Monday, May 21, 2012

=+=ከሳምራይቱ ሴት ጋር የተደረገ ንግግር- የዮሐንስ ወንጌል የ19ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡7-15)=+=

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 ጌታ ለተገፉት ምርኩዛቸው ለተጨነቁትም ዕረፍት ነው፡፡ አዎ! ሳምራይቱ ሴት በጧት ውኃ ልትቀዳ አለመምጣቷ መለኰታዊ ዕቅድ ከመሆኑ በተጨማሪ ውኃ የሚቀዱት ሴቶች በእርሷ ላይ የሚሳድሩት ተጽዕኖ እንዳለ ያመለክታል፡፡ ስለዚህ አዋልደ ሰማርያ በማታገኝበት ሰዓት ብቻዋን “ውኃ ልትቀዳ መጣች” /ቁ.7/። ይገርማል! ርብቃ ከይስሐቅ፣ ራሄል ከያዕቆብ እንዲሁም የካህኑ የዮቶር ልጅ ከሙሴ ጋር የተገናኙት በውኃ ጉድጓድ ነበር፡፡ ይህች ሳምራይቱ ሴትም ከነፍሷ እጮኛ ከክርስቶስ ጋር የምትገናኘው በያዕቆብ ጕድጓድ ነው፡፡ በዚሁ ሰዓት ነው እንግዲህ ደቀ መዛሙርቱ ምግብ ሊገዙ ወደ ከተማ በሄዱ ጊዜ ውኃን በደመና እየቋጠረ ምድርን የሚያረሰርሳት ጌታ  እንደ ምስኪን “ውኃ አጠጪኝ” የሚላት  /ቁ.8/። እንዴት ያለ ግሩም ንግግር፣ እንዴት ያለ ታላቅ ምሥጢርን የያዘ ቃል ነው? ምክንያቱም የሴትዮዋን መሻት ይመለከት ዘንድ ውኃ አጠጪኝ ይላታልና፡፡ በእርግጥም ጌታችን ውኃ ተጠምቶ ነበር፡፡ የእምነት ውኃ! የሰው ልጆች የመዳን ውኃ! ስለዚህም “አንቺ ሴት! እምነትሽን ተጠምቻለሁ፤ መዳንሽን ተርቤአለሁ” ይላታል /ቁ.34፣ አውግስጢኖስ- Sermon On New Testamen Lessons, 49:3/፡፡
 ሳማራይቱ ሴትም ጌታን በአለባበሱ አንድም በንግግሩ ብታውቀው “አንተ አይሁዳዊ እኔም ሳምራዊት ስሆን እንዴት ውኃ አጠጭኝ ብለህ ትለምናለህ? አይሁድ ከሳምራውያን ጋር በሥርዓት እንደማይተባበሩ አታውቅምን?” ትሏለች /ቁ.9/። ሴቲቱ ይህን የምትለው በቅንነት  እንጂ በክፋት አልነበረም! “እኛ ሳምራውያን ከእናንተ ከአይሁድ ጋር መነጋገር አንችልም” ሳይሆን በመገረም “አንተ አይሁዳዊ ስትሆን እኔም ሳምራዊት ስሆን እንዴት ያንን የጥል ግድግዳን አፍርሰህ በፍቅር ልታነጋግረኝ ቻልክ?” ትሏለች /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ-Homilies On St. John,31:4/፡፡
 የፍቅር ጌታም የሴትዮዋን ልብ በሳምራውያንና በአይሁድ መካከል ካለው መለያየት ይልቅ ስለ ማየ ሕይወት እንድታሰላስል ያደርጋታል፡፡ ስለዚህም፡- “የእግዚአብሔርን ስጦታና ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር” ይላታል /ቁ.10/።  እንዲህ ማለቱም ነበር፡-“ልጄ! አሁን ስለዚያ መለያየትና ጥል ሚነገርበት ሰዓት አብቅቷል፡፡ የሚያነጋገረሽ አምላክ ወልደ አምላክ፣ የሰው ልጆች ተስፋ፣ ኃይሉ ለአብ ወጸጋ ዘአሕዛብ እርሱ መሆኑን ብታውቂ ሁለመናሽን ከኃጢአት እድፍ ትርቂበት ዘንድ አንቺው ራስሽ እንደ መዝሙረኛው ዳዊት “ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ አቤቱ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች” እያልሽ በለመንሽው ነበር” ይላታል /መዝ.42፡1፣ St.Ambros-Of The Holy Spirit,1:16;175/፡፡
 ሴቲቱም እንደ ግራ መጋባትም እንደ መደነቅም ብላ፡- “ጌታ ሆይ! ቀድተህ ታጠጣኛለህ እንዳልል መቅጃ የለህም ጕድጓዱም ጥልቅ ነው፤ ከያዝከው ውኃ ታጠጣኛለህ እንዳልልም በእጅህ መንቀል አልያዝክም፤ እንግዲህ የሕይወት ውኃ ከወዴት ታገኛለህ?” ትሏለች/ቁ.11/፡፡ አስቀድመን እንዳልነው የሴትዮዋ ንግግር እንደ አይሁድ በተንኰል የተለወሰ አልነበረም፡፡ ለዚህም ነው አሁንም በአክብሮት “ጌታ ሆይ!” ስትለው የምናስተውለው፡፡ እንዴት ያለች ልበ ንጹሕ ሴት ነች? ቅንነቷ ምሁረ ኦሪት ከተባለው ከኒቆዲሞስ በላይ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ምንም ምሁረ ኦሪት ቢሆንም አንዳንድ የሚተገብራቸው ነገር ግን ምን ማለት እንደሆኑ የማያስተውላቸው ነገሮች ነበሩ (ለምሳሌ፡- የማንጻት