Showing posts with label ታላቅ መሆንን ስትፈልጉ. Show all posts
Showing posts with label ታላቅ መሆንን ስትፈልጉ. Show all posts

Sunday, May 27, 2012

ታላቅ መሆንን ስትፈልጉ ታላቅ መሆንን አትፈልጉ ከዚያም ታላቅ ትሆናላችሁ


ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ሲያሰተምር እንዲህ አለ፡- “ማንም ከእናንተ ታላቅ መሆን የሚወድ የእናንተ አገልጋይ ይሁን… ማንም ፊተኛ ሊሆን የሚወድ የእናንተ ባርያ ይሁን… ታላቅ መሆንን ማሰብ የክፉዎች ሐሳብ ነው… የመጀመርያነትን ስፍራ መፈለግ የክፋት ሁሉ ምንጭ ነው… ታላቅነትን መፈለግ ታናሽነት ነው፡፡
   ስለዚህ ይህን ልቡና ከእናንተ ገርዛችሁ ጣሉት… በእናንተ በክርስቲያኖች ዘንድ እንዲህ አይደለም… በአሕዛብ ዘንድ የመጀመርያነትን ስፍራ የሚይዙ በሌሎች ዘንድ አለቆች እንዲሆኑ ነው… በእኔ ዘንድ ግን የመጨረሻውን ስፍራ የሚይዝ እርሱ የመጀመርያ ነው፡፡
   ይህን ከእኔ መማር ትችላላችሁ… እኔ ምንም የነገሥታት ንጉሥ የአለቆችም አለቃ ብሆንም በፈቃዴ የባርያዎቼን የእናንተን መልክ እይዝ ዘንድ አልተጠየፍኩም… በሰዎች ዘንድ የተገፋሁ ሆንኩ… ተተፋብኝ… ተገረፍኩኝ… ይህም ሳይበቃኝ በመስቀል ሞት ሞትኩኝ፡፡ ነገር ግን ላገለግል ስለ ብዙዎችም ነፍሴን ቤዛ ልሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉኝ አልመጣሁም፡፡ ቤዛነቴም ለወዳጆቼ ብቻ ሳይሆን ለሚጠሉኝም ለሚወግሩኝም ለሚያሰቃዩኝም ጭምር ነው፡፡ የእናንተ አገልጋይነት ግን ለእናንተ ለራሳችሁ እንጂ ለሌሎች ቤዛነት የሚሆን አይደለም፡፡
  እንዲህ አድርጌ ስነግራችሁ ክብራችሁ ዝቅ ዝቅ ያለ መስሎ አይታያችሁ… ምንም ያህል ዝቅ ዝቅ ብትሉም እኔ የተዋረድኩትን ያህል አትዋረዱም… እኔ ይኼን ያህል ከመጨረሻው የክብር ጠርዝ ወደ መጨረሻው የውርደት ጠርዝ ብወርድም ለብዙዎች መነሣት ሆንኩኝ… ክብሬ ከመቃብር በላይ ሆነ… ክብሬ በዓለም ላይ ከአጥብያ ኮከብ በላይ ደመቀ፡፡ ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ከመወለዴ በፊት መታወቄ በመላእክት ዘንድ ብቻ ነበር… አሁን ሰው ከሆንኩኝ በኋላ ግን ክብሬ በመላእክት ብቻ ሳይሆን በሰው ዘንድም የታወቀ ነው፡፡

FeedBurner FeedCount