Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ17ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts
Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ17ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts

Monday, May 21, 2012

ዳግመ ስምዑ ለዮሐንስ- የዮሐንስ ወንጌል የ17ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.3፡22-ፍጻሜ)!!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!
 ጌታችን አስቀድሞ የአይሁድ ፋሲካ ሲሆን ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፡፡ የሄደበትም ምክንያት ለበዓሉ የመጡትን ሰዎች ገቢረ ተአምራቱን አይተው አንድም ትምህርቱን ሰምተው እንዲያምኑ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ከዮሐንስ ለመጠመቅ ወደ ተሰበሰቡት ሰዎች ወደ ፈለገ ዮርዳኖስ ይሄዳል፡፡ አካሄዱም በዚያ የነበሩት ሰዎች ስለ ወንጌለ መንግሥት ሊሰበክላቸው ይገባ ስለ ነበር ነው፡፡ ስለዚህም ወንጌላዊው፡- “ከዚህ በኋላ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ ይሁዳ አገር መጣ፥ በዚያም ከእነርሱ ጋር ተቀምጦ ያጠምቅ ነበር” ይለናል /ቁ.22፣ /። “ያጠምቅ ነበር” ሲባልም በደቀመዛሙርቱ አድሮ ያጠምቅ ነበር ማለት ነው፤ እርሱ ራሱ ግን አላጠመቀምና /ዮሐ.4፡2/፡፡ “ለምንስ አላጠመቀም?” ቢሉ መጥምቁ እንደተናገረው ጌታችን የሚያጠምቀው በእሳትና በመንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ገና አልወረደም ነበር /ዮሐ.7፡39/፡፡ “ለምንስ ደቀ መዛሙርቱ አጠመቁ?” ቢሉ ደግሞ ሕዝቡ ከዮሐንስ ይልቅ ወደ ሐዋርያት ይመጡ ይገባልና፡፡ “ለምንስ ዮሐንስ ማጥመቁን አላቆመም?” ቢሉም የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት፡- “መምህራችን ዮሐንስ ማጥመቅ ካቆመ  የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት እንደሚያጠምቁ ሁሉ እኛም ማጥመቅ አለብን” ብለው ችግር በፈጠሩ ነበርና /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ፣ Homily on the Gospel of John, Hom.29/፡፡
  ስለዚህም “ወሀሎ ዮሐንስኒ ያጠምቅ በሄኖን በቅሩበ ሳሌም በማዕዶተ ዮርዳኖስ- ዮሐንስ ደግሞ በሳሌም አቅራቢያ በሄኖን በዚያ ብዙ ውኃ ነበርና ያጠምቅ ነበር፡፡ ብዙ ሰዎችም እየመጡ ይጠመቁ ነበር፤ ዮሐንስ ገና ወደ ወኅኒ አልተጨመረም ነበርና” /ቁ.23-24/።  