ውኃ እንዴት ያነጻ እንደ ነበር አያውቅም)፡፡ ይህች ሴት ግን “አባታችን ያዕቆብ እና ልጆቹ ከብቶቹም ውኃ የጠጡት ከዚህ ጕድጓድ ነው፡፡ ሌላ የተሻለ የውኃ ጕድጓድ ቢኖራቸው ኖሮ ሁሉም ከዚህ ጕድጓድ ብቻ ባልቀዱ ነበር፡፡ አንተ ግን ሌላ ከዚህ የተሻለ ውኃ እሰጥሻለሁ እያልከኝ ነው፡፡ እንግዲህ ከአባታችን ከያዕቆብ ካልበለጥክ በስተቀር ሌላ የተሻለ ውኃ እንዴት መስጠት ይቻልሃል?” ትሏለች፡፡ ንግግሯ ከቅንነት የመነጨ መሆኑን የበለጠ የምናውቀው ደግሞ ጌታችን እንዲህ ሲላት፡- “ሌላ የተሻለ ውኃ ካለህ እንዴት መጀመርያ አንተው ራስህ አትጠጣም” ማለት ትችል ነበር፡፡ የዋሕነቷ ግን እንዲህ እንድትል አልፈቀደላትም /ቁ.12, St.John Chrysostom,Ibid/፡፡
 ጌታችን ይቀጥላል፡፡ ሴትዮዋ እርሱ ወደሚፈልገው አቅጣጫ እየመጣች ነው፡፡ ስለሆነም በአንድ ጊዜ “አዎ! አንቺ እንዳልሽው እኔ ከያዕቆብ እበልጣለሁ” አይላትም፡፡ ከዚሁ ይልቅ ጥበብ በተመላበት ንግግር፡- “ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ሁሉ እንደ ገና ይጠማል፤ እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈስ የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል እንጂ ለዘላለም አይጠማም” ይላታል /ቁ.13-14/። በዚህ ንግግሩ በያዕቆብ ውኃና እርሱ በሚሰጠው የሕይወት ውኃ ያለው ልዩነት ቀስ አድርጎ እየነገራት ነበር፡፡ “በእኔ የሚያምን ሁል ጊዜ ከቶ አይጠማም፤ ጽምዓ ነፍስ አያገኘውም” እንዲል /ዮሐ.6፡35/፡፡  እንዲህ ሲላትም እኔ ያስተማርኩትን ትምህርት እኔ በጥምቀት የሰጠሁትን ልጅነት የተቀበለ ሁሉ ዳግመኛ በነፍሱ አይጠማም ማለቱ ነበር፡፡ እውነት ነው! ይህ ማየ ሕይወት በደስታ የሚጠጡት መለኰታዊ ውኃ ነው፤ ይህ ውኃ ዳግመኛ የሚያስጠማ ውኃ አይደለም፤ ይህን ውኃ የሚጠጣ መጽሐፍ እንደሚል ዳግመኛ አይጠማም፤ ይህ ውኃ እንስራውን ካልሰበረ (ሰውነቱን በኃጢአት ባላቆሸሸ) ሰው ጋር ለዘላለም ይኖራል /ኢሳ.12፡3፣ዮሐ.7፡38፣ ቅ.አምብሮስ, On the Holy Spirit 1:16:181-182/፡፡
 ዕጹብ ድንቅ ነው! ሴቲቱ በዚሁ የጌታ ንግግር ይህ ጥምን የሚቆርጥ የሕይወት ውኃ ትጠጣ ዘንድ ጎመጀች፤ ስትመካበት የነበረው የአባቶቿ ጕድጓድም ናቀችውና፡-“ጌታ ሆይ! እንዳልጠማ ውኃም ልቀዳ ወደዚህ እንዳልመጣ ይህን ውኃ ስጠኝ” ትላለች /ቁ.15/።  አስቀድሞ “ትለምኝኝ ነበር” ብሏት ነበር፤ ያላት አልቀረ ይሄው ተፈጸመ፡፡ አሁን የሴትዮዋን ሁናቴ በጽሞና አስታውሱ! ሰማያዊውን ውኃ ስትጐነጭ፤ እንስራዋን ስትጥለው፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ስለ ያዕቆብ ጕድጓድም ትዝ አይላትም፡፡ እንስራዋ የት እንደጣለቸው ትዝ አይላትም፡፡ ተወዳጆች! እምነቷ እንዴት እያደገ እንደሄደ ልብ በሉ፡፡ አስቀድማ ጌታዋን “አይሁዳዊ!” አለችው /ቁ.9/፤ ቀጥላ “ጌታ ሆይ!” አለችው /ቁ.11/፤ ትንሽ ቆይታም ከያዕቆብ እንደሚበልጥ አስተዋለች /ቁ.12/፤ አሁን ደግሞ የሕይወት ውኃ ምንጭ እርሱ መሆኑን ተገነዘበች /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ዝኒከማሁ/፡፡
ወዮ! አባት ሆይ የሳምራይቱን ሴት እንስራ ያስጣለ ፍቅርህ እንዴት ብርቱ ነው?! ጌታ ሆይ! ከደሀይቱና ከተጨነቀችው ሳምራይቱ ሴት ጋር የተነጋገረ ትሕትናህ እንዴት ግሩም ነው?! አባት ሆይ! ዛሬም ነፍሳችን እንደ ዋልያ አንተን ተጠምታለችና የሰጠኸንን ማየ ሕይወት (ክቡር ደምህ) በአግባቡ እንጠጣው ዘንድ እርዳን! በኃጢአታችን ምክንያት እንደ ሳምራይቱ ሴት ያፈርን ብዙዎች ነንና በቸርነትህ ተቀበለን! ከወራጅ ውኃ ጋር የምንታገል ብዙዎች ነንና ከማየ ገነት ታጠጣን ዘንድ እንማጸናሃለን! ፍቅርህ፣ ጥበብህ፣ ትሕትናህ ሳምራይቱን ሴት እንዳንበረከካት እኛንም ያቅፈን ዘንድ ፈቃድህ ይሁን! ሳምራይቱ ሴት ቀስ በቀስ እምነቷ እየጨመረ እንደሄደ እኛም በእምነትና በምግባር እንድናድግ ክንድህ ትርዳን አሜን ለይኩን ለይኩን!

