ሆይ! ነቢያት ላንቺ “ኢይትዐፀዉ አናቅጽኪ (በሮችሽ ኹል ጊዜ ይከፈታሉ - ንስሐ የሚገቡ ኃጥአንን ለመቀበል)፤ ወኢይጸልም ወርኅኪ (ጨረቃሽ አይቋረጥም)፤ ወኢየዐርብ ፀሐይኪ (ፀሐይሽ ከዚያ በኋላ አትጠልቅም - ፈጣሪሽ አያልፍም)፤ እስመ እግዚአብሔር ብርሃንኪ ለዓለም (ለዘለዓለም ብርሃንሽ እግዚአብሔር ነውና)” /ኢሳ.፷፡፲፩፣፳/፤ “ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር - የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ! ስላንቺ የተነገረው ነገር ድንቅ (ልዩ) ነው” /መዝ.፹፮፡፫/ እያሉ ድንቅ ድንቅ ነገርን ተናገሩልሽ፡፡ በርግጥም ሰማይና ምድር የማይችሉትን አምላክ የአንቺን ማኅፀን ከተማ አድርጎ ፱ ወር ከ፭ ቀን መኖሩ፤ ያለ ዘር ያለ ሩካቤ አካላዊ ቃልን መፀነስሽ፤ በኅቱም ድንግልና መወለዱ፤ የድንግልና ጡቶችሽን ማጥባትሽ ድንቅ ነው፡፡
 ደስ ብሏቸው የሚኖሩ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣ የመላእክት ማደሪያ ኹነሻልና የምድር ነገሥታት ይህን ዜናሽን ሰምተው፣ ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን ምረረ ገሃነምን ዐውቀው መንነው ይሄዳሉ፡፡ እነርሱ ብቻ አይደሉም፤ ሠራዊቶቻቸውም ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን ምረረ ገሃነምን ዐውቀው መንነው ይሄዳሉ፡፡ አንድም ብርሃን ልጅሽን አምነው ጸንተው ይኖራሉ፡፡ አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ! አንቺን ብቻሽን ትውልደ ሴም፣ ትውልደ ካም፣ ትውልደ ያፌት ያመሰግኑሻል /ሉቃ.፩፡፵፰/፤ ካንቺ ለተወለደውም ይሰግዱለታል፤ዐቢይ እግዚአብሔር - እግዚአብሔር ታላቅ ነው” እያሉም ያከብሩታል፤ ያገኑታልም፡፡ “ዐቢይ እግዚአብሔር” እያሉ ከሚያከብሩት ከሚያገኑት ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፫. እንተ በአማን ንጹሕ ዝናም” የተባለ፣ የነፍሳትን ጥም ያበረደ የሕይወት ዝናም፣ የሕይወት ጠል፣ የሕይወት ውሃ ክርስቶስን ቋጥረሽ (በድንግልና ፀንሰሽ፣ በድንግልና ወልደሽ) የታየሽልን እውነተኛ ደመና አንቺ ነሽ፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ አባ ጊዮርጊሥ ዘጋሥጫም፡- “ንዑ እንከ ከመ ናልዕላ ለዛቲ ደመና ብርሃን እንተ ጾረቶ ለማየ ዝናም ንጹሕ- ንጹሑን የዝናም ውሃ የተሸከመችውን የብርሃን ደመና ኑ ከፍ ከፍ እናድርጋት” ብሎ ጋብዞናል /አርጋኖን ዘሠሉስ ፮፡፪/፡፡ ስትወልጂው ማኅተመ ድንግልናሽ አለመለወጡ፤ አካላዊ ቃል ሰው ሲኾን አምላክነቱ ላለመለወጡ፣ ድንግል ወእም (ድንግልም እናትም) ስትባዪ መኖርሽም ልጅሽ  አምላክ ወሰብእ (ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው) ሲባል ለመኖሩ ምሳሌ ነውና አብ የልጁ ምልክት አደረገሽ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ቢያድርብሽ፣ ኀይለ ልዑል ወልድም ሥጋሽን ቢለብስ፤ አንድም መንፈስ ቅዱስ ከሦስቱ ግብራት (ማለትም ከሩካቤ፣ ከዘር፣ ድንግልናን ከመለወጥ) ቢከለክልሽ፣ ኀይለ ልዑል ወልድም ከሦስቱ ግብራት ቢከልልሽ ለዘላለሙ የሚኖር አካላዊ ቃልን ወለድሽልን /ሃይ.አበ.፻፲፡፳፱/፡፡ እርሱም ሰው ኾኖ ከኃጢአት አንድም ከኃጢአታችን ፍዳ አዳነን፡፡
