Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ16ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts
Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ16ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts

Monday, May 21, 2012

የዮሐንስ ወንጌል የ16ኛው ሳምንት ጥናት (ዮሐ.3፡13-21)!!

የዮሐንስ ወንጌል የ16ኛው ሳምንት ጥናት (ዮሐ.3፡13-21)!!

by Gebregziabher Kide on Wednesday, March 14, 2012 at 5:14pm ·
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!
“ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው /ቁ.13/። “ይህ አነጋገር ከኒቆዲሞስ ንግግር ጋር ምን ግንኝነት አለው” የሚል ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ ግንኝነትስ አለው፡፡ ምክንያቱም ኒቆዲሞስ ጌታችንን “ከእግዚአብሔር የተላከ መምህር” አድርጎ አስቦት ስለ ነበር ጌታ ኒቆዲሞስን “አንተ እንደምታውቃቸው ምድራውያን መምህራን አድርገህ አታስበኝ፤ ምክንያቱም ከእኔ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ደግሞም የወረደ የለም፡፡ በሌላ አገላለጽ እነዚህ መምህራን በዚህ ምድር ስታያቸው እዚህ ምድር ብቻ የሚታዩና ከሰማይ የሌሉ ናቸው፤ እኔ ግን እዚህ በግዙፍ ሥጋ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ብታየኝም ከአባቴ ጋራ በህልውና አንድ ነኝ፤ በሰማይም በምድርም ሙሉዕ ነኝ፤ ሰማያዊ ሀብትን ሰማያዊ ዕውቀትን ገንዘብ አድርጌ የመጣሁኝ እኔ ብቻ ነኝ” ሲለው ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች “ታድያ እርሱ ሙሉዕ በኵለሄ በመለኰቱ ሳለ እንዴት ወረደና ወጣ ይባላል?” ይላሉ፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስላቸዋለን፡- እንዲህ እየተባለለት ያለው ወልድ በመለኰቱ ዙፋኑን ትቶ መውረዱን ለመግለጥ ሳይሆን በሥጋ ማርያም ገዝፎ መታየቱን፣ የባሮቹን መልክ ይዞ መምጣቱን ለማመልከት ነው፡፡ የሰው ልጅ ብሎ ራሱን ሲገልጥም እርሱ ሙሉ ሰውነትን ማለትም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሥጋንና ፍጹም ነፍስን ነስቶ መገለጡን ለማመልከት ነው /St. John Chrysostom on the Gospel of John, hom.27:1/፡፡
 አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ያደረጉ ቅዱሳን ወደ ሰማይ ቢወጡም ዓለምን ለማዳን አልወረዱም፡፡ ስለዚህ እኛም መውጣት ከፈለግን ሠረገላም ይሁን አውሮፕላን ሳያስፈልገን እንወጣ ዘንድ እንዲያወጣን የወረደውን ጌታ እንመን፡፡ መውጣት ከፈለግን ከእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም እንዲል ብቻችንን መውጣት አንችልም፡፡ ዳግም ተወልደን የሙሽራው ብልቶች ከሆንን ግን ከእርሱ ጋር አንድ አካል ስለምንሆን መውጣቱ ቀላል ነው /Augustine, Sermon on the New Testament Lessons 41:7-8/፡፡
 “ሙሴ በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ ወልደ እጓለ እመሕያው ክርስቶስ ይሰቀል ዘንድ” መጥቷልና፡፡ የዚህ የዳግም ልደታችን ምንጭ አንድም የመውረዱ ምሥጢር መስቀል ነውና /ቁ.14-15/። እነዚህ ሁለቱም ምሥጢራት ማለትም የጥምቀቱና የመስቀሉ ምሥጢር ክርስቶስ ለምንጠላው እንኳን ድንቅ የሆነ ፍቅሩን ያሳየባቸው ምሥጢራት ናቸው፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ኃጢአት ሲያበዙ በመርዘኛ እባብ ተነድፈው ሙሴ በሰቀለው የነሐሱ እባብ ከሞት እንደተረፉ አሁንም በመርዘኛው እባብ (ኃጢአት ፍዳ ባለበት በዲያብሎስ) የተነደፍን ሁሉ በነሐሱ እባብ (ኃጢአት ፍዳ በሌለበት በንጹሐ ባሕርይ በጌታ ስቅለት) እንደምንድን እየተናገረ ነው፡፡ ልናስተውለው የሚገባ ነገር ግን ብዙ ጊዜ እባብ የክፋት ምሳሌ ብትሆንም ጌታችን (ሎቱ ስብሐትና) በነሐሱ እባብ እየተመሰለ ያለው ክፉ ሆኖ ሳይሆን በፍቃዱ “በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ…ኃጢአትን በሥጋ ለመኰነን” ስለ መጣ ነው /ሮሜ.8፡3፣ St. Gregory of Nyssa, Vita Moysis, PG 44:415/፡፡
