Showing posts with label ድንግል ማርያም. Show all posts
Showing posts with label ድንግል ማርያም. Show all posts

Friday, May 18, 2012

=+=ድንግል ማርያም በቅ/ገብርኤል ሠላምታ (ክፍል ሁለት)=+=በመምህር ቃለአብ ካሳዬ=+=


ያለፈው ክፍል
ድንግል ማርያም በቅ/ገብርኤል ሠላምታ (ክፍል 1)

አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ

            ይህን የመልአኩን ቃል ቅ.ኤልሣቤጥም ሳትጨምር ሳትቀንስ ደግመዋለች (ሉቃ 1.47)። የድንግል ማርያም ከሴቶች ሁሉ ተለይቶ መባረክ በቅ.ገብርኤልና በቅ.ኤልሳቤጥ መመስከሩ ይህ እውነት በሠማይና በምድር የጸና መሆኑን ያሳያል። ገብርኤል ከሰማይ ኤልሳቤጥ ከምድር ለሆኑት ወኪል ናቸውና።

     አንዳንዶች ከሴቶች መካከል ማለት “እንደሴቶች ሁሉ” ወይም “ከእነርሱ እንደ አንዱ” ማለት ነው። ከዚህ ውጭ “ ተለይታ” የሚል ሐረግ ባለመኖሩ ከአማኞች ጋር የምትቆጠር አንድ ተራ ግለሰብ ናት ብለዋል። ታድያ እንደሌሎች ሴቶች ከሆነች ሌሎች ሴቶች ይህን ብሥራት ለምን አንደ እርሷ አልተቀበሉም?

  ከሴቶች ተለይታ የመባረኳ ምስጢር:-

  • ሌሎች ሴቶቸ ቢወልዱ፣ ፃደቃን ሰማዕታትን ነው ፣እርሷ ግን የወለደችው የእነርሱን ጌታ ነው።
  • ሌሎች ድንግል ቢሆኑ እስከጊዜው ነው፣ኋላ ተፈትሆ/ድንግልናን ማጣት/አለባቸው። እርሷ ግን በጊዜው ሁሉ ድንግል ናት።
             በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንዲህ የሚል ጽሑፍ አለ:-“እነዚህ ሁሉ ከሴቶችና ከኢየሱስ እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው በፀሎት ይተጉ ነበር።” (ሐዋ 1፡14) ጸሐፊው ሐዋርያው ሉቃስ የኢየሱስ እናት እንደሌሎች ሴቶች ብትሆን “ ከሴቶች ጋር” ይል አልነበረምን? ከሴቶችተለይታ የተባረከች በመሆኗ ግን “ ከሴቶችና ከኢየሱስ እናት” ብሎ ለይቶ ፃፈ።

አርሷም ባየቸው ጊዜ ከንግግሩ በጣም ደነገጠቸና ይህ አንዴት ያለ ሠላምታ ነው ብላ አሰበች ድንጋጤ የህሊና ፤ ፍርሃት የልቦና፣ ረዓድ የጉልበት ነው። ድንግል ማርያም የደነገጠችው ከመልአኩ ንግግር የተነሳ በመሆኑ“ ከንግግሩ በጣም ደነገጠችና” የሚል ቃል እናነባለን። የተነገረን ቃል ሁሉ እንደወረደ መቀበል ከቶ መንፈሳዊነት አይደለም። ይልቁንም“ይገባኛል ወይ?”   ማለት ይገባናል። በደነገጡበት ሰዓት ማሰብ ከባድ ቢሆንም ድንግል ማረያም ግን “ ……ብላ አሰበች” ይላል። ድንጋጤ የህሊና ነዉና በህሊናዋ ጠየቀች ማለት ነዉ።  እንግዲያውስ ድንጋጤዋ ከእምነት ማነስ ሳይሆን “እንዴት ያለ ሰላምታ ነው?” ከሚል ጥልቅ መገረም ነው። የሚገባትን የክብር ሰላምታ ቆም ብላ ከመረመረችው፣ የማይገባቸውን ምስጋና  ሳይመረምሩ ለሚቀበሉ፣ በአሚና ዝማሬ በደብተራ ቅኔ ለሚኮፈሱ ይህ ተግሣጽ  ነው።!