 ደስ ያለህ ባለ ምሥራች ገብርኤል ሆይ! ወደኛ የመጣ የጌታን ልደት ነግረኸናልና ላንተ የተሰጠ ክብር ፍጹም ነው፡፡ አንድምወነዋ ተወልደ ፍስሐ ዘይከውን ለክሙ ወለኩሉ ዓለም - እነሆ ለሕዝቡ ኹሉ የሚኾን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁ” ብለህ /ሉቃ.፪፡፲/ የጌታን ልደት ለኖሎት (ለእረኞች) ነገርኻቸዋልና ለአንተ የተሰጠ ክብር ፍጹም ነው፡፡ “እግዚአብሔር ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነሥቶ ካንቺ ጋራ አንድ ይሆናልና ደስ ይበልሽ” ብለህ /ሉቃ.፩፡፴/ ለእመቤታችን ነግረኻታልና ለአንተ የተሰጠ ክብር ፍጹም ነው፡፡ እንዲህ ካለ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳነሣን ለምኚልን፡፡
፬. መንፈስ ቅዱስ ቢያድርብሽ፣ ኃይለ ልዑል ወልድም ሥጋሽን ቢለብስ ጸጋን አገኘሽ፡፡ መንፈሰ ቅዱስ ከሦስቱ ግብራት ቢከለክልሽ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብለው ከሚመሰገኑት ከሦስቱ አካላት አንዱን ቅዱስ ወለድሽልን፡፡ ሰውን ኹሉ የሚያድን እርሱም ሰው ኾኖ አዳነን፡፡ ሰው ኾኖ ካዳነን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፭. ቀድሞ ከነበሩት ጋር አንድ ኾኖ አንደበታችን የድንግልን ሥራ ያመሰግናል፡፡ ዛሬ ካሉት ጋር ኾኖም እመቤታችንን ያመሰግናል፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዳዊት አገር በዳዊት ባሕርይ ካርሷ ተወልዷልና፡፡ አሕዛብ ሆይ! እመቤታችንን እናመስግናት /ሃይ.አበ.፷፮፡፳/፡፡ እናትን ኹናለችናድንግልናም ደርባለችና ኑ እመቤታችንን እናመስግናት፡፡ አካላዊ ቃል ካንቺ ሰው የኾነ አደፍ ጉድፍ የሌለብሽ ድንግል ሆይ! ደስ ይበልሽ፡፡ አደፍ ጉድፍ የሌለብሽ ንጹሕ ሽቱ ዕቃ ሆይ! ደስ ይበልሽ፡፡ የሽቱን ዕቃ ጢስ እንዳይተንበት ትቢያ እንደይበንበት ቤት ሰፍተው፣ ሰቅለው፣ ተንከባክበው ያኖሩታል፡፡ እርሷንምመንፈስ ቅዱስ ዐቀባ እምከርሠ እማ ከመ ኢትጌጊ - እንዳትበድል ድንግልን ከእናቷ ሆድ ጀምሮ የጠበቃት መንፈስ ቅዱስ እንዳትረክስም ያነጻት ለወልድ ዋሕድም ማደርያ ያደረጋት እርሱ ነው” ይላታልና /አርጋኖን ዘእሑድ፣ ቁ.፲፰/፡፡ ዐጤ ዘርዐ ያዕቆብም በነገረ ማርያም መጽሐፉ፡- “ንጽሕት ይእቲ እምኵሉ ትሕዝብት ወእምኵሉ ርስሐተ ኀጢአት - እርሷ (እመቤታችን) ከርስሐተ ኀጢአትና ከመጠራጠርም ኹሉ ንጽሕት ናት” ብሏል /ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን፣ ገጽ ፶፮-፶፯/፡፡