በዚህን ጊዜ አርድእተ ዮሐንስ መምህራቸው ያጠመቃቸው ሰዎች ወደ ጌታ ሲሄዱ የጌታ ደቀ መዛሙርት ያጠመቋቸው ግን ወደ ዮሐንስ እንደማይመጡ አስተዋሉ፡፡ በዚህም ምክንያት የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት “የማን ጥምቀት ብትበልጥ ነው” ብለው ግራ ተጋቡ፡፡ በዮሐንስ እጅ ተጠመምቀው ነገር ግን ዮሐንስ እንደነገራቸው ወደ ጌታ ሲሄዱ የነበሩ አይሁድ አግኝተውም “የእኛ መምህር እያለ ወዴት ትሄዳላችሁ” ይልዋቸዋል፡፡ አይሁድም “የእናንተማ መምህር መስክሮ አለፈ እኮን” ሲልዋቸው “ስለ ማንጻት በመካከላቸው ክርክር ሆነ” /ቁ.25, Augustine, Tractes on the Gospel of John/።
  ከዚህ በኋላ አርድእተ ዮሐንስ “ወደ ዮሐንስ መጡና፡- መምህር ሆይ! በዮርዳኖስ ማዶ ከአንተ ጋር የነበረው አንተም የመሰከርህለት፥ እነሆ፥ እርሱ ያጠምቃል፤ ሁሉም ወደ እርሱ ይመጣሉ አሉት” /ቁ26/። በዚሁ ንግግራቸው ለዮሐንስ ያላቸውን ክብር “መምህር ሆይ!” በማለት ሲገልጡ ስለ ጌታችን ግን (ሎቱ ስብሐትና) ስሙን እንኳን ለመጥራት ተጠይፈው በንቀት “ከአንተ ጋር የነበረው ያጠምቃልና ስለዚህ ምን ትላለህ?” በማለት ሊያበሳጩት ይሞክራሉ፡፡
  ዮሐንስ ግን እነርሱ እንደገመቱት ሳይሆን በእጅጉ ሐሴት አድርገ፡፡ አሁንም እንደገና ስለ ክርስቶስ እንዲመሰክርላቸው ዕድል ስላገኘ ተደሰተ፡፡ በጥበብና በለሰለሰ ንግግርም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፡- “ከሰማይ ካልተሰጠው ማለትም ከእግዚአብሔር መምህርነትን ካልተሰጠው በቀር ሰው አንዳች ገንዘብ ማድረግ አይቻለውም፤ ይልቅ ክርስቶስን ስትተዉ ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ እንዳትገኙ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ /ሐዋ.5፡39/፡፡ እርሱ (ጌታ) ይህን ሁሉ የሚያደርገው በራሱ ሥልጣን ነውና፡፡ ደግሞም፡- ትምህረቴን የምትቀበሉ ከሆነና እኔንም የምትወዱኝ ከሆነ እኔ ክርስቶስ አይደለሁም፥ ነገር ግን መንፈቅ አስቀድሜ ከእርሱ በፊት ተልኬአለሁ እንዳልሁ ራሳችሁ ትመሰክሩልኛላችሁ። እኔ የተላክሁት የእርሱን መንገድ እጠርግ ዘንድ እንጂ ራሴን እሰብክ ዘንድ አይደለም፡፡ እኔ የመጣሁት በእርሱ ከፍ ከፍ እል ዘንድ እንጂ እርሱን ዝቅ ዝቅ እንዳደርግ አይደለም፤ የመጣሁት እንኳን የባሕርይ አባቱ ልኮኝ እንጂ ከራሴ አልነበረም፡፡ የተናገርኩትም ሁሉ ከእኔ ሳይሆን ከእርሱ የተቀበልሁትን እንደሆነ ቅሉ ምስክሮቼ እናንተው ናችሁ፡፡ ስለዚህ እኔ ታላቅ እንደሆንኩ አታስቡ፡፡ ታላቅስ ዓለማትን በእጁ የያዘ ጌታ በእውነት እርሱ ነው፤ ዘቦቱ መርዓት መርዓዊ ውእቱ- ሙሽራይቱ  ያለችው (ምእመናን ያሉት) እርሱ ሙሽራ (ክርስቶስ) ነው፤ ማለትም የሚያገባው እርሱ ያጨ ነው፡፡ ማለትም ምእመናንን ቤተ ክርስቲያንን ያጨ እርሱ ነው፡፡ ቆሞ የሚሰማው ሚዜው ያጨ አይደለም፡፡ ሚዜው የሙሽራውን ሚስት (ምእመናንን) ለራሱ ቢወስድ እርሱ አመንዝራ ነው፡፡ ስለዚህ ሚዜው በሙሽራው ድምጽ፣ በሙሽራው (በክርስቶስ) ወደ ሚስቱ (ወደ ቤተ ክርስቲያን) መምጣት እጅግ ደስ ይለዋል። የክርስቶስ ባለሟል የምሆን የእኔ ደስታ፣ የእኔ ሐሴት የእርሱ የሙሽራው