በእንተ ሐዊሮቱ ገሊላ- የዮሐንስ ወንጌል የ18ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡1-6)!!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ሳምንት እንደተነጋገርነው ብዙ ሰዎች ዮሐንስን ትተው ወደ ክርስቶስና ወደ ደቀመዛሙርቱ ይሄዱ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት  ማለትም ከአርድእተ ዮሐንስ ይልቅ አርድእተ ክርስቶስ አብዝተው እንዳጠመቁ አይተው ፈሪሳውያን ቅንዓት ይዞዋቸዋል፡፡ ጌታችንም ፈሪሳውያኑ ይህን ሰምተው እንዳዘኑ “ባወቀ ጊዜ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ ደግሞ ሄደ” /ቁ.1-2/፡፡ ከእናንተ መካከል “ጌታችን ለምን እንዲህ አደረገ?” የሚል ቢኖር እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- ጌታችን እንዲህ ያደረገው ፈሪሳውያኑን ፈርቶ ሳይሆን የፈሪሳውያኑ ቅናትና ክፋት መልሶ እነርሱን እንደሚጎዳቸው ስለሚያውቅ ነው፡፡ ምክንያቱም ክፉ አድራጊ ራሱን እንጂ ማንንም ሊጎዳ አይችልምና፡፡ ፈሪሳውያን እርሱን ለመጉዳት ሲመጡ ከእነርሱ በላይ ሊጎዳቸው ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን በባሕሪይው ፍቅር የሆነው ጌታችን አንድ ቀንስ እንኳ እንዲህ አድርጎ አያውቅም፡፡ ስለዚህም ነገር ሁሉ እንደ እነርሱ ደካማነት ያደርግላቸው ነበር(ለምሳሌ፡- በእነርሱ እይታ ጌታ ፈርቷቸው ሄዷል- ሎቱ ስብሐት)፡፡
የሚገርመው ደግሞ “ደቀ መዛሙርቱ እንጂ ኢየሱስ ራሱ አላጠመቀም” /ቁ.3/። ይህም ማለት የተደረገው ሁሉ ስለ እነዚህ ደካማ ሰዎች የተደረገ ነበር፡፡ የሚደረገው ሁሉ ስለ እነርሱ ጥቅም ይደረግ ነበር፡፡ ሆኖም ግን እነርሱ የባሰ በቅናት ይሰክሩ ነበር፡፡ ጌታ የእነዚህ ቅናተኞች እጅና እግራቸውን አስሮ በይሁዳ መቆየት ቢፈልግ መቆየት ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን የሰውን ነጻ ፈቃድ የሚጋፋ አምላክ አይደለም፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አንድ አገልጋይ አሳዳጆቹ ሲበዙ መሸሽ ኃጢአት እንዳልሆነ ለማስተማር ማለትም ፈርቶ ሳይሆን እንደ መልካም አስተማሪ “ሰው የሚጠላባችሁን ሥራ አትሥሩ” ብሎ ለአርአያነት ሀገራቸውን ለቆ ወደ ገሊላ ሄደ /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ፣ Homoly on the Gospel of John, Hom.31:1/፡፡
 አስቀድሞ (ምዕ.3፡26) “እርሱ ያጠምቃል” ተብሎ አሁን ደግሞ “እርሱ አላጠመቀም” ስለተባለ የሚጋጭ ሐሳብ ሊመስላችሁ ይችላል፡፡ ነገር ግን የሚጋጭ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ጌታ በግዙፉና በሚዳሰሰው እጁ አላጠመቀም፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ግን ያጠምቁ ነበር፡፡ ይህም ማለት በእነርሱ አድሮ ያጠምቅ ነበር ማለት ነው፡፡ መጥምቁስ “እርሱ…ያጠምቃችኋል” ብሎ የለ /ማቴ.3፡11/? አሁንስ መቼ ማጥመቅ አቁሞ ያውቃል? በካህኑ እጅ የሚያጠምቅ እርሱ አይደለምን?
