Showing posts with label ፕሮቴስታንት ለጠየቀኝ የተለያዩ ጥያቄዎች. Show all posts
Showing posts with label ፕሮቴስታንት ለጠየቀኝ የተለያዩ ጥያቄዎች. Show all posts

Sunday, May 27, 2012

አንድ ፕሮቴስታንት ለጠየቀኝ የተለያዩ ጥያቄዎች በጽሑፍ የሰጠሁት ምላሽ

        በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!  

   1. “በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ፥ ጠላቶቹም አፈር ይልሳሉ። የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የዓረብና የሳባ ነገሥታት እጅ መንሻን ያቀርባሉ።”  እና “የግመሎች ብዛት፥ የምድያምና የጌፌር ግመሎች፥ ይሸፍኑሻል፤ ሁሉ ከሳባ ይመጣሉ፥ ወርቅንና ዕጣንን ያመጣሉ የእግዚአብሔርንም ምስጋና ያወራሉ።” ተብሎ በነብያቱ የተነገረውን ትንቢት በቀጥታ “ወደ ቤትም ገብተው ሕፃኑን ከእናቱ ከማርያም ጋር አዩት፥ ወድቀውም ሰገዱለት፥ ሣጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን ከርቤም አቀረቡለት።” ተብሎ ሲፈጸም ስለምንመለከተው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ. ጌታ ሲወለድ በቤተልሔም ተመሠረተች ቢባል ያስኬዳል /መዝ.71፡9-10፣ ኢሳ.60፡6፣ ማቴ.2፡1-11/፡፡ በኋላ ደግሞ የሐዋርያት ሥራ ጸሐፊ እንደሚነግረን፡- “የጌታም መልአክ ፊልጶስን። ተነሥተህ በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ ወደሚያወርደው ምድረ በዳ ወደ ሆነ መንገድ ሂድ አለው።ተነሥቶም ሄደ። እነሆም፥ ህንደኬ የተባለች የኢትዮጵያ ንግሥት አዛዥና ጃንደረባ የነበረ በገንዘብዋም ሁሉ የሠለጠነ አንድ የኢትዮጵያ ሰው ሊሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር፤ሲመለስም በሰረገላ ተቀምጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ያነብ ነበር። መንፈስም ፊልጶስን። ወደዚህ ሰረገላ ቅረብና ተገናኝ አለው። ፊልጶስም ሮጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ሲያነብ ሰማና። በውኑ የምታነበውን ታስተውለዋለህን? አለው። እርሱም። የሚመራኝ ሳይኖር ይህ እንዴት ይቻለኛል? አለው። ወጥቶም ከእርሱ ጋር ይቀመጥ ዘንድ ፊልጶስን ለመነው።ያነበውም የነበረ የመጽሐፉ ክፍል ይህ ነበረ፤ እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፥ የበግ ጠቦትም በሸላቹ ፊት ዝም እንደሚል፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። በውርደቱ ፍርዱ ተወገደ፤ ሕይወቱ ከምድር ተወግዳለችና ትውልዱንስ ማን ይናገራል?  ጃንደረባውም ለፊልጶስ መልሶ። እባክህ፥ ነቢዩ ይህን ስለ ማን ይናገራል? ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ? አለው። ፊልጶስም አፉን ከፈተ፥ ከዚህም መጽሐፍ ጀምሮ ስለ ኢየሱስ ወንጌልን ሰበከለት። በመንገድም ሲሄዱ ወደ ውኃ ደረሱ፤ ጃንደረባውም። እነሆ ውኃ፤ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምንድር ነው? አለው። ፊልጶስም። በፍጹም ልብህ ብታምን፥ ተፈቅዶአል አለው። መልሶም። ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ አምናለሁ አለ። ሰረገላውም ይቆም ዘንድ አዘዘ፥ ፊልጶስና ጃንደረባው ሁለቱም ወደ ውኃ ወረዱ፥ አጠመቀውም። ከውኃውም ከወጡ በኋላ የጌታ መንፈስ ፊልጶስን ነጠቀው፤ ጃንደረባውም ሁለተኛ አላየውም፥ ደስ ብሎት መንገዱን ይሄድ ነበርና።” ይለናል /ሐዋ.8፡26-39/፡፡ ይህም የሆነው በ34 ዓ.ም. ነው፡፡ በይፋ በጳጳስ መመራት የጀመረችው ግን በ330 ዓ.ም. በአባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን አማካኝነት ነው፡፡
  • “ኦርቶዶክስ” የሚለው ቃል “ኦርቶዶክስያ” ከሚለው የግሪክ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ቀጥተኛ (እምነት) ማለት ነው፡፡ የምስራቅና የኦሬንታል አብያተ ክርስቲያናትም ይጠሩበታል፡፡
  • “ተዋሕዶ” የሚለው ቃል በግሪኩ “Miaphysis” የሚለውን ቃል የሚተካ የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ክርስቶስ ሰው የሆነ አምላክ መሆኑን /ዮሐ.1፡1፣14/፣ መለኰትና ትስብእትም ያለ መለያየት፣ ያለ መቀላቀል፣ ያለ መለያየት ስለ ተዋሐዱ አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ ፈቃድ፣ አንድ ግብር መሆኑን የሚገልጽ ነው፡፡
     

FeedBurner FeedCount