 ስለ ቀደመ ሰው (ስለ አዳም) ዳግመኛ አዳም የተባለክርስቶስ እናቱ ነባቢት ገነት ሆይ! ደስበልሽ፡፡  ከአባቱ ዕሪና (አንድነት) ያልተለየ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው እርሱን የወሰንሺው በፍጹም ጌጥ ያጌጠች ንጹሕ የሰርግ ቤት ሆይ! ደስ ይበልሽ፡፡ የሰርግን ቤት አስቀድመው በሐር ያንቆጠቁጡል፤ ያነጽፉታል፤ ይጎዘጉዙታል፤ ሽቱ ያረበርቡበታል፤ ሐረግ ወርድ ይሥሉበታል፡፡ እንደዚህም ኹሉ አስቀድመን እንደተናገርን መንፈስ ቅዱስ ድንግልን ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ ጠብቋታልና እንዳትረክስም አንጽቷታልና እንዲህ አለ፡፡  አንድም በየጊዜው የጸጋ ክብር ይጨመርላታልና፡፡
ባሕርየ መለኮቱ ያልለወጠሽ ዕፀ ጳጦስ ሆይ! ደስ ይበልሽ፡፡ (ዕፀ ጳጦስ ማለት በሀገራችን ደደሆ፣ እንጆሪ የምንለው ነው) /ዘጸ.፫፡፩-፫/፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም የዚህን ግሩም ምሥጢር “ዲያተሳሮን” በተባለ መጽሐፉ ሲተነትነው ፡- “ፈጣሬ ዓለማት ቅዱስ እግዚአብሔር የወደቀውን ፍጥረቱ ወርዶ ያነሣው ዘንድ፣ ቆሽሾ የነበረው ሕንፃዉንም (ሰውንም) ይወለውለው ዘንድ ተገቢ ነበር፡፡ በመኾኑም ፈጣሪ ራሱ በሰው ልጆች ላይ ፈርዶት የነበረውን ፍርድ የባሕርይ ልጁ እንዲሸከመው ካደረገ (በእርግጥም አድርጐታልና) የሰው ልጅ ወደ ጥንተ ተፈጥሮው ይመለሳል ማለት ነው (በርግጥም ተመልሷል)፡፡ ይህ አካላዊ ቃል፣ በሰው መተላለፍ ምክንያት በቅለው የነበሩት እሾክንና አሜኬላን ያቃጥል ዘንድ የመጣ ነባቢ ፍሕም ነው /ዘፍ.፫፡፲፰፣ ኢሳ.፱፡፲፰/፡፡ መጥቶም በማኅፀነ ድንግል አደረ፤ አነጻው፤ የጭንቅና የርግማን ቦታ የነበረው ማኅፀን ቀደሰው /ዘፍ.፫፡፲፮/፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴ ያየው ነበልባል ሐመልማሉን አላጠፋውም፤ ይልቁንም  እንዲለመልም አደረገው እንጂ /ዘጸ.፫፡፪-፫/፡፡ የነጠረ ወርቅ የሚመስል አካልም ወደ ነበልባሉ ገባ፤ ኾኖም አሁንም እሳቱ አልፈጀውም፡፡ ይኸውም በዘመኑ ፍጻሜ ሊመጣ ላለው ነባቢ እሳትና የድንግልን ማኅፀን አለምልሞ ቁጥቋጦውን እንደከደነውም እንደሚከድናት የሚያስረዳ ነው” ብሏል፡፡ ዳግመኛም አባ ጊዮርጊሥ ዘጋሥጫ የእሳተ መለኮት መምጣት ምክንያቱ ሲገልጽ፡- “… (ጌታችንም) የዓለምን ኃጢአት በትከሻው ተሸክሞ ወደ ዕፀ መስቀል ወጣ፡፡… ያን ጊዜ እግዚአብሔር እሾኽና አሜኬላ ይብቀልብህ ብሎ በረገመው ጊዜ በአዳም ሥጋ የበቀለ የኃጢአት እሾኽ ተቃጠለ” ብሏል /መጽሐፈ ምሥጢር ፲፱፡፳፩/፡፡