 ስለዚህ ደቀ መዛሙርቱ ያጠምቁ ነበር፡፡ በዚሁ መሠረት ይሁዳም ያጠምቅ ነበር ማለት ነው፡፡ ልትደነቁ ትችላላችሁ!! ይሁዳ ያጠመቀው ዳግመኛ አልተጠመቀም፡፡ ዮሐንስ መጥምቅ ያጠመቀው ግን ዳግመኛ ይጠመቅ ነበር፡፡ ይሁዳ ሲያጠምቅ ጥምቀቱ የክርስቶስ ነበር፤ ዮሐንስ ሲያጠምቅ ግን ጥምቀቱ የዮሐንስ ብቻ ነበር፡፡ ምንም እንኳን ከይሁዳ ይልቅ ዮሐንስ ጻድቅ ቢሆንም ከዮሐንስ ጥምቀት ግን የይሁዳ ጥምቀት ትበልጣለች /አውግስጢኖስ፣ Tractes on the Gospel of John, 15:2-3/፡፡
 ከዚህ በኋላ ጌታችን ወደ ገሊላ ለመሄድ “በሰማርያ በኵል ያልፍ ዘንድ ግድ ሆነበት” /ቁ.4/።  ይህች ሰማርያ በይሁዳና በገሊላ መካከል የምትገኝ ግዛት ናት፡፡ ስለዚህ በዚህች ግዛት ሳይረገጡ መሄድ አይቻለም ነበር፡፡ እነዚህ ሳምራውያን ጥንተ ነገዳቸው አይሁዳውያን ሲሆኑ ሀገራቸው በአሦር ነገሥታት በስልምናሶርና ሳርጎን ስትያዝ ከአሕዛብ ከመጡ ሰዎች ጋር ተደባለቁ /2ነገ.17፡24-33/፡፡ መደባለቅ ብቻ ሳይሆን ከእነርሱ ጋር ተጋቡ፤ ጣዖታቸውን አምለኩ፡፡ እግዚአብሔርን ስላልፈሩም የአንበሳ መዓት ተሰዶባቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ከዚህ ተመልሰው እግዚአብሔርን ማምለክ ፈለጉ፡፡ ካህን ተልኮላቸውም የሙሴ መጻሕፍትን እንዲያውቁ ተገደረጉ፡፡ አይሁድ ከባቢሎን ምርኮ ሲመለሱ ከእነርሱ ጋር ቤተ መቅደስን መሥራት ቢፈልጉም በበዘሩባቤልና በነህምያ ተቀባይነት ስላላገኙ በገሪዛን ተራራ ለራሳቸው ቤተ መቅደስ ሠሩ፡፡ “ማንበብ ያለብን አምስቱ የሙሴ መጻሕፍት ብቻ ነው፤ እግዚአብሔርን የምናመልከው በኢየሩሳሌም ሳይሆን በገሪዛን ተራራ ነው፤ የእግዚአብሔር ማደርያም ጽዮን ሳትሆን ሴኬም ናት” አሉ፡፡
 ጊዜው ሲደርስ ግን ጌታችን የሕይወትን ዘር ይዘራባቸው ዘንድ ወደ ሀገራቸው መጣ፡፡ ጌታችን መጥቶ ዘሩን የዘራባት ቦታም ሴኬም (ሲካር) ትባላለች፡፡ ወንጌላዊው፡- “ስለዚህ ያዕቆብ ለልጁ ለዮሴፍ በሰጠው ስፍራ አጠገብ ወደምትሆን ሲካር ወደምትባል የሰማርያ ከተማ መጣ” እንዲል /ቁ.5/፡፡ የቦታው ስም ያለ ምክንያት የተጠቀሰ አይደለም፡፡ እነዚህ የሰማርያ ሰዎች፡- “እኛ የተለየንና የተከበርን ሰዎች ነን፤ እንደ አይሁድ የማንንም ነብይ ደም አላፈሰስንም፡፡ ስለዚህ የአብረሃም ልጆች ነን፤ የልጁም የያዕቆብ ልጆች መባል የሚገባንም እነርሱ ሳይሆኑ እኛው ነን” እያሉ ይመኩ ነበር፡፡ ጌታችንም ይህን ትምክሕታቸው ስለሚያውቅ የያዕቆብ ልጆች የሆኑት ሌዊና ስምዖን በእኅታቸው በዲና ምክንያት የሴኬም ሰዎችን ወደ ገደሉባት ሀገር መጣ፤ የሚያስመካ ነገር እንደሌላቸውም በዘዴ አስተማራቸው፤ እነርሱም ደም እንዳፈሰሱ በጥበብ ነገራቸው /ዘፍ.34፣ ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡
 “በዚያም የያዕቆብ ጕድጓድ ነበረ። ኢየሱስም መንገድ ከመሄድ ደክሞ በጕድጓድ አጠገብ እንዲህ ተቀመጠ፤ ጊዜውም ስድስት ሰዓት ያህል ነበረ” /ቁ.6/።  የሚገርም ነው! ጌታችን በዚሁ ጕድጓድ የሚያገኛት ሳምራይቱ ሴት በጧት ውኃ መቅዳት ትችል ነበር፡፡ ነገር ግን የእርሷ አመጣጥ መለኰታዊ ዕቅድ አለበትና አንድም ሴትዮዋ ለመሲሑ የሚምበረከክ ልብ አላትና አንድም ይህች ሴት ከያዕቆብ የጕድጓድ ውኃ ይልቅ የማይነጥፍ የውኃ ምንጭ የምትሻ ናትና በተዋሐደው ሥጋ ደክሞ የሚመጣውን ጌታ ትገናኝ ዘንድ እስከዚሁ ሰዓት ሳትወጣ ቆየች፡፡
ወዮ! ስንደክም የሚያበረታን እርሱ ደከመው፡፡ የሕይወት ውኃ ምንጭ እርሱ ውኃ አጠጭኝ አላት፡፡ ከባሕርዪው የሕይወትን ውኃ የሚያጠጣ እርሱ ከወራጁ ውኃ አጠጭኝ አላት፡፡ እንዴት ዕጹብ ነው? የአምላክ ትሕትና እንዴት ያለ ነው? /ቅ.አምብሮስ፣ Of the Holy Spirit 1:16:184-85/፡፡
ውኃ አጠጪኝ አላት አፍላጋት የሠራው፤
እንደተቸገረ ውኃ እንደጠማው ሰው፡፡
     አይሁዳዊ አለችው አወይ አለማወቅ፤
    ሰማያዊው አምላክ ‘ራሱን ቢደብቅ፡፡ (ዘማሪ ይልማ ኃይሉ)!!

