Wednesday, May 2, 2012

የጉብዝናን ወራት እንደ ዮሴፍ!!

ብዙዎች እንደሚስማሙት የጉብዝና ወራት የሚባለው ከ20 እስከ 40 ዓመት ያለ ጊዜ ነው፡፡ ይህ ወራት ደግሞ ብዙዎቻችን በጸረ ክርስትና ፍልስፋናዎች ማለትም ካፒታሊዝም፣ ሶሻሊዝም፣ ኮሙኒዝም፣ ግራ ዘመም እና ቀኝ ዘመም ፖለቲካ የምንያዝበት ወራት ነው፡፡ ሂዩማኒዝም የሚባል የፍልስፍና ዓይነት “የችግሮቻችን መፍትሔ ሁሉ ያለው በእኛ እጅ እንጂ በሌላ አካል አይደለም” ይላል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ግን “አቤቱ የሰው መንገድ ከራሱ እንዳይደለ አውቃለሁ” ይላል /ኤር.10፡23/፡፡ ቅዱስ ዳዊትም ይኸንን ቢያውቅ “ቅዱስ መንፈስህን ከእኔ አትውሰድብኝ” አለ /መዝ.50፡12/፡፡ ከዚሁ በተጨማሪ ብዙ ወጣቶች ለአላስፈላጊ ግብረ ሥጋ ግንኝነት፣ ለጫት፣ ለሐሽሽ፣ ለስካር ይጋለጣሉ፡፡ በ2001 እ.ኤ.አ. በዓለም አቀፍ ደረጃ የተደረገ ጥናት እንደሚያመለክተው ኰሌጅ ውስጥ ከገቡ ወጣቶች 71% ሳይጋቡ የግብረ ሥጋ ግንኝነት ያደርጋሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ግን እንዲህ ይላል፡- “ልጄ ሆይ ስማ ጠቢብም ሁን፤ የልብህን ሐሳብ አቅና፡፡ የወይን ጠጅ ጠጭ አትሁን፤ ለሥጋም አትሣሣ፤ ሰካራምና አመንዝራ ይደኸያል” /ምሳሌ.23፡19-22/፡፡ ወጣቱ ዮሴፍ ወልደ ያዕቆብ ለብዙዎቻችን አርአያ ሊሆን የሚችል ነውና ከሕይወቱ መማር ያስፈልገናል፡፡ 1. ዮሴፍና የወንድሞቹ ቅናት፡ ዮሴፍ አባቱ ያዕቆብ ከወንደሞቹ ይልቅ በሥነ ምግባሩ መልካምነት አብልጦ እንዲወደው ባዩ ጊዜ ይጠሉት ነበር፣ በሰላም ይናገሩትም ዘንድ አልወደዱም፡፡ የዮሴፍ ልብ ግን ያው ነበር እንጂ አልተቀየረም፡፡ ወንድሞቹን ይወዳቸው ነበር፡፡ ለዚህም ነው ሰማያት ተከፍተው እየተመለከተ ወንድሞቹ ሁሉ ለእርሱ እንደሚሰግዱ ሲያይ የነበረው፡፡ ወንድሞቹ ሰማያዊውን መልእክት ከማስተናገድ ይልቅ የገዛ ወንድማቸውን የበለጠ ይጠሉት፤ ይቀኑበትም ነበር፡፡ ዮሴፍ የእነርሱን ቅናት ሳይመለከት በፍጹም ፍቅር ይወዳቸዋልና ከሴኬም ወደ ኬብሮን፣ ከኬብሮንም ወደ ዶታይን እየተቅበዘበዘ በበረሀው ደኅንነታቸውን ይመለከት ነበር፡፡ እነርሱ ግን ከሩቅ ሆነው እርሱን በመመልከት ይገድሉት ዘንድ ይማከሩ ነበር፡፡ ከዚሁ ይልቅ ግን