 መልአኩም እንዲህ አላት፡- ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አግኝተሻልና አትፍሪ!

ፍርሃት አርቆ መናገር ለመልአክ አዲስ ባለመሆኑ ሲሆን ዋናው ግን ነደ እሳትን ብሩህ መለኮትን ትሸከሚያለሽና አትፍሪ ሲላት ነው።

እነሆም ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅም ትወልጂያለሽ፣ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ !

ጸንሳ ወንድ ልጅ መውለዷ ቀድሞም በትንቢት በሰፊው ተጠቁሟል። (ት.ኢሳ.7፡14) (ት.ኢሳ 9/6)። መልአኩ ግን የዚህ ወንድ ልጅ ስሙ ኢየሱስ መሆኑን ነገራት። ኢየሱስ ማለት “መድሃኒት” ማለት ነው። መድሃኒትነቱ ለ^ጢአትም፣ ለሞትም ነው! ይህን ስም ተሸክሞ ታምሞ  የማይታከም፣ ሞቶ የማይነሳ ማንም የለም!

   ኢየሱስ የሚለው ክቡር ስሙ
  •  ከስም ሁሉ በላይ የሆነ (ፊሊ 2፡10)
  • ከሰማይ በታች እንድንድንበት ዘንድ የተሠጠ ( ሐዋ4፡12)
  • ጉልበት ሁሉ የሚሰግድለት (ፊሊ 2፡10)
  • ምላስ ሁሉ የሚመሰክርለት (ፊሊ2፡11)
  • ተጠርቶ የሚለመን (ዮሐ14፡14)
  • የ^ጢአት ሥርየት የሆነ (ሐዋ2.38) (ሐዋ3፡16)
  •  ብዙ መከራ የሚጠራ (ማቴ 5፡11)
  • ዘወትር የምናጌጥበት (ራዕ7:5)
  • እንዲሁም የሚያጸድቀን ነው (ሮሜ 10፡13)
እርሱም ታላቅ ይሆናል! የልዑል ልጅ ይባላል።

አርሱም ታላቅ ይሆናል:- እርሱ ቀድሞም ታላቅ ነው! ተንቆ የነበረው የእኛን ማንነት ሲዋሐድ ያገኘነውን ክብር ለመግለጽ ግን ታላቅ ይሆናል አለ!
የልዑል ልጅ ይባላል:- እርሱ ቀድሞም የልዑል ልጅ ነው፣ እርሱ የሰው ልጅ ሲሆን፣እኛም የልዑል ልጆች መሆናቸንን አረጋገጠልን። እርሱ እኛ ጋር ሲሆን እኛም እርሱ ጋር ሆነናልና ከራሱ ጋር ይጠራናል!

ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋነ ይሰጠዋል!

 የዳዊትን ዙፋን የማይሻ ፣የእሳት ዙፋን ጥሎ የመጣ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል ማለት አብ ክርቶስን የዳዊትን ሥጋ ያዋሕደዋል ማለት ነው። ክርሰቶስ በዳዊት ሥጋ የዳዊት ልጅ ነውና። አብ በማዋሐድ ፣ ወልድ በመዋሐድ፣ መንፈስ ቅዱስ በማጽናት በድንግል ማርያም ረቂቅ ሥራ ተፈጽሟል። መዝ (88)
በያዕቆብ ቤትም ለዘለዓለም ይነግሳል

       ያዕቆብ አስራኤል ተብሏል (ዘፍ 32:22)። ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል
       ዘሥጋ ለጊዜው በትንቢት፣ በእስራኤል ዘነፍስ  (በክርስቲያኖች) ላይ ግን በፍቅር    
       ለዘለዓለም ነግሷል።
      ለመንግሰቱም መጨረሻ የለውም

