Monday, May 21, 2012

በእንተ ሐዊሮቱ ገሊላ- የዮሐንስ ወንጌል የ18ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡1-6)!!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ሳምንት እንደተነጋገርነው ብዙ ሰዎች ዮሐንስን ትተው ወደ ክርስቶስና ወደ ደቀመዛሙርቱ ይሄዱ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት  ማለትም ከአርድእተ ዮሐንስ ይልቅ አርድእተ ክርስቶስ አብዝተው እንዳጠመቁ አይተው ፈሪሳውያን ቅንዓት ይዞዋቸዋል፡፡ ጌታችንም ፈሪሳውያኑ ይህን ሰምተው እንዳዘኑ “ባወቀ ጊዜ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ ደግሞ ሄደ” /ቁ.1-2/፡፡ ከእናንተ መካከል “ጌታችን ለምን እንዲህ አደረገ?” የሚል ቢኖር እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- ጌታችን እንዲህ ያደረገው ፈሪሳውያኑን ፈርቶ ሳይሆን የፈሪሳውያኑ ቅናትና ክፋት መልሶ እነርሱን እንደሚጎዳቸው ስለሚያውቅ ነው፡፡ ምክንያቱም ክፉ አድራጊ ራሱን እንጂ ማንንም ሊጎዳ አይችልምና፡፡ ፈሪሳውያን እርሱን ለመጉዳት ሲመጡ ከእነርሱ በላይ ሊጎዳቸው ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን በባሕሪይው ፍቅር የሆነው ጌታችን አንድ ቀንስ እንኳ እንዲህ አድርጎ አያውቅም፡፡ ስለዚህም ነገር ሁሉ እንደ እነርሱ ደካማነት ያደርግላቸው ነበር(ለምሳሌ፡- በእነርሱ እይታ ጌታ ፈርቷቸው ሄዷል- ሎቱ ስብሐት)፡፡
የሚገርመው ደግሞ “ደቀ መዛሙርቱ እንጂ ኢየሱስ ራሱ አላጠመቀም” /ቁ.3/። ይህም ማለት የተደረገው ሁሉ ስለ እነዚህ ደካማ ሰዎች የተደረገ ነበር፡፡ የሚደረገው ሁሉ ስለ እነርሱ ጥቅም ይደረግ ነበር፡፡ ሆኖም ግን እነርሱ የባሰ በቅናት ይሰክሩ ነበር፡፡ ጌታ የእነዚህ ቅናተኞች እጅና እግራቸውን አስሮ በይሁዳ መቆየት ቢፈልግ መቆየት ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን የሰውን ነጻ ፈቃድ የሚጋፋ አምላክ አይደለም፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አንድ አገልጋይ አሳዳጆቹ ሲበዙ መሸሽ ኃጢአት እንዳልሆነ ለማስተማር ማለትም ፈርቶ ሳይሆን እንደ መልካም አስተማሪ “ሰው የሚጠላባችሁን ሥራ አትሥሩ” ብሎ ለአርአያነት ሀገራቸውን ለቆ ወደ ገሊላ ሄደ /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ፣ Homoly on the Gospel of John, Hom.31:1/፡፡
 አስቀድሞ (ምዕ.3፡26) “እርሱ ያጠምቃል” ተብሎ አሁን ደግሞ “እርሱ አላጠመቀም” ስለተባለ የሚጋጭ ሐሳብ ሊመስላችሁ ይችላል፡፡ ነገር ግን የሚጋጭ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ጌታ በግዙፉና በሚዳሰሰው እጁ አላጠመቀም፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ግን ያጠምቁ ነበር፡፡ ይህም ማለት በእነርሱ አድሮ ያጠምቅ ነበር ማለት ነው፡፡ መጥምቁስ “እርሱ…ያጠምቃችኋል” ብሎ የለ /ማቴ.3፡11/? አሁንስ መቼ ማጥመቅ አቁሞ ያውቃል? በካህኑ እጅ የሚያጠምቅ እርሱ አይደለምን?