እሱን በመሸጥ የሚያገኙትን ገንዘብ በማየት እንዲሁም ደግሞ በዓይናቸው እንኳን እንዳያዩት ለእስማኤለውያን ሸጡት፡፡ እርሱ እነርሱን በመውደድ ቢመጣም እነርሱ ግን በቅናት ተቃጥለው ጠበቁት፡፡ ቅናት አደገኛ በሽታ ነው፡፡ ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታ ላይ ቅናት ስለያዛቸው ቤታቸው እንደ ተፈታ ቀርቷል፤ መዳን ከእነርሱ ቤት ቀርቷል፤ ሐዋርያትን አሳድዷል፡፡ ወንድሞቹ ከቅናታቸው የተነሣ የዮሴፍን ልብስ ደም በመንከር እርሱ እንደ ሞተ በማስመሰል አባታቸውን አሳዝነዋል፤ ለብዙ ቀናት አስለቅሰውታል፤ ይጽናናም ዘንድ አልወደደም፡፡ 2. የዮሴፍ ንጽህና እና የጴጢፋራ ሚስት፡ ምንም እንኳን ዮሴፍ እንደ ባርያ ለእስማኤለውያን ቢሸጥም ልቡ ግን እንደ ባርያ አልነበረም፡፡ ከምንም በላይ ረዳቱ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነውና ጭንቀት የሚባል ነገር አይታይበትም ነበር፡፡ ባርያ ቢሆንም ግብጽን ከረሀብ ታድጓታል፡፡ ምንም ወንድሞቹ በቅናት ወደ ባርነት ቢሸጡትም እርሱ ግን በፎርዖን ቤት ነገሠ፡፡ በፎርዖን ዘንድ ባለሟልነትን አገኘ፡፡ እግዚአብሔርም ከእርሱ ጋር ስለ ነበረ የውስጡ ውበት በየዕለቱ ይፈካ ነበር፡፡ ይህም ቢሆን ግን ልቡ ወደ ትዕቢት አላዘነበለበትም፡፡ በዚሁ ሰዓት ግን ሌላ ፈተና ተጋረጠበት፡፡ የንጉሡ ሚስት ታስነቅፈው ዘንድ ወደደች፡፡ ይህም ቢሆን ግን ምናልባት ልብሱ ትቀድበት እንደ ሆነ እንጂ ልቡን ታቆሽሽበት ዘንድ አልተቻላትም፡፡ ዮሴፍ እንደ ስሙ ጥንካሬ እና ንጽህናን እየጨመረ ሄደ፡፡ ወንደሞቹን እንደወደዳቸውም የጴጢፋራን ሚሰት ይወዳት ነበር፡፡ ስለዚህም ነበር ልብን በሚያቆስል አነጋገር “አንቺ አመንዝራ ሴት ነሽ፤ ከአመንዝራ ሴትም ጋር እተኛ ዘንድ አይገባም” ሳይላት ስለ ራሱ ብቻ ይናገር የነበረው፡፡ እርሷ ንግሥት እርሱ ግን ባርያ እንደሆነም ይነግራት ነበር፡፡ ምንም ወደ ወኅኒ ብትጥለውም አንዳች እንኳን አልመለሰላትም፡፡ እርሷ ግን በተቃራኒው እንኳንስ እርሱን ራሷንም የማትወድ ምስኪን ነበረች፡፡ ምክንያቱም ወዳውስ ቢሆን ኖሮ ወደ እስር ቤት ባልጣለችው ነበርና፤ ራሷንም የምትወድ ብትሆን ኖሮ ንግሥት ሆና ሳለ ይህን የመሰለ አሳፋሪ ሥራ አታደርግም ነበርና፡፡ ስለዚህ እርሷ በፍቅር ሳይሆን በዝሙት