 በኪሩቤል አድሮ የሚኖረው ሰማያዊ መለኮትን በሥጋ የተሸከምሽው ማኅደርምተባልሽ እመቤትነትን ከገረድነት፣ እናትነትን ከድንግልና ጋር አስተባብረ የያዝሽ ሰማይ ሆይ! ደስ ይበልሽ፡፡ለዚህ ነገር፡-አምላክ ለኾነ ለሥጋ ከሥላሴ ጋራ በአንድነት ምሥጋና ይገባዋል፤ በምድርም ዕርቅ ተወጠነ” እያልን ንጹሐን ከኾኑ መላእክት ጋር በፍጹም ደስታ ደስ ተሰኝተን እናመስግን፡፡ ክብር የክብር ክብር ያለው እርሱ አንቺን ለእናትነት መርጧልና ንጹሐን ከኾኑ መላእክት ጋር በፍጹም ደስታ ደስ ተሰኝተን እናመስግን /ሉቃ.፪፡፳/፡፡ አንቺን ለእናትነት ከመረጠ ልጅሽ ጽንዕት ሥርጉት በቅድስና በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳነሳን ለምኚልን፡፡

፮. ከቅዱሳን ክብር የእመቤታችን ክብር ይበልጣል፡፡ አካላዊ ቃልን ለመቀበል በቅታ ተገኝታለችና፡፡መላእከት የሚፈሩትን፣ ትጉሃን በሰማያት የሚያመሰግኑትን ድንግል ማርያም በማኅፀንዋ ቻለችው፡፡ እንዲህም ከኾነ ከመላእክት ትበልጣለች፤ ከሱራፌልም ትበልጣለች፤ ከሦስቱ አካል ላንዱ ማደሪያ ኾኖለችና፡፡ ኢትዮጲያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስም ይህን በኆኅተ ብርሃን መጽሐፉ ላይ ሲገልጽ “አንቲ ተዓብዪ እምኪሩቤል ወትፈደፍዲ እምሱራፌል፣ እምሱራፌል ወኪሩቤል በሠረገላ እሳት ይጸውርዎ ወበምጽንዐ እሳት ይጼንዑ መንበሮ፤ ወአንቲሰ ጾርኪዮ በከርሥኪ ወሐዘልኪዮ በዘባንኪ ወሐቀፍኪዮ በአብራክኪ ህየንተ ሠረገላ እሳተ አብራክኪ ኮነ ወህየንተ ምጽንዐቲሁ ዘእሳተ እደውኪ ኮና - ከኪሩቤል ይልቅ አንቺ ትበልጫለሽ፤ ከሱራፌልም ይልቅ አንቺ ትልቂያለሽ፤ ኪሩቤልና ሱራፌል በእሳት ሠረገላ ተሸክመውታልና፤ አንቺ ግን በማኅፀንሽ ወሰንሺው፤ በዠርባሽም አዘልሺው፤ በጉልበቶችሽም ዐቀፍሽው፤ ጉልበቶችሽም እንደ እሳት ሠረገላ ኾኑ፤ እጆችሽም እንደ እሳት አዕማድ ኾኑ” በማለት የተሰጣት ክብር ከኪሩቤል ከሱራፌል የበለጠ መኾኑን አስተምሯል፡፡
 የነቢያት ሀገራቸው ኢየሩሳሌም ይህች ናት፡፡ መንግሥተ ሰማያትን የሚያወርሰን ከእርሷ በነሣው ሥጋ ምክንያት ነውና ደስ ብሏቸው የሚኖሩ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣ የመላእክት ማደሪያቸው ይህቺ ናት፡፡ በድንቁርና በቀቢፀ ተስፋ ለነበሩ ሰዎች ዕውቀት ተሰጣቸው፤ ክርስቶስ ተወለደላቸው /ኢሳ.፱፡፪/፡፡ ወንጌል ተጻፈላቸው /ሉቃ.፩፡፩-፬/፡፡ በቅዱሳን አድሮ የሚኖር እግዚአብሔር እኛን ለማዳን ሰው ኹኗዋልና በሞተ ሥጋ፣ በሞተ ነፍስ ለነበሩ ሰዎች ልጅነት ተሰጣቸው /ዮሐ.፩፡፲፫/፡፡ በኃጢአት በክሕደት ለነበሩ ሰዎች ሃይማኖት (አሚን) ተሰጣቸው /ማቴ.፬፡፲፬/፡፡ ተወዳጆች ሆይ! ይህን ድንቅ ምሥጢር እዩ፡፡ ስለ ተገለጸን ምሥጢር ምስጋና አቅርቡ፡፡ ከዚህ ቀደም ሰው ኾኖ የማያውቀው እንግዲህም ወዲህ ሰው ማይኾነው ሰው ኾኗልና ይህን ድንቅ ምሥጢርእዩ፡፡ ቃል ከሥጋ ጋር ቢዋሐድ ጥንት የሌለው መለኮትሺሕ ከ፭፻ ዘመን ሲፈጸም ዘመን ተቀድሞት ወደ ኋላ ተገኘ፡፡ ቅድምና የሌለውም ሥጋ ቀዳማዊ አምላክ ተባለ፡፡ አንድም ጥንት (ቅድምና) የሌለው ሥጋ ቀዳማዊ አምላክ ተባለ፡፡ ዘመን የማይቆጠርለትም መለኮት ፲፪ ዓመት ኾነው /ሉቃ.፪፡፵፪/፤ ዓመት ሞላው ተብሎ ዘመን ተቆጠረለት /ሉቃ.፫፡፳፫/፡፡ አንድም አካላዊ ቃል በጎላ በተረዳ ሰው ኹኗልና በኵ ያልነበረ መለኮት በኵር ተባለ /ማቴ.