ዳግመ ስምዑ ለዮሐንስ- የዮሐንስ ወንጌል የ17ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.3፡22-ፍጻሜ)!!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!
 ጌታችን አስቀድሞ የአይሁድ ፋሲካ ሲሆን ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፡፡ የሄደበትም ምክንያት ለበዓሉ የመጡትን ሰዎች ገቢረ ተአምራቱን አይተው አንድም ትምህርቱን ሰምተው እንዲያምኑ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ከዮሐንስ ለመጠመቅ ወደ ተሰበሰቡት ሰዎች ወደ ፈለገ ዮርዳኖስ ይሄዳል፡፡ አካሄዱም በዚያ የነበሩት ሰዎች ስለ ወንጌለ መንግሥት ሊሰበክላቸው ይገባ ስለ ነበር ነው፡፡ ስለዚህም ወንጌላዊው፡- “ከዚህ በኋላ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ ይሁዳ አገር መጣ፥ በዚያም ከእነርሱ ጋር ተቀምጦ ያጠምቅ ነበር” ይለናል /ቁ.22፣ /። “ያጠምቅ ነበር” ሲባልም በደቀመዛሙርቱ አድሮ ያጠምቅ ነበር ማለት ነው፤ እርሱ ራሱ ግን አላጠመቀምና /ዮሐ.4፡2/፡፡ “ለምንስ አላጠመቀም?” ቢሉ መጥምቁ እንደተናገረው ጌታችን የሚያጠምቀው በእሳትና በመንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ገና አልወረደም ነበር /ዮሐ.7፡39/፡፡ “ለምንስ ደቀ መዛሙርቱ አጠመቁ?” ቢሉ ደግሞ ሕዝቡ ከዮሐንስ ይልቅ ወደ ሐዋርያት ይመጡ ይገባልና፡፡ “ለምንስ ዮሐንስ ማጥመቁን አላቆመም?” ቢሉም የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት፡- “መምህራችን ዮሐንስ ማጥመቅ ካቆመ  የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት እንደሚያጠምቁ ሁሉ እኛም ማጥመቅ አለብን” ብለው ችግር በፈጠሩ ነበርና /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ፣ Homily on the Gospel of John, Hom.29/፡፡
  ስለዚህም “ወሀሎ ዮሐንስኒ ያጠምቅ በሄኖን በቅሩበ ሳሌም በማዕዶተ ዮርዳኖስ- ዮሐንስ ደግሞ በሳሌም አቅራቢያ በሄኖን በዚያ ብዙ ውኃ ነበርና ያጠምቅ ነበር፡፡ ብዙ ሰዎችም እየመጡ ይጠመቁ ነበር፤ ዮሐንስ ገና ወደ ወኅኒ አልተጨመረም ነበርና” /ቁ.23-24/።  በዚህን ጊዜ አርድእተ ዮሐንስ መምህራቸው ያጠመቃቸው ሰዎች ወደ ጌታ ሲሄዱ የጌታ ደቀ መዛሙርት ያጠመቋቸው ግን ወደ ዮሐንስ እንደማይመጡ አስተዋሉ፡፡ በዚህም ምክንያት የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት “የማን ጥምቀት ብትበልጥ ነው” ብለው ግራ ተጋቡ፡፡ በዮሐንስ እጅ ተጠመምቀው ነገር ግን ዮሐንስ እንደነገራቸው ወደ ጌታ ሲሄዱ የነበሩ አይሁድ አግኝተውም “የእኛ መምህር እያለ ወዴት ትሄዳላችሁ” ይልዋቸዋል፡፡ አይሁድም “የእናንተማ መምህር መስክሮ አለፈ እኮን” ሲልዋቸው “ስለ ማንጻት በመካከላቸው ክርክር ሆነ” /ቁ.25, Augustine, Tractes on the Gospel of John/።
  ከዚህ በኋላ አርድእተ ዮሐንስ “ወደ ዮሐንስ መጡና፡- መምህር ሆይ! በዮርዳኖስ ማዶ ከአንተ ጋር የነበረው አንተም የመሰከርህለት፥ እነሆ፥ እርሱ ያጠምቃል፤ ሁሉም ወደ እርሱ ይመጣሉ አሉት” /ቁ26/። በዚሁ ንግግራቸው ለዮሐንስ ያላቸውን ክብር “መምህር ሆይ!” በማለት ሲገልጡ ስለ ጌታችን ግን (ሎቱ ስብሐትና) ስሙን እንኳን ለመጥራት ተጠይፈው በንቀት “ከአንተ ጋር የነበረው ያጠምቃልና ስለዚህ ምን ትላለህ?” በማለት ሊያበሳጩት ይሞክራሉ፡፡