የተቃጠለች ሴት ነበረች፡፡ ምንም እንኳን ዮሴፍ አብርሃም እና ይስሐቅን ከመሰሉ ታላላቅ አባቶች የተወለደ ቢሆንም ራሱን ከፍ ከፍ ሳያደርግ ለፎርዖን ይታዘዝ ነበር፡፡ ንጽህናው ለወጣት ወንዶች ሁሉ አርአያ ነው፡፡ አዎ! ወንዶች ከዮሴፍ፣ ሴቶች ከሶስና ደናግላንም ከድንግል ማርያም ንጽህናን መማር ይገባናል፡፡ ይህን ንጽህና እንይዝ ዘንድ ጌታ ይፈልጋል፡፡ ይኸንንስናደርግ አምላካችን ይደሰታል፤ በሕይወታችንም እንደ ዮሴፍ ይባርከናል፡፡ ምንም እንኳን ዮሴፍ ልብሱን ትቶላት ቢሮጥም እንደ አዳም ግን አላፈረም፡፡ ንጽህናው በገነት ውስጥ ሆኖ ከበደለው አዳም ትበልጥ ነበርና፡፡ እንግዲያስ እኛም ወጣቶች ክብራችንን ለማጉደፍ እንቅልፍ ላጣች ዓለም ልብሳችንንም እንኳን ቢሆን ጥለንላት ከዝሙት ግብዣዋ እንራቅ (ዮሐንስ አፈወርቅ)፡፡ ይህንን ስናደርግ በእርግጥም መስቀላችንን ተሸክመናልና የክርስቶስ ደቀመዛሙርት እንባላለን፡፡ ኤልያስ የዚህ ዓለም የሆነውን መጐናጸፍያ በዚሁ ዓለም ትቶት እንደ ሄደ እኛም የዓለም የሆነውን ለራሷ እንስጣት (ቅዱስ ጀሮም)፡፡ 3. ዮሴፍና የማያቋርጥ አገልግሎቱ፡ ከላይ እንደገለጽነው የጴጢፋራ ሚስት የዮሴፍን ልብ መውሰድ ስላልተቻላት ልብሱን ብቻ በመያዝ እርሱን በመክሰስ የባሏን ቁጣ ታነሣሣበት ዘንድ ትጮኽ ነበር፡፡ ለካ የሴፍ ወደ እስር ቤት የተጣለው ለወንጀለኞችም የሚያስተምረው ትምህርት ስለ ነበረው ነው፡፡ አንዳንዴ ለእኛ የማይገባን እግዚአብሔርኛ ክንውኖች በእኛ ሕይወት ውስጥ ይከናወናሉ፡፡ የጴጢፋራ ሚስት ምንም በዙፋኗ ብትሆንም ከወንጀለኛ ሰው በላይ ብስጩ ነበረች፤ ዮሴፍ ግን “በወኅኒም” ቢሆን በወኅኒ ጠባቂው ዘንድ ሞገስን ስላገኘ እጅግ ደስተኛ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋራ ስለ ነበረ ወኅኒ ቤቱ ገነት ሆኖለታል፡፡ ዮናስ በዓሳ አንበሪ ሆድ ውስጥ ስለ ገባ የባሕሩ ወጀብና ማዕበል አላሰጠመውም፡፡ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳት ውስጥ ቢጣዱም ወላፈኑ ጨርቃቸውን እንኳን አልነካውም፡፡ ጌታ ዛሬም እንደ ዮሴፍ የመንፈስ ቅዱስ ማደርያ እንሆን ዘንድ ይሻል፡፡ እርሱ በእኛ ውስጥ ካደረ የትም ብንሆን አንጨነቅም፡፡ እርሱ ዕረፍታችን ነውና፡፡ እርሱ ሰላማችን ነውና፡፡ እኛን ለመጉዳት የመጡት ሆኔታዎችም