ይህ ቃል አሰቀድሞ በነቢዩ በዳንኤል “በወገኖችና አሕዛብ ላይ ልዩ ቋንቋም  የሚናገሩ ሁሉ ይገዙለት ዘንድ ግዛትና ክብር መንግስትም ተሰጠው፣ ግዛቱም የማያልፍ የዘለዓለም ግዛት ነው። መንግስቱም የማይጠፋ ነው”። ተብሎ ተነግሯል (ት.ዳን 7፡13-14)

ማርያምም መልአኩን ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል? አለችው።

በአካልም በአሳብም ወንድ የማታውቅ መሆኗን የሚያሳይ የከበረ ቃል ነው።እኔ አንዱንም ሳላሰብ አንተ ብዙ ነገረ አልከኝ፣ ምድር ያለ ዘር፣ ሴት ያለወንድ ዘር እንዴት ይሆናል? አለችው “ እንዴት?” ስትል መልአኩ እንደካህኑ ዘካርያስ አልገሠፃትም! ምክንያቱም:-

    1ኛ. ካህኑ ዘካርያስ ካረጀሁ በኋላ እንዴት አወልዳለሁ? ቢል ካረጀ በኋላ የወለደ
      አባቱ አብርሃም ነበረና ማመን ይገባው ነበር። ድንግል ማርያም ግን
      በድንግልና ወልዶ የታየ ምሳሌ የሌላት ከመሆኑም ባሻገር ይህ ነገር
      ከመልአኩ ዕውቀት በላይ በመሆኑ ነው።
     2ኛ. መልአኩ በፊቱ ቆሞ  የሚያገለግለውን ጌታ እርሷ ወልዳው ያገለግላታልና በማዕረግ ጉዳይ ያከብራታል (ሉቃ 1፡19)  (ሉቃ2፡51)።

  “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፣ የልዑልም ^ይል ይጸልልሻል፣ ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፣ እነሆ ዘመድሽ ኤልሣቤጥ እርሷ  ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ጸንሣለች። ለእርስዋ መካን ትባል ለነበረችው ይህ ሰደስተኛ ወር ነው።”

የመልአኩ መልእክት ለኤልሣቤጥ ባለፈ ሠዓት፣ በስተርጅናዋ ለማሀፀኗ ልጅን የሰጠ አንቺንም በድንግልና ሳለሽ ለማህጸንሽ ልጅ ይሰጣል የሚል ነው። የቅ.ኤልሳቤጥ በስተርጅና የድንግል ማርያም በድንግልና የመውለድ ጸጋ የሆነው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና

     ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና:-

የመልአኩ ማሳረጊያ ቃል፣ ማሸነፊያ ብርታት የሆነው ይህ ቃል ነው። ሰው የሚቻለውን ይችላል። አግዚአብሔር የማይቻለውን ይችላል። ሰው እግዚአብሔር አሰችሎት ይችላል። እግዚአብሔር ግን ማንም ሳያስችለው ይችላል!
ማርያምም እነሆኝ የጌታ ባርያ እንደቃልህ ይሁንልኝ
የጌታ ባርያ ነኝ የሚል ፈቃዱን በእግዚአብሔር ፈቃድ የሚለውጥ ነው። እንደቃሌ ሳይሆን እንደቃልህ፣ እንደወሰድሁት ሳይሆን እንደሰጠኸኝ፣ እንደአሳቤ ሳይሆን እንደ ፈቃደህ፣ እኔ ላድርግ ሳይሆን ይሁንልኝ፣ እንደመሰለኝ ሳይሆን እንደወሰንከው፣ ስማኝ ሳይሆን ልስማህን የሚያስቀድም ነው!
                                                                                                                          ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Tuesday, May 8, 2012

