Showing posts with label “እስክመጣ ድረስ በማንበብ ተጠንቀቅ” (1ኛ ጢሞ.4፡13)፡፡. Show all posts
Showing posts with label “እስክመጣ ድረስ በማንበብ ተጠንቀቅ” (1ኛ ጢሞ.4፡13)፡፡. Show all posts

Thursday, August 17, 2017

“እስክመጣ ድረስ በማንበብ ተጠንቀቅ” (1ኛ ጢሞ.4፡13)፡፡



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ 11 ቀን 2009 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
እንደ መንደርደሪያ
ኃይለ ቃሉን የተናገረው በመንፈሳዊው ትምህርት ከሕግ መምህሩ ከገማልያል፣ በዚህ ዓለም ትምህርት ደግሞ በዘመኑ እጅግ ታዋቂ ከነበረው የተርሴስ ዩኒቨርሲቲ በእጅግ ከፍተኛ ማዕረግ የተመረቀው ንዑድ ክቡር የሚኾን ጳውሎስ ነው፡፡ የተናገረው ደግሞ በመንፈስ ለወለደው ልጁ ለሊቀ ጳጳሱ ለቅዱስ ጢሞቴዎስ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለቅዱስ ጢሞቴዎስ፡- “እስክመጣ ድረስ በማንበብ ተጠንቀቅ፤ በማንበብ ተወስነህ ኑር” በማለት መንፈሳውያን መጻሕፍትን እንዲያነብ ሲመክረውም ምክንያቱን ነግሮታል፤ እንዲህ ሲል፡- “ይህን ብታደርግ ራስህንም የሚሰሙህንም ታድናለህ” (1ኛ ጢሞ.4፡16)፡፡
ስለዚህ መንፈሳዊ ንባብ ማለት ራሳችንንም የሚሰሙንንም ለማዳን - አስተውሉ! ለማዳን - መጽሐፍ ቅዱስን ጨምሮ የአበው ድርሳናትን፣ ትርጓሜያትን፣ ምክሮችን፣ ገድሎችን፣ ታሪኮችን ማንበብ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የማንበብ ግቡ እኛ ራሳችን እግዚአብሔርን ወደ መምሰል እንድናድግ ሌሎችንም ወደዚህ ምንድግና እንዲመጡ ማድረግ ነው ማለት ነው፡፡ ንባብ ብቻ ሳይኾን የማንኛውም መንፈሳዊ ግብር ዓላማም ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትና አንድነት መፍጠር ነው፡፡
ከላይ ባነሣነው የቅዱስ ጳውሎስ ቃል እንደምንመለከተው አንድ ኦርቶዶክሳዊ ኹልጊዜ በመደበኛነት ሊያነብ እንደሚገባው ያስረዳል፡፡ ጢሞቴዎስ ጳጳስ ነው፡፡ ቢኾንም ግን ማንበብ - ያውም ኹልጊዜ - መጻሕፍትን መመልከት እንዳለበት ተመከረ! ቅዱስ ጢሞቴዎስ ከሴት አያቱና ከእናቱ ከልጅነቱ አንሥቶ ቅዱሳት መጻሕፍትን ሲያነብ ያደገ ነው (2ኛ ጢሞ.3፡14-15)፡፡ አሁንም ቅዱስ ጳውሎስ ተቀብሎ ይበቃሃል ሳይኾን “በማንበብ ተጠንቀቅ” አለው፡፡

FeedBurner FeedCount