  ዮሐንስ ግን እነርሱ እንደገመቱት ሳይሆን በእጅጉ ሐሴት አድርገ፡፡ አሁንም እንደገና ስለ ክርስቶስ እንዲመሰክርላቸው ዕድል ስላገኘ ተደሰተ፡፡ በጥበብና በለሰለሰ ንግግርም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፡- “ከሰማይ ካልተሰጠው ማለትም ከእግዚአብሔር መምህርነትን ካልተሰጠው በቀር ሰው አንዳች ገንዘብ ማድረግ አይቻለውም፤ ይልቅ ክርስቶስን ስትተዉ ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ እንዳትገኙ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ /ሐዋ.5፡39/፡፡ እርሱ (ጌታ) ይህን ሁሉ የሚያደርገው በራሱ ሥልጣን ነውና፡፡ ደግሞም፡- ትምህረቴን የምትቀበሉ ከሆነና እኔንም የምትወዱኝ ከሆነ እኔ ክርስቶስ አይደለሁም፥ ነገር ግን መንፈቅ አስቀድሜ ከእርሱ በፊት ተልኬአለሁ እንዳልሁ ራሳችሁ ትመሰክሩልኛላችሁ። እኔ የተላክሁት የእርሱን መንገድ እጠርግ ዘንድ እንጂ ራሴን እሰብክ ዘንድ አይደለም፡፡ እኔ የመጣሁት በእርሱ ከፍ ከፍ እል ዘንድ እንጂ እርሱን ዝቅ ዝቅ እንዳደርግ አይደለም፤ የመጣሁት እንኳን የባሕርይ አባቱ ልኮኝ እንጂ ከራሴ አልነበረም፡፡ የተናገርኩትም ሁሉ ከእኔ ሳይሆን ከእርሱ የተቀበልሁትን እንደሆነ ቅሉ ምስክሮቼ እናንተው ናችሁ፡፡ ስለዚህ እኔ ታላቅ እንደሆንኩ አታስቡ፡፡ ታላቅስ ዓለማትን በእጁ የያዘ ጌታ በእውነት እርሱ ነው፤ ዘቦቱ መርዓት መርዓዊ ውእቱ- ሙሽራይቱ  ያለችው (ምእመናን ያሉት) እርሱ ሙሽራ (ክርስቶስ) ነው፤ ማለትም የሚያገባው እርሱ ያጨ ነው፡፡ ማለትም ምእመናንን ቤተ ክርስቲያንን ያጨ እርሱ ነው፡፡ ቆሞ የሚሰማው ሚዜው ያጨ አይደለም፡፡ ሚዜው የሙሽራውን ሚስት (ምእመናንን) ለራሱ ቢወስድ እርሱ አመንዝራ ነው፡፡ ስለዚህ ሚዜው በሙሽራው ድምጽ፣ በሙሽራው (በክርስቶስ) ወደ ሚስቱ (ወደ ቤተ ክርስቲያን) መምጣት እጅግ ደስ ይለዋል። የክርስቶስ ባለሟል የምሆን የእኔ ደስታ፣ የእኔ ሐሴት የእርሱ የሙሽራው መምጣትና ምእመናኑም ትምህርቱን ተቀብለዉትና አምነውበት ሲያድርባቸው ሲዋሐዳቸው ማየት ነው፡፡ ይህ ሁሉ ባይሆን ሐዘኔ በበዛ ነበር፡፡ አሁን ግን ስለ መጣ ይህ ደስታዬ ተፈጸመልኝ። የእኔ የማዘጋጀት መምህርነትም አለፈች፤ የእርሱ ግን መቼም መች አታልፍም፡፡ ስለዚህ እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ያስፈልጋል። እናንተም ከእኔ ይልቅ ወደ እርሱ ዘወር ትሉ ዘንድ ይገባል፡፡ ምንም በኃጢአት ወደ ተጨማለቅነው ያለ ኃጢአት በሥጋ ተገልጦ ቢመጣም ከላይ የመጣው እርሱ ከሁሉ በላይ ነውና ማለትም አማናዊው ሙሽራ የባሕርይ አምላክ ነውና፤ ከምድር የተገኘሁ እኔ ግን ምድራዊ ነኝ፤ አባቴ ዘካርያስ እናቴ ኤልሳቤጥ እያልኩም ምድራዊ ልደቴን አስተምራለሁ። ዓለምን ለማዳን ከእርሱ በቀር ከላይ የመጣ የሌለ እርሱ ግን ከሁሉ የሚበልጥ፣ ሰማያዊ ደግሞም አልፋና ዖሜጋ ነው። ከአባቱ ዘንድ በህልውና ያየውንና የሰማውንም ይህን ይመሰክራል፤ ምስክርነቱን ግን የሚቀበለው የለም። ምስክሩን የተቀበለ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ አተመ፤ ተናገረ። እግዚአብሔር የሾመው እውነተኛ መምህርም የእግዚአብሔርን ቃል ያስተምራል፤ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና። ማለትም የለበሰው ሥጋ የባሕርይ አምላክ የሆነ እንጂ ልዩ ልዩ ጸጋ እንደተሰጠን እንደ እኛ በተከፍሎ አይደለም /1ቆሮ.12፡4/፡፡ አባት ልጁን እንደ እኛ በፈቃድ ሳይሆን በባሕርይው ይወዷል፤ ሁሉንም በእጁ ጭብጥ በእግሩ እርግጥ አድርጎ ሰጥቶታል። ስለዚህ በእኔ ሳይሆን በዚሁ ሙሽራ በወልድ ያመነ የማታልፍ መንግሥተ ሰማይን ይወርሳል፤ በወልድ ያላመነ ግን  የእግዚአብሔር የቁጣው መቅሰፍት ማለት ፈርዶ ያመጣበትን ፍዳ ሲቀበል ይኖራል እንጂ የማታልፍ መንግሥተ ሰማያትን አይወርስም” /ቁ.27-36/፡፡
 ፀሐየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! እኛ ከአንተ እንወለድ ዘንድ አንተ ከእኛ ባሕርይ ስለተወለድክልን እናመሰግንሃለን፡፡ በጥምቀት ከአንተ ጋር ቀብረህ ዳግመኛ ከአንተ ጋር ስላነሣኸንም እናመሰግንሃለን፡፡ አዲስ ልደት፣ አዲስ ሕይወት፣ አዲስ ልብም ስለ ሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ በመርዛማው እባብ በፈቃዳችን ብንሞትም በአንተ ሞት ሞታችንን ስለገደልከው እናመሰግንሃለን፡፡ አባት ሆይ! አሁንም ምንም ኃጢአተኞች ብንሆንም አብሮነትህ አይለየን፡፡ ቅዱስ መንፈስህም አትውሰድብን፡፡ እኛ አንሰን አንተ ግን ከፍ ከፍ እንድናደርግህ ማስተዋሉን ስጠን፡፡ አለማወቃችን እንድናውቅ እርዳን፡፡ አንተ ማን መሆንህን ሳያውቁ ሙሽራይቱን (ቤተ ክርስቲያንን) የሚያሳድዱም አስታግስልን፡፡ እኛንም በምግባር በሃይማኖት እስከ ሕቅታ ድረስ እንድንታመን ደግሞም በፈተና እንድንጸና እርዳን፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን!!!!