ድንግል ማርያም በቅ/ገብርኤል ሠላምታ (ክፍል 1)=+= በመምህር ቃለአብ ካሳዬ=+=

በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩  አምላክ አሜን

  እንኳን ለእመቤታችን ለቅድስትድንግል ማርያም በዓለ ልደት በሠላም አደረሳችሁ!
     ድንግል ማርያም በቅ/ገብርኤል ሠላምታ(ክፍል 1)

በታሪክ ፍሰት ውስጥ ድንግል ማርያም ከቅዱስ ገብርኤል የተቀበለችውን ያህል ሠላምታ የከበረ ሠላምታ አይገኝም። መልአኩ ያቀረበላት ይህ ተወዳጅ ሠላምታ የዓለምን መዳን ዜና ያዘለ የአርሷንም የክብሯን መጠን ያሳየ ነበረ። የእመቤታችን የልደቷም ምሥጢር ፍቺ የጌታ መወለድ ነው።

ጌታ ቅድመዓለም ከአብ ለመወለዱ ጡት የምታጠባው ምድራዊት እናት፣ ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም ለመወለዱ ለዘር ምክንያት የሚሆን ምድራዊ አባት የለውም። ባለሁለት ልደቱ ጌታ ግን አንድ ነው። ባለበገናውም፡-
 “በአባትህ ስም ስንጠራህ
ወልደ ማርያም በላይ ነህ” በማለት ተቀኝቶለታል። ይህም የአብ የማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ የበላይ አስተዳዳሪ፣ ገ™ ነህ ማለት ነው።

ከዚህ ቀጥለን የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤል ቃለ ብሥራት ከጌታ ፍቅር ባሻገር ክብረ ማርያምንም ወለል ያደርግልናልና በጥቂቱ    እንዳስሰው!

  “በሰድስተኛውም ወር መልአኩ ገብርኤል ናዝሬት ወደምትባል ወደገሊላ ከተማ ከዳዊት ወገን ለሆነው ዮሴፍ ለሚባል ሰው ወደታጨች ወደ አንዲት ድንግል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ”ስድስተኛው ወር…. ይህ ወር ቅድስት ኤልሣቤጥ በስተርጅናዋ ዘመን ጸንሳ” ነቀፌታዬን ከሰው መካከል ያሰወግድልኝ ዘንድ ጌታ በተመለከተበት ወራት እንዲህ አድርጎልኛል” ስትል ራሷን ከሰወረችባቸው ከ5ቱ ወራቶች ቀጥሎ የሚመጣ ነው።

ናዝሬት ገሊላ… ናዝሬት በገሊላ አውራጃ ይገኙ ከነበሩ ከተሞች መካከል አንዷ የሆነች፣ ብዙ የማይጠበቅባትና የተናቀች ነበረች (ዬሐ1.47)ከዳዊት ወገን ለሆነው ለዮሴፍ ..ዮሴፍ በመልአኩ” የዳዊት ልጅ “ተብሎ ተጠርቷል(ማቴ 1÷20)። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በወንጌላዊው ማቴዎስ የትውልድ አቆጣጠር የዳዊት ልጅ የተባለው በአሳዳጊው በዮሴፍ በኩል  በተዘረዘረው ትውልድ ነው። (ማቴ.21÷9) (ማቴ. 12÷23) (ማር.10÷47)ወደታጨች… መታጨት፡- መታሰብ፣ መመደብ፣ መመረጥ ማለት ነው። 

