Showing posts with label ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነቢይ ነው. Show all posts
Showing posts with label ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነቢይ ነው. Show all posts

Wednesday, June 13, 2012

ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነቢይ ነው- የዮሐንስ ወንጌል የ27ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.6፡1-15)!!


          በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

 ተወዳጆች ሆይ! ከክፉዎች ጋር ክፉዎች አንሁን፡፡ ይልቁንም ክፋታቸው በእኛ ላይ ምንም ዓይነት ጕዳት ሊያመጣ እንደማይችል እንረዳ፡፡ አንድ የሚፈነዳ መሣርያ ድንጋይ ላይ ቢወረወር ተስፈንጥሮ ወደ ወረወረው ሰውዬ ይመለሳል፤ ይጐዳዋልም፤ ባስ ካለም ሕይወቱን ሊያሳጣው ይችላል፡፡ ምናልባት የተወረወረው መሣርያ ለስላሳ መሬት ላይ አርፎ ቢሆን ግን መሬቱ የመሣርያውን ግለት ስለሚያቀዘቅዘው ሰውዬውን ባልጐዳው ነበር፡፡ በእኛ ላይ ክፋትን የሚፈጽም ሰውም እንደዚሁ ነው፡፡ እኛ መልሰን ክፋት የምናደርግበት ከሆነ ክፋቱን ይበልጥ ይገፋበታል፤ እኛ ትዕግሥተኞችና ሰው ወዳዶች ብንሆን ግን ክፋቱን እንዲመለከት መስታወት ስለምንሆነው ከክፋቱ ይቀዘቅዛል፡፡ ይህን የምንለው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ይልቁንም ጸሐፍትና ፈሪሳውያን ጌታችን ከዮሐንስ ይልቅ ደቀ መዛሙርት እንደሚያደርግ በሰሙ ጊዜ በእርሱ ላይ ክፋትን ለመፈጸም ወደ ቃና ዘገሊላ ስለሚሄዱ እንጂ፡፡ ሰው አፍቃሪው ጌታ ግን ይህን ክፋታቸው ስላወቀባቸው እንዳይገፉበትና ራሳቸውን የበለጠ እንዳይጐዱ ስለወደደ እነርሱ ወዳሉበት ወደ ቃና ዘገሊላ አልሄደም፡፡  ይልቁንም “የጥብርያዶስ ባሕር ወደሆነው ወደ ገሊላ ባሕር ማዶ ተሻገረ” እንጂ /ቁ.1/፡፡ ሲሄድም “በበሽተኞች ያደረገውን ምልክቶች አይተው ብዙ ሰዎች ተከተሉት” /ቁ.2፣ ምዕ.5፡9/። እነዚህ ሰዎች ሐዋርያው “በልሳን መናገር (በአጠቃላይ ተአምራትን ማድረግ!) ለማያምኑ ምልክት ነው እንጂ ለሚያምኑ አይደለም” እንዳለው ከጌታችን ትምህርት ይልቅ ተአምራቱ ይማርካቸው ነበር፡፡ /1ቆሮ.14፡22፣ Saint John Chrysostom, Homilies on St. John, Hom: 42:1/።
 ከዚህ በኋላ “አስተምራችሁ ገስጻችሁ፣ መክራችሁ ዘክራችሁ የራሳችሁ የሆነ የጽሞና ጊዜ ያስፈልጋችኋል፤ ከጥብብ ምንጭ ከእግዚአብሔር ጋር የምትገናኙበት ልዩ ጊዜ ሊኖራችሁ ይገባል፤ እንዳትታበዩ ሥጋችሁን የምትጐስሙበት ትሕርምት፣ ጾም ጸሎት ያስፈልጋችኋል” ሲልወደ ተራራ ወጣና በዚያ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ተቀመጠ” /ቁ.3/።  ይህም ሲሆን የአይሁድ በዓልም ፋሲካ ቀርቦ ነበር” /ቁ.4/፡፡ ሆኖም ግን ጌታችን ወደዚሁ ገቢረ በዓል አይሄድም፡፡ አስቀድመን እንደተነጋገርነው በቤተ መቅደሱም ያሉት ጸሐፍትና ፈሪሳውያን አብዝተው ሊገድሉት ይፈልጋሉና፡፡ ስለዚህ ፈርቶ ሳይሆን ጊዜው ስላልደረሰ፣ አንድም ለክርስቲያኖች መሸሽ ኃጢአት አለመሆኑን ለማሳየት፣ አንድም እነዚህ ሰዎች እርሱን የጐዱ መስሎዋቸው ራሳቸውን እንዳይጐዱ፣ አንድም ነፍሱ በዓላቶቻቸውን እንደጠላች ደግሞም እንዳለፉ ለማሳየት ወደ ገቢረ በዓላቸው አይሄድም /ኢሳ.1፡14፣ Saint John Chrysostom, Ibid /፡፡

    ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በተራራው በተቀመጠ ጊዜ፣ ከልጆቹ ጋር መነጋገር በጀመረ ጊዜ ዓይኖቹን አራምዶ አየ፤ ብዙ ሕዝብም ወደ እርሱ ሲመጡ ተመለከተና አዘነላቸው /ቁ.5፣ ማቴ.14፡6/፡፡ አቤት ፍቅር! አቤት ቸርነት! አቤት ርኅራኄ! ወንድሞቼ እስኪ የጌታችንን የፍቅር ፊት በኅሊናችሁ ሣሉት! እስኪ የርኅራኄና ሰው ወዳዱ ፊቱን በልቡናችሁ ቅረጹት፡፡ አያችሁ?! ጌታ እንዲህ ይወደናል! አባታችን እንዲህ ይሳሳልናል! ወዮ አባት ሆይ ስላፈቀርከን እናመሰግንሃለን!!

   ከዚህ በኋላ ኅብስቱን አበርክቶ ሊሰጣቸው እንደሚችል ኃይልና ሥልጣን እንዳለው ቢያውቅም ደቀ መዛሙርቱ ገና በእምነት ያልጠነከሩ ስለነበሩ እምነታቸው ይጨምር ዘንድ በፊልጶስ በኵል፡-“ለእኒህ ሰዎች የምንመግባቸውን እንጀራ ከወዴት እንገዛለን?” አላቸው። ይህም እግዚአብሔር ሙሴን ለማሳመን ያደረገውን ተአምር ያስታውሰናል፡፡ ሙሴ እስራኤላውያንን ከፎርዖን አገዛዝ እንዲያላቅቃቸው በእግዚአብሔር ሲታዘዝ

FeedBurner FeedCount