ምክንያቱም፡- “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና” /ቁ.16/። የዘላለምን ሕይወት የሚሰጠን እርሱ ዘላለማዊ ስለሆነ ነው፤ ትንሣኤ ሕይወትን የሚሰጠን እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ስለሆነ ነው፡፡ እኛ ምንም አፈርና ጭቃ ብንሆንም እንዲሁ (ያለ ምክንያት) ወደደን፡፡ እኛን ለማዳንም አንድያ (የባሕርይ) ልጁን እንጂ ከባሮቹ አንዱን፣ ወይም መላእክትን፣ ወይም ሊቃነ መላእክትን አልላከልንም፡፡ ምንም ቸርነቱን ለመቀበል ያልተገባን ብንሆንም እንዲሁ ደሙን አፈሰሰልን /St. John Chrysostom. Ibid/፡፡
 “ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና” /ቁ.17/። በሌላ አገላለጥ በሥጋዊው እጅ ለሌለው እጅ፣ እግር ለሌለው እግር፣ ዓይን ለሌለው ዓይን በመንፈሳዊው ቅሉ ደግም ተሐድገ ለኪ ኃጢአትኪ- ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል ተሐድገ ለከ ኃጢአትከ- ኃጢአትህ ተሰርዮልሀል ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትኖራለህ እያለ ሊያድነው ካሳ ሊከፍልለት እንጂ ቀድሞ በፈረደበት ፍርድ ሌላ ፍርድ ሊፈርድበት አልመጣም፡፡ ስለዚህ “በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል” /ቁ.18/። ያላመነው ሁሉ ትንሣኤ ቢኖሮውም ትንሣኤ ለዘሐሳር ነው፡፡ አሁን ተፈርዶበታል ሲልም አስቀድሞ ለዚያ ተወስኗል ማለት ሳይሆን አስቀድሞ ባለማመኑ ያው ትንሣኤው ለፍርድ ነው ማለት ነው፡፡/ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ/፡፡
 “ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው” /ቁ.19/። “ይህ ማለት” ይላል ክርስቶስ “እኔ ዓለምን እፈርድበት ዘንደ መጥቼ ብሆን ኖሮ ሰዎች ላለማመናቸው ምክንያት ባገኙ ነበር፡፡ ነገር ግን አመጣጤ የሰው ልጅን በሙሉ ከጨለማ ወደ ብረሃን አወጣ ዘንድ ነው፡፡ ወደ ብርሃን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ማለትም በእኔ ያምኑ ዘንድ ፈቃደኞች ያልሆኑ ይፈረድባቸዋል፤ ስለ ተፈረደባቸውም ምክንያት የላቸውም” /St. John Chrysostom. Ibid/፡፡
“ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጎ እንደ ሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል” /ቁ.20-21/።
 እንግዲያስ ወንድሞቼ ሆይ! ጨለማው እንዳይጋርደን ወደ ብርሃን ለመውጣት እንቻኰል፤ እንድን ዘንድ እንንቃ፤ ጊዜ ሳለልን እንነሣ፤ ቀን ሳለልን ብርሃኑም  ሲያበራልን እንንቃ፤ ቀኑም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ወደ እርሱ ብንመጣ ኃጢአታችን ይቅርታ ይደረግለታል፡፡ ምንም ጽድቅ ሳይኖረን በባዶ ራሳችንን ከፍ ከፍ የምናደርግ ሁሉ ትርፉ በጨለማ መቅረት ነውና ወደ ብርሃን ክርስቶስ እንውጣ፡፡
 ሰው የእግዚአብሔር ፈቃድ ፍጥረት ነው፡፡ ኃጢአት ደግሞ የእኛ ፈቃድ ውጤት ነው፡፡ ስለዚህ አኛ ያደረግነውን ትተን እግዚአብሔር ወዳደረገልን የፍቅር ሥራ እንውጣ፡፡ የእኛ ሥራ ሕጸጽ እንዳለበት ስናውቅ ሕጸጽ ወደሌለበት የእግዚአብሔር ሥራ እንፍጠን፡፡ ንስሐ የመልካም ነገር ጅማሬ ናት፡፡ ሰው በጨለማ ውስጥ መኖሩን ሲያውቅ (በኃጢአት ውስጥ ለማለት ነው) ይቅርታ እንደሚያስፈልገውም ያውቃል፡፡
ይህን ሁሉ እንድናደርግ ሰውን እንዲሁ በማፍቀር ሰው የሆነው ጌታ ይርዳን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!!

FeedBurner FeedCount