መምጣትና ምእመናኑም ትምህርቱን ተቀብለዉትና አምነውበት ሲያድርባቸው ሲዋሐዳቸው ማየት ነው፡፡ ይህ ሁሉ ባይሆን ሐዘኔ በበዛ ነበር፡፡ አሁን ግን ስለ መጣ ይህ ደስታዬ ተፈጸመልኝ። የእኔ የማዘጋጀት መምህርነትም አለፈች፤ የእርሱ ግን መቼም መች አታልፍም፡፡ ስለዚህ እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ያስፈልጋል። እናንተም ከእኔ ይልቅ ወደ እርሱ ዘወር ትሉ ዘንድ ይገባል፡፡ ምንም በኃጢአት ወደ ተጨማለቅነው ያለ ኃጢአት በሥጋ ተገልጦ ቢመጣም ከላይ የመጣው እርሱ ከሁሉ በላይ ነውና ማለትም አማናዊው ሙሽራ የባሕርይ አምላክ ነውና፤ ከምድር የተገኘሁ እኔ ግን ምድራዊ ነኝ፤ አባቴ ዘካርያስ እናቴ ኤልሳቤጥ እያልኩም ምድራዊ ልደቴን አስተምራለሁ። ዓለምን ለማዳን ከእርሱ በቀር ከላይ የመጣ የሌለ እርሱ ግን ከሁሉ የሚበልጥ፣ ሰማያዊ ደግሞም አልፋና ዖሜጋ ነው። ከአባቱ ዘንድ በህልውና ያየውንና የሰማውንም ይህን ይመሰክራል፤ ምስክርነቱን ግን የሚቀበለው የለም። ምስክሩን የተቀበለ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ አተመ፤ ተናገረ። እግዚአብሔር የሾመው እውነተኛ መምህርም የእግዚአብሔርን ቃል ያስተምራል፤ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና። ማለትም የለበሰው ሥጋ የባሕርይ አምላክ የሆነ እንጂ ልዩ ልዩ ጸጋ እንደተሰጠን እንደ እኛ በተከፍሎ አይደለም /1ቆሮ.12፡4/፡፡ አባት ልጁን እንደ እኛ በፈቃድ ሳይሆን በባሕርይው ይወዷል፤ ሁሉንም በእጁ ጭብጥ በእግሩ እርግጥ አድርጎ ሰጥቶታል። ስለዚህ በእኔ ሳይሆን በዚሁ ሙሽራ በወልድ ያመነ የማታልፍ መንግሥተ ሰማይን ይወርሳል፤ በወልድ ያላመነ ግን  የእግዚአብሔር የቁጣው መቅሰፍት ማለት ፈርዶ ያመጣበትን ፍዳ ሲቀበል ይኖራል እንጂ የማታልፍ መንግሥተ ሰማያትን አይወርስም” /ቁ.27-36/፡፡
 ፀሐየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! እኛ ከአንተ እንወለድ ዘንድ አንተ ከእኛ ባሕርይ ስለተወለድክልን እናመሰግንሃለን፡፡ በጥምቀት ከአንተ ጋር ቀብረህ ዳግመኛ ከአንተ ጋር ስላነሣኸንም እናመሰግንሃለን፡፡ አዲስ ልደት፣ አዲስ ሕይወት፣ አዲስ ልብም ስለ ሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ በመርዛማው እባብ በፈቃዳችን ብንሞትም በአንተ ሞት ሞታችንን ስለገደልከው እናመሰግንሃለን፡፡ አባት ሆይ! አሁንም ምንም ኃጢአተኞች ብንሆንም አብሮነትህ አይለየን፡፡ ቅዱስ መንፈስህም አትውሰድብን፡፡ እኛ አንሰን አንተ ግን ከፍ ከፍ እንድናደርግህ ማስተዋሉን ስጠን፡፡ አለማወቃችን እንድናውቅ እርዳን፡፡ አንተ ማን መሆንህን ሳያውቁ ሙሽራይቱን (ቤተ ክርስቲያንን) የሚያሳድዱም አስታግስልን፡፡ እኛንም በምግባር በሃይማኖት እስከ ሕቅታ ድረስ እንድንታመን ደግሞም በፈተና እንድንጸና እርዳን፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን!!!!

FeedBurner FeedCount