የዮሐንስ ወንጌል የ16ኛው ሳምንት ጥናት (ዮሐ.3፡13-21)!!

የዮሐንስ ወንጌል የ16ኛው ሳምንት ጥናት (ዮሐ.3፡13-21)!!

by Gebregziabher Kide on Wednesday, March 14, 2012 at 5:14pm ·
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!
“ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው /ቁ.13/። “ይህ አነጋገር ከኒቆዲሞስ ንግግር ጋር ምን ግንኝነት አለው” የሚል ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ ግንኝነትስ አለው፡፡ ምክንያቱም ኒቆዲሞስ ጌታችንን “ከእግዚአብሔር የተላከ መምህር” አድርጎ አስቦት ስለ ነበር ጌታ ኒቆዲሞስን “አንተ እንደምታውቃቸው ምድራውያን መምህራን አድርገህ አታስበኝ፤ ምክንያቱም ከእኔ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ደግሞም የወረደ የለም፡፡ በሌላ አገላለጽ እነዚህ መምህራን በዚህ ምድር ስታያቸው እዚህ ምድር ብቻ የሚታዩና ከሰማይ የሌሉ ናቸው፤ እኔ ግን እዚህ በግዙፍ ሥጋ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ብታየኝም ከአባቴ ጋራ በህልውና አንድ ነኝ፤ በሰማይም በምድርም ሙሉዕ ነኝ፤ ሰማያዊ ሀብትን ሰማያዊ ዕውቀትን ገንዘብ አድርጌ የመጣሁኝ እኔ ብቻ ነኝ” ሲለው ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች “ታድያ እርሱ ሙሉዕ በኵለሄ በመለኰቱ ሳለ እንዴት ወረደና ወጣ ይባላል?” ይላሉ፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስላቸዋለን፡- እንዲህ እየተባለለት ያለው ወልድ በመለኰቱ ዙፋኑን ትቶ መውረዱን ለመግለጥ ሳይሆን በሥጋ ማርያም ገዝፎ መታየቱን፣ የባሮቹን መልክ ይዞ መምጣቱን ለማመልከት ነው፡፡ የሰው ልጅ ብሎ ራሱን ሲገልጥም እርሱ ሙሉ ሰውነትን ማለትም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሥጋንና ፍጹም ነፍስን ነስቶ መገለጡን ለማመልከት ነው /St. John Chrysostom on the Gospel of John, hom.27:1/፡፡
 አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ያደረጉ ቅዱሳን ወደ ሰማይ ቢወጡም ዓለምን ለማዳን አልወረዱም፡፡ ስለዚህ እኛም መውጣት ከፈለግን ሠረገላም ይሁን አውሮፕላን ሳያስፈልገን እንወጣ ዘንድ እንዲያወጣን የወረደውን ጌታ እንመን፡፡ መውጣት ከፈለግን ከእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም እንዲል ብቻችንን መውጣት አንችልም፡፡ ዳግም ተወልደን የሙሽራው ብልቶች ከሆንን ግን ከእርሱ ጋር አንድ አካል ስለምንሆን መውጣቱ ቀላል ነው /Augustine, Sermon on the New Testament Lessons 41:7-8/፡፡
 “ሙሴ በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ ወልደ እጓለ እመሕያው ክርስቶስ ይሰቀል ዘንድ” መጥቷልና፡፡ የዚህ የዳግም ልደታችን ምንጭ አንድም የመውረዱ ምሥጢር መስቀል ነውና /ቁ.14-15/። እነዚህ ሁለቱም ምሥጢራት ማለትም የጥምቀቱና የመስቀሉ ምሥጢር ክርስቶስ ለምንጠላው እንኳን ድንቅ የሆነ ፍቅሩን ያሳየባቸው ምሥጢራት ናቸው፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ኃጢአት ሲያበዙ በመርዘኛ እባብ ተነድፈው ሙሴ በሰቀለው የነሐሱ እባብ ከሞት እንደተረፉ አሁንም በመርዘኛው እባብ (ኃጢአት ፍዳ ባለበት በዲያብሎስ) የተነደፍን ሁሉ በነሐሱ እባብ (ኃጢአት ፍዳ በሌለበት በንጹሐ ባሕርይ በጌታ ስቅለት) እንደምንድን እየተናገረ ነው፡፡ ልናስተውለው የሚገባ ነገር ግን ብዙ ጊዜ እባብ የክፋት ምሳሌ ብትሆንም ጌታችን (ሎቱ ስብሐትና) በነሐሱ እባብ እየተመሰለ ያለው ክፉ ሆኖ ሳይሆን በፍቃዱ “በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ…ኃጢአትን በሥጋ ለመኰነን” ስለ መጣ ነው /ሮሜ.8፡3፣ St. Gregory of Nyssa, Vita Moysis, PG 44:415/፡፡