የእመቤታችን ለዩሴፍ መታጨት ለጋብቻ ከመታጨት ወይም በእንግሊዘኛው betrothal ከሚባለው የተለየ ነው። የእመቤታችን መታጨት መመረጥን የሚወክል ነው። መጽሐፍ ቅዱስም መታጨትን “መመረጥ” እያለ በቀጥታ እንደሚተረጉም መረዳት እንችላለን (2ኛ ቆሮ 11÷2) (ሆሴ 2÷21)። የድንግል ማርያምና የዮሴፍንም ስንመለከት “እጮኝነቱ” መመረጥ በሚለው ትርጓሜ የሚነበብ እንጂ ሌላ መላምት የሚቀርብበት አይደለም። ቅዱስ ዮሴፍና እመቤታችን ለጋብቻ የማይሆን የዝምድና ትስስር፣ የእድሜ አለመመጣጠን የሚያግዳቸው ከመሆኑም ባሻገር እንዲህ የሚያስቡትን መጽሐፍ ቅዱስ “የተሰናከሉ” መሆናቸውን በግልጽ አማርኛ አስቀምጧል (ማር. 6÷3)። የኪንግ ጀምስ የእንግሊዘኛው መጽሐፍ ቅዱስም የሚመሰክረው ይህንኑ ነው። በአማርኛ “እጮኛ” የሚለውን እንግሊዘኛው” espouse” ብሎ ጠርቶታል። ይህም “አንድን ዓላማ ወይም አሳብ የሚደገፍን አካልን “ ያመለክታል። ለጋብቻ መታጨትን የሚመለክት ቢሆን ኖሮ የድንግል ማርያም ለዮሴፍ መታጨት “befrothed” ተብሎ ይጻፍ ነበር። /long man dictionary of  contemporary English 1987).

ወደ አንዲት ድንግል … ልዩ ድንግል በመሆን አንድ ናትና “አንዲት!” ብሎ ገለጻት። ሌሎች  በሥጋ ድንግል ይሆኑ ይሆናል። እርሷ ግን በሥጋም በኀሊናም ድንግል ናት “ርግቤ መደምደሚያዬ አንዲት ናት፣ ለወለደቻትም የተመረጠች ናት” (መኀመኀ.6÷9)። ጠቢቡ በትንቢት መንፈስ ሆኖ፡-ርግቤ አላት የየዋሕነቷን
መደምደሚያዬ አላት የሞትን ታሪክ የሚደመድመውን ትውልዳለችና ለወለደቻትም የተመረጠች ናት፡- የተወለደ ሁሉ ምርጥ አይደለም። ድንግል ማርያም ግን እንኳን ለወለደቻት ለወለደችውም የተመረጠች ናት።

ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ፡- ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከ የሚናገረው እውነት ነውና ::

የድንግሊቱም ስም ማርያም ነበረ፡- ማርያም ማለት ጸጋወሀብት ማለት ነው። ለጊዜው ለእናት ለአባቷ ልጅ ሆና ተሰጥታለች በፍጻሜው ግን የጸጋ እናት ሆና ለልጆቿ ሁሉ ተሰጥታለችና። መልአኩም ወደ እርሷ ገብቶ ደስ ይበልሽ፣ ጸጋን የሞላብሽ ሆይ፣ ጌታ ከአንቺ ጋር ነው፣

ደስ ይበልሽ…ይህንቃል የተናገራት ቅዱስ ገብርኤል ቢሆንም መልአክቱ የመጣው ግን ከሰማይ ነው። ጌታ ደስ ይበልሽ አላት። ደስ ይበልሽ ያላት በመጀመርያ ድኅነተ ዓለም ስለደረሠ ሲሆን ቀጥሎ ደግም እርሱን ለመውለድ ክብር በመመረጧ ነው። አንዳንዶች ግን ጌታን ደስ ያሰኙት እየመሰላቸው “ደስ ይበልሽ” ያላት እናቱን “ይሰድቡለታል”!

ጸጋን የሞላብሽ ሆይ

           ከቅዱስ ሕዝብ ወገን ጸጋ ያለው እንጂ ጸጋ የሞላበት የለም። አንድ ሁለት ጸጋ ይሞላበት ይሆናል፣ ጸጋ ሁሉ ግን አይሞላበትም። የጸጋ ስጦታ ልዮ ልዩ ነውና (1ቆሮ. 12÷4)። ድንግል ማርያም ግን “ ምልዕተ ጸጋ” የሚለው ማዕርጓ ጸጋ ሁሉ እንደሞላባት የሚያሳየን ነው። እንዴት በሉ?

    1ኛ- ጌታ ከነ ጸጋ ስጦታው ሁሉ ጋር  በማኀፀኗ በማደሩ ነው። ታዲያ አባቶች ” የጸጋ ግምጃ ቤት” ቢሏት ተሳስተው ይሆን?
    2ኛ- ፍጹሙ ጸጋ እርሱን  ጌታን መውለድ ነውና።
ጌታ ከአንቺ ጋር ነው

አንዳንዶች ጌታ በዮሐንስ ወንጌል ላይ..” አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? “ ብሏታል። ስለዚህ ማርያም ማርያም አትበሉ ሲሉ ብዙ ጊዜ ሰምተናል (ዮሐ. 2÷4)። አንድን ጹሑፍ ላልተጻፈበት ዓላማ ማዋል አለመታደል ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ዘይቤ “ከአንቺ ጋር ምን አለኝ” ማለት “ከአንቺ ጋር ምን ጠብ አለኝ?” ማለት እንደሆነ ግልጽ ቢሆንም መልአኩ ግን በቀጥተኛ መልዕክት “ጌታ ከአንቺ ጋር ነው”ይላታል። “ጌታ ከአንቺ ጋር ነው” የሚለው የእግዚአብሔር መልእክተኛ ከሆነ “ጌታ ከእርሷ ጋር ምን አለው?” የሚለውስ የማን መልእክተኛ ነው ትላላችሁ? ተወዳጆች ሆይ፡- ጌታ ከእርሷ ጋር ባይሆን ዛሬ እኛ ከእርሱ ጋር አንሆንም ነበር፣ የእርቃችን ሰነድ፣ የአብሮነታችን ምስጢር፣ የመገናኛ ድንኳናችን ናት። አማኑኤል ትርጓሜውም “እግዚአብሔር ከእኛ ጋር” የተባለው ከእርሷ ሰው ሆኖ አይደለምን? (ማቴ.1÷23)። ፍቅርን እየወደደ የፍቅርን ሀገር የሚጠላ ማነው? ፍቅር ጌታን እየወደደ ሀገረ ፍቅር ድንግል ማርያምንስ የሚጠላ ማነው? እርሱ ይመለካል፣ እርሷን ብጽዕት እንላለን! እርሱ ታላቅ ገናና ነው፣ እርሷ ታላቅ ሥራ ተደርጎባታል (ሉቃ.1÷49)።  እርሱ አምላክ ነው፣ እርሷ እናቱ ናት። የልባችን መሻት እንዲሞላ እርሱ ከእርሷ  ጋር እንደሆነ እርሷም ከእርሱ ጋር ናት።

 ሴትየዋ በዕድሜ የገፉ ናቸው፣ አንዱ በመንገድ አስቁሞ “ቃል ላካፍልዎት” ይላቸዋል። እርሳቸውም “ተወኝ ባክህ ልጄ ልደትዬን ተሣልሜ እየተመለስሁ እንደመሆኔ ደክሞኛል” ይሉታል፣ እርሱም “ ማናት ደግሞ ልደትዬ” ? ይላቸዋል፣ “ድንግል ማርያም ናት“ይሉታል። እርሱም “ጌታ እኮ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ!“ ብሏታል ሲል ደንግጠው “ እናቱን?” አሉ “አዎ”! አላቸው። እርሳቸውም “ለእናቱ ያልሆነ ለእኔ ይሆናል ብለህ ነው” ብለው እንደቆመ ጥለውት ሄዱ። እባካችሁ ለእናቱ የማይሆን ኢየሱስ እኛ ቤት የለም!

   ወሰብሐት ለእግዚአብሔር

በቅ/ገብርኤል ሠላምታ (ክፍል ሁለት)
የዮሐንስ ወንጌል የ10ኛ ሳምንት ጥናት
የዮሐንስ ወንጌል የ11ኛ ሳምንት ጥናት

FeedBurner FeedCount