፩፡፳፭/፡፡ ክብር የሌለውም ሥጋ ክቡር አምላክ ተባለ፡፡  በገዥነት የማይታወቅ ሥጋ በገዥነት ታወቀ፤ በተገዢ ሥጋ ታይቶ የማይታወቅ መለኮትም በተገዢ ሥጋ ታየ፡፡ ቅድመ ዓለምነበረው፣ በማዕከለ ዓለም ያለው፣ መቼም መች የሚኖረው ኢየሱስ ከርስቶስ እንሰግድለትና እናመሰግነው ዘንድ ከአብ ከባሐርይ አባቱ ከመንፈስ ቅዱስ ከባሕርይ ሕይወቱ ጋራ አንድ ባሕርይ ነው፡፡ ከአብ ከባሕርይ አባቱ ከመንፈስ ቅዱስ ከባሕርይ ሕይወቱ ጋራ አንድ ባሕርይ ከሚኾን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንደይነሣን ለምኚልን፡፡

፯. ነቢዩ ሕዝቅኤል የእርሷን ነገርበድንቅ ቁልፍ የተቈለፈች ደጅ በምሥራቅ አየሁ” ብሎ ተናገረ /ሕዝ.፵፬፡፩-፪/፡፡ ከእግዚኣ ኃያላን በቀር ሳይከፍታት ገብቶ ሳይከፍታት የወጣ የለም፡፡ እግዚአ ኃያላን እሱ ሳይከፍታት ገብቶ ሳይከፍታት ወጣ እንጂ፡፡ እግዚአ ኃያላን ከሚባለው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን አንዳነሣን ለምኚልን፡፡
፰. ኆኀትም (ድጅም) የተባለች መድኃኒታችንን ጌታንወለደችልን ድንግል ናት፡፡ እሱን ከወለደችው በኋላ እንደ ቀድሞ ማኅተመ ደንግልናዋ ሳይለወጥ ኑራለቸና፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግም፡- “… አንተ መናገር የተሰጣቸውን ሠረገሎች ድምፅ የሰማህ ባለ ሞገስ ሆይ (ሕዝ.፫፡፲፫)! እንደዚሁም የክንፎቻቸውን ድምፅና የዚያን ሠረገላ ታላቅ እንቅስቃሴ የሰማህ ሆይ (ሕዝ.፲፡፭)! አንተ የኪሩቤልን መልክ መለወጥ ያየህ የበራልህ ነፍስ ሆይ! እንዲሁም እኒያ የእሳት ላንቃዎች በከፍታ ላይ የተቀመጠውን ሲያመሰግኑ የሰማህ ሕዝቅኤል ሆይ (ሕዝ.፩፡፬-፳፰) ና! አንተ የቡዝ ልጅ ሆይ (ሕዝ.፩፡፳፫) ና! የተጠቀለለውን የትንቢትህን ቃል ብራና አምጣልን፡፡ አንተ ቁምና እውነትን ተናገር፤ ሌሎቻችን ኹሉ ዝም እንበል፡፡ ካየኻቸው ራዕዮች መካከል ድንግል ማርያም ታይታህ እንደኾነ፤ ፍጥረት ኹሉ ውበቷን ያይ ዘንድ መልኳን ግለጥልን፡፡ በትንቢትህ ውስጥ የጌታህን እናት የሚመለከት አንዳች ነገር ካለ ይህ ለሚሰሙት እጅግ ውድ ስለኾነ ተነሣና አብራራልን፡፡ ይህም ያም (መናፍቅ) ከመውለዷ በኋላ ድንግል አልነበረችም በማለት ይናገራልና እውነት ድንግልናዋን አጥታ እንደኾነ እስኪ አንተ አስረዳን፡፡ ሕዝቅኤል ሆይ! ዛሬ የአንተ ተራ ነውና እስኪ ተናገር፡፡ ስለ እመቤታችን ማርያም ተናገርና ከንቱ ምርምሮችን ግታልን፡፡ እስከ አሁን በትንቢት ተነግሮ የነበረው ምን እንደነበር እንስማ፡፡ የማትመረመር ስለኾነችው ስለ ድንቅ እናታችን ይህ ነቢይ በትንቢቱ ውስጥ እንዲህ ተናግሮ ነበር፡- ‘ወደ ምሥራቅም ወደሚመለከተው በስተ ውጭ ወዳለው ወደ መቅደሱ በር አመጣኝ፤ ተዘግቶም ነበር። እግዚአብሔርም። ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም፥ ሰውም አይገባበትም፤ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ገብቶበታልና ተዘግቶ ይኖራል።’ አንተ የመንፈስ ነቢይ ሆይ! ይህ ቃል ምን ማለት እንደኾነ እስኪ ገልጠህ አብራራልን፡፡ በትንቢት የተነገረው የተዘጋው በር ድንግል ማርያም ናት፡፡ ምክንያቱም መሲሑ ጌታ በእርሱ በኵል ወደ ዓለም መጥቶ ዝግ አድርጎ ትቶታልና፡፡ ጌታ በዚህ በር ሲገባ እንዳልከፈተው ዕብራዊ የኾነ ሕዝቅኤል ከእኛ ጋር አብሮ ይህንኑ ይመሰክራል፡፡ እግዚአብሔር እንደወደደው በመውለድ በር ወደ ዓለም ገባ፡፡ ያንንም በር በድንግልና ዘጋው፡፡ ነቢዩ በሩ ተዘግቶ ያየው ያ ቤተ መቅደስ ስለ ድንግልናና ስለማይለወጥ ድንግልናዋ የሚያሳየን ነው፡፡ ቅዱሱ መሲሑ (ክርስቶስ) ሲኾን ቤተ መቅደሱም ማርያም ናት፡፡ የተዘጋውም በር በእርሷ የሚኖረውና ተፈትሖ የሌለበት የድንግልዋ ማኅተም ነው” ብሏል /Jacob of Serug, Homily on the Perpetual Virginity of Mary, pp VII-X/፡፡
 የማኅፀንሽ ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለበት በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል ነው፡፡ ለሰው ከማያዝን ከማይራራ፤ አንድም ለእርሱ ከሥላሴ ዘንድ ምሕረት ከሌለው፤ አንድም ኃጢአቱን ሸልጎ ከማይሠራ ከዲያብሎስ እጅ ያዳነን ጌታችንን የወለድሽው ሆይ! በደንግሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ ፍጽምት ነሽ፡፡ መርገም ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለብሽ /ኢሳ.፩፡፱/ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ እያማለድሽ የምታሰጭ ነሽ፡፡ ጌትነቱ እንደ ነገሥታት በጉልበት፣ እንደ ካህናት በሀብት፣ እንደ ጣዖታትም በሐሰት ባይደለ በክብር ባለቤት ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሸልና በዚህ ዓለም ከሚኖሩ ሰዎች ኹሉ ይልቅ ክብር ላንቺ ይገባል፡፡ አካላዊ ቃል መጥቶ ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነሥቶ ሰው ኾነ፡፡ ሰው ሰውኛውንም ኖረ፡፡ መሐሪ፣ ይቅር ባይ፣ ሰው የሚወደው ሰው ወዳጅ ነውና በልዩ  አመጣጡ መጥቶ አዳነን፡፡ “አ በተንባልአኮ በመልአክ አላ ለሊሁ እግዚእ መጸእ ወያድኅነነ - በአማላጅ አይደለም፤ በመልአክም አይደለም፡፡ እርሱ ራሱ፣ በራሱ ደም፣ በራሱ ሊቀ ካህንነት መጥቶ ያድናቸዋል እንጂ ” /ኢሳ.፷፫፡፱/ እንዲል እንደ ቀደመውረድኤት ሳይኾን በኩነት (ሰው ኹኖ) መጥቶ አዳነን፡፡ አንድም አምስት ሺሕ ካምሰት መቶ ዘመን ሲፈጸም አንድ ሰዓት ስንኳ ሳያሳልፍ በጽኑ ቀጠሮው መጥሮ አዳነን፡፡ በጽኑ ቀጠሮ መጥቶ ካዳነን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡

አነሣሥቶ ላስጀመረን አስጀምሮ ላስፈጸመን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይግባው አሜን፡፡

9 comments:

FeedBurner FeedCount