 ስለዚህ ደቀ መዛሙርቱ ያጠምቁ ነበር፡፡ በዚሁ መሠረት ይሁዳም ያጠምቅ ነበር ማለት ነው፡፡ ልትደነቁ ትችላላችሁ!! ይሁዳ ያጠመቀው ዳግመኛ አልተጠመቀም፡፡ ዮሐንስ መጥምቅ ያጠመቀው ግን ዳግመኛ ይጠመቅ ነበር፡፡ ይሁዳ ሲያጠምቅ ጥምቀቱ የክርስቶስ ነበር፤ ዮሐንስ ሲያጠምቅ ግን ጥምቀቱ የዮሐንስ ብቻ ነበር፡፡ ምንም እንኳን ከይሁዳ ይልቅ ዮሐንስ ጻድቅ ቢሆንም ከዮሐንስ ጥምቀት ግን የይሁዳ ጥምቀት ትበልጣለች /አውግስጢኖስ፣ Tractes on the Gospel of John, 15:2-3/፡፡
 ከዚህ በኋላ ጌታችን ወደ ገሊላ ለመሄድ “በሰማርያ በኵል ያልፍ ዘንድ ግድ ሆነበት” /ቁ.4/።  ይህች ሰማርያ በይሁዳና በገሊላ መካከል የምትገኝ ግዛት ናት፡፡ ስለዚህ በዚህች ግዛት ሳይረገጡ መሄድ አይቻለም ነበር፡፡ እነዚህ ሳምራውያን ጥንተ ነገዳቸው አይሁዳውያን ሲሆኑ ሀገራቸው በአሦር ነገሥታት በስልምናሶርና ሳርጎን ስትያዝ ከአሕዛብ ከመጡ ሰዎች ጋር ተደባለቁ /2ነገ.17፡24-33/፡፡ መደባለቅ ብቻ ሳይሆን ከእነርሱ ጋር ተጋቡ፤ ጣዖታቸውን አምለኩ፡፡ እግዚአብሔርን ስላልፈሩም የአንበሳ መዓት ተሰዶባቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ከዚህ ተመልሰው እግዚአብሔርን ማምለክ ፈለጉ፡፡ ካህን ተልኮላቸውም የሙሴ መጻሕፍትን እንዲያውቁ ተገደረጉ፡፡ አይሁድ ከባቢሎን ምርኮ ሲመለሱ ከእነርሱ ጋር ቤተ መቅደስን መሥራት ቢፈልጉም በበዘሩባቤልና በነህምያ ተቀባይነት ስላላገኙ በገሪዛን ተራራ ለራሳቸው ቤተ መቅደስ ሠሩ፡፡ “ማንበብ ያለብን አምስቱ የሙሴ መጻሕፍት ብቻ ነው፤ እግዚአብሔርን የምናመልከው በኢየሩሳሌም ሳይሆን በገሪዛን ተራራ ነው፤ የእግዚአብሔር ማደርያም ጽዮን ሳትሆን ሴኬም ናት” አሉ፡፡
 ጊዜው ሲደርስ ግን ጌታችን የሕይወትን ዘር ይዘራባቸው ዘንድ ወደ ሀገራቸው መጣ፡፡ ጌታችን መጥቶ ዘሩን የዘራባት ቦታም ሴኬም (ሲካር) ትባላለች፡፡ ወንጌላዊው፡- “ስለዚህ ያዕቆብ ለልጁ ለዮሴፍ በሰጠው ስፍራ አጠገብ ወደምትሆን ሲካር ወደምትባል የሰማርያ ከተማ መጣ” እንዲል /ቁ.5/፡፡ የቦታው ስም ያለ ምክንያት የተጠቀሰ አይደለም፡፡ እነዚህ የሰማርያ ሰዎች፡- “እኛ የተለየንና የተከበርን ሰዎች ነን፤ እንደ አይሁድ የማንንም ነብይ ደም አላፈሰስንም፡፡ ስለዚህ የአብረሃም ልጆች ነን፤ የልጁም የያዕቆብ ልጆች መባል የሚገባንም እነርሱ ሳይሆኑ እኛው ነን” እያሉ ይመኩ ነበር፡፡ ጌታችንም ይህን ትምክሕታቸው ስለሚያውቅ የያዕቆብ ልጆች የሆኑት ሌዊና ስምዖን በእኅታቸው በዲና ምክንያት የሴኬም ሰዎችን ወደ ገደሉባት ሀገር መጣ፤ የሚያስመካ ነገር እንደሌላቸውም በዘዴ አስተማራቸው፤ እነርሱም ደም እንዳፈሰሱ በጥበብ ነገራቸው /ዘፍ.34፣ ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡
 “በዚያም የያዕቆብ ጕድጓድ ነበረ። ኢየሱስም መንገድ ከመሄድ ደክሞ በጕድጓድ አጠገብ እንዲህ ተቀመጠ፤ ጊዜውም ስድስት ሰዓት ያህል ነበረ” /ቁ.6/።  የሚገርም ነው! ጌታችን በዚሁ ጕድጓድ የሚያገኛት ሳምራይቱ ሴት በጧት ውኃ መቅዳት ትችል ነበር፡፡ ነገር ግን የእርሷ አመጣጥ መለኰታዊ ዕቅድ አለበትና አንድም ሴትዮዋ ለመሲሑ የሚምበረከክ ልብ አላትና አንድም ይህች ሴት ከያዕቆብ የጕድጓድ ውኃ ይልቅ የማይነጥፍ የውኃ ምንጭ የምትሻ ናትና በተዋሐደው ሥጋ ደክሞ የሚመጣውን ጌታ ትገናኝ ዘንድ እስከዚሁ ሰዓት ሳትወጣ ቆየች፡፡
ወዮ! ስንደክም የሚያበረታን እርሱ ደከመው፡፡ የሕይወት ውኃ ምንጭ እርሱ ውኃ አጠጭኝ አላት፡፡ ከባሕርዪው የሕይወትን ውኃ የሚያጠጣ እርሱ ከወራጁ ውኃ አጠጭኝ አላት፡፡ እንዴት ዕጹብ ነው? የአምላክ ትሕትና እንዴት ያለ ነው? /ቅ.አምብሮስ፣ Of the Holy Spirit 1:16:184-85/፡፡
ውኃ አጠጪኝ አላት አፍላጋት የሠራው፤
እንደተቸገረ ውኃ እንደጠማው ሰው፡፡
     አይሁዳዊ አለችው አወይ አለማወቅ፤
    ሰማያዊው አምላክ ‘ራሱን ቢደብቅ፡፡ (ዘማሪ ይልማ ኃይሉ)!!

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount