Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ21ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts
Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ21ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts

Monday, May 21, 2012

በእውነት ክርስቶስ የዓለሙ መድኃኒት እንደ ሆነ ዓወቅን፤ አምነንበታልም - የዮሐንስ ወንጌል የ21ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡27-42)


ሰላመ እግዚአብሔር ይብዛላችሁ፡፡
 ደቀ መዛሙርቱ ምግብ ሊገዙ ወደ ከተማ ሄደው ነበር ብለናል /ዮሐ.4፡8/፡፡ አሁን ግን “መጡና ከአንዲት ደሀ ብቻ ሳይሆን ከሳምራይት ሴት ጋር ዝቅ ብሎ በመነጋገሩ ተደነቁ፤ ነገር ግን በግሩም ትሕትናው ስለተደነቁ ምን ትፈልጊያለሽ? ወይም ስለ ምን ትናገራታለህ? ያለ ማንም አልነበረም” /ቁ.27፣ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ Homily On John,Hom.33:3/።
  ወንጌላዊው እንደነገረን ሴቲቱ ውኃ ልትቀዳ ወደ ያዕቆብ ጕድጓድ መጥታ ነበር፡፡ ነገር ግን የክብር ንጉሥ ወደ ልቧ ሰተት ብሎ ሲገባ “ማድጋዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች” /ቁ.28/፡፡  በሐሴት ሠረገላ ተጭናም ወንጌሉን ለማፋጠን ተሯሯጠች፡፡ “ለሰዎችም ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” እያለች መላ ከተማውን ጠራርጋ ታመጣቸው ነበር። የሚገርመው ሴቲቱ የምታመጣቸው ሰዎች እንደ እንድርያስ ወይም ደግሞ እንደ ፊሊጶስ አንድ ወይም ሁለት ሰዎች ብቻ አይደሉም፡፡ መላ ከተማውን እንጂ፡፡ ትጋቷም ከኒቆዲሞስ በላይ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በወልደ እግዚአብሔር ቢያምንም እንደ እርሷ ግን በግልጥ ለመመስከር አልወጣም፡፡ በእውነት ይህች ሴት ከሐዋርያት ጋር ብትተካከል እንጂ አታንሥም፡፡ ሐሳብዋን ብቻ ይግለጥላት እንጂ እንዴት እንደምትነግራቸው እንኳን የቃላት ምርጫ አታደርግም፡፡ እናም “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?”  ትላቸዋለች፡፡ ተጠራጥራ አይደለም፤ መጥተው ራሳቸው ለራሳቸው እንዲወስኑ እንጂ፡፡ ስለዚህም “ኑና እዩ፤ አይታችሁም እመኑ” እያለች ከነፍሳቸው እረኛ ጋር እንዲገናኙ ትፈልጋቸው ነበር፡፡ ሰዎቹም የምትነግራቸውን ነገር ለማየትከከተማ ወጥተው ወደ ጌታችን ይመጡ ነበር” /ቁ.29-30/። የሚገርመው ደግሞ ይህች ሴት አዋልደ ሰማርያን ላለማየት ብላ በጠራራ ፀሐይ ውኃን ለመቅዳት የመረጠች ሴት ነበረች፡፡ አሁን ግን እውነተኛው ፀሐይ ሲነካት ሐፍረቷ እንደ በረዶ ተኖ ጠፋ፡፡ ስለዚህም ቀድሞ ወደምታፍራቸው ሰዎች በመሄድ “አንድ ነብይን ትመለከቱ ዘንድ” ሳይሆን “ያደረግሁትን ሁሉ፣ ምሥጢሬን ሁሉ የነገረኝን ሰው ትመለከቱ ዘንድ ኑ” እያለች ሕዝቡን ጠራቻቸው /St.John Chrysostom, Hom.34:1/፡፡
 ይህም ሲሆን ሳለ ደቀ መዛሙርቱ “ጌታችን ብዙ መንገድ በመሄድ ደክሟልና፤ ደግሞም ጠራራ ፀሐይ ነውና

FeedBurner FeedCount