ምክንያቱም፡- “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና” /ቁ.16/። የዘላለምን ሕይወት የሚሰጠን እርሱ ዘላለማዊ ስለሆነ ነው፤ ትንሣኤ ሕይወትን የሚሰጠን እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ስለሆነ ነው፡፡ እኛ ምንም አፈርና ጭቃ ብንሆንም እንዲሁ (ያለ ምክንያት) ወደደን፡፡ እኛን ለማዳንም አንድያ (የባሕርይ) ልጁን እንጂ ከባሮቹ አንዱን፣ ወይም መላእክትን፣ ወይም ሊቃነ መላእክትን አልላከልንም፡፡ ምንም ቸርነቱን ለመቀበል ያልተገባን ብንሆንም እንዲሁ ደሙን አፈሰሰልን /St. John Chrysostom. Ibid/፡፡
 “ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና” /ቁ.17/። በሌላ አገላለጥ በሥጋዊው እጅ ለሌለው እጅ፣ እግር ለሌለው እግር፣ ዓይን ለሌለው ዓይን በመንፈሳዊው ቅሉ ደግም ተሐድገ ለኪ ኃጢአትኪ- ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል ተሐድገ ለከ ኃጢአትከ- ኃጢአትህ ተሰርዮልሀል ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትኖራለህ እያለ ሊያድነው ካሳ ሊከፍልለት እንጂ ቀድሞ በፈረደበት ፍርድ ሌላ ፍርድ ሊፈርድበት አልመጣም፡፡ ስለዚህ “በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል” /ቁ.18/። ያላመነው ሁሉ ትንሣኤ ቢኖሮውም ትንሣኤ ለዘሐሳር ነው፡፡ አሁን ተፈርዶበታል ሲልም አስቀድሞ ለዚያ ተወስኗል ማለት ሳይሆን አስቀድሞ ባለማመኑ ያው ትንሣኤው ለፍርድ ነው ማለት ነው፡፡/ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ/፡፡
 “ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው” /ቁ.19/። “ይህ ማለት” ይላል ክርስቶስ “እኔ ዓለምን እፈርድበት ዘንደ መጥቼ ብሆን ኖሮ ሰዎች ላለማመናቸው ምክንያት ባገኙ ነበር፡፡ ነገር ግን አመጣጤ የሰው ልጅን በሙሉ ከጨለማ ወደ ብረሃን አወጣ ዘንድ ነው፡፡ ወደ ብርሃን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ማለትም በእኔ ያምኑ ዘንድ ፈቃደኞች ያልሆኑ ይፈረድባቸዋል፤ ስለ ተፈረደባቸውም ምክንያት የላቸውም” /St. John Chrysostom. Ibid/፡፡
“ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጎ እንደ ሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል” /ቁ.20-21/።
 እንግዲያስ ወንድሞቼ ሆይ! ጨለማው እንዳይጋርደን ወደ ብርሃን ለመውጣት እንቻኰል፤ እንድን ዘንድ እንንቃ፤ ጊዜ ሳለልን እንነሣ፤ ቀን ሳለልን ብርሃኑም  ሲያበራልን እንንቃ፤ ቀኑም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ወደ እርሱ ብንመጣ ኃጢአታችን ይቅርታ ይደረግለታል፡፡ ምንም ጽድቅ ሳይኖረን በባዶ ራሳችንን ከፍ ከፍ የምናደርግ ሁሉ ትርፉ በጨለማ መቅረት ነውና ወደ ብርሃን ክርስቶስ እንውጣ፡፡
 ሰው የእግዚአብሔር ፈቃድ ፍጥረት ነው፡፡ ኃጢአት ደግሞ የእኛ ፈቃድ ውጤት ነው፡፡ ስለዚህ አኛ ያደረግነውን ትተን እግዚአብሔር ወዳደረገልን የፍቅር ሥራ እንውጣ፡፡ የእኛ ሥራ ሕጸጽ እንዳለበት ስናውቅ ሕጸጽ ወደሌለበት የእግዚአብሔር ሥራ እንፍጠን፡፡ ንስሐ የመልካም ነገር ጅማሬ ናት፡፡ ሰው በጨለማ ውስጥ መኖሩን ሲያውቅ (በኃጢአት ውስጥ ለማለት ነው) ይቅርታ እንደሚያስፈልገውም ያውቃል፡፡
ይህን ሁሉ እንድናደርግ ሰውን እንዲሁ በማፍቀር ሰው የሆነው ጌታ ይርዳን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!!

FeedBurner FeedCount