እኛን ይጠቅሙ ዘንድ ጌታ ይቀይራቸዋል፡፡ ጌታ ጠላት ብለን በምናስባቸው ሰዎች እጅ እንኳን ማሳደግ እንደሚችል ከሙሴ ተምረናልና፡፡ ዮሴፍ ወደ እስር ቤቱ ባይገባ ኖሮ ሴትዮዋ አሥር ጊዜ እየመጣች “አብረን እንተኛ፤ ዝሙትም እንፈጽም” እያለች በጨቀጨቀችው ነበር፤ አሁን ግን ወደ ወኅኒ ስለ ጣለችው ይኸ ሁሉ ቀርቶለታል፡፡ በእስር ቤቱ ውስጥ ሆኖም እስረኞቹን እንደ ወንድሞቹ ያገለግላቸው ነበር፡፡ ስለዚህ እርሱ በሄደበት ሁሉ ሁሉንም በትሕትና ያገለግል ነበር፡፡ ለካስ እኛ ወጣቶች ትሕትናን ገንዘብ ስናደርግ ወደ ሕይወት ነው የምንወጣው!! 4. ዮሴፍ እና ሥልጣን፡ ዮሴፍ ከፍቅር ትምህርት ቤት ከተመረቀ በኋላ ማለትም የሚጠሉት ወንድሞቹን፣ የጴጢፋራን ሚስት እንዲሁም እስረኞችን በመውደድ በእጅግ ከፍተኛ ማዕረግ ካጠናቀቀ በኋላ እግዚአብሔር ወደ ክብር ዙፋን አውጥቶታል፡፡ ሲወጣም የመጀመርያ ሥራው የግብጽ ጠንቋዮችና አስማተኞች ሊፈቱት ያልቻሉትን ሕልም መፍታት ነበር፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያ ማንም ሊፈታው ያልቻለ ጥያቄ በእኛ በወጣቶች እጅ ይገኛል፡፡ እንደ ዮሴፍ እግዚአብሔርን አጋዥ የምናደርግ ከሆነ በየጊዜው የሚፈታተነን የድርቅ ዘመን በጥጋብ ማለፍ እንችላለን፡፡ የእግዚአብሔር በረከት ከእኛ ጋር ትሆናለች፡፡ በየትኛውም የሐላፊነት ቦታ ብንቀመጥም የተበደለውን ደሃ እንረዳለን እንጂ አናስጨንቅም፡፡ 5. ዮሴፍና ይቅርታ፡ የእስራኤል ልጆች ወንድማቸውን ከሸጡት በኋላ በረከት ርቋቸው በረሀብ ተጠቁ፡፡ በረከቱ ከዮሴፍ ጋራ ወደ ግብጽ ሄዷልና፡፡ ወንድሞቹ “ዳግም አናየውም” ያሉትን ዮሴፍ ጌታ በሀገራቸው ረሀብ አመጣ እና ዳግም እንዲገናኙት አደረገ፡፡ ወንደሞቹ ሲመጡ ግን ክፋታቸው ያውቁ ዘንድ አንዳንድ ማንቅያ ድርጊቶችን ከማድረግ ውጪ በፍቅር ተቀበላቸው እንጂ አልተበቀላቸውም፡፡ መጀመርያ ሲገናኛቸውም ስለ ፍቅሩ ለብቻው እየሄደ ያለቅስ ነበር፡፡ ዛሬ ክፉ ላደረጉብን ሁሉ ልናለቅስላቸውና ልናዝንላቸው ይገባል፤ ለእነርሱም እንባችንን እንጂ ቁጣችንን ልንስጣቸው አይገባንም፤ ካደረጉት መጥፎ ነገር የተነሣ ሊያጋጥማቸው ከሚችል ክፉ ሁሉ ይድኑ ዘንድ እንማልድላቸው ዘንድ ይገባናል፡፡ ምክንያቱም እየገፉን ያሉት (እነርሱ እንደዚያ ባያስቡትም) ወደ ክብር አክሊል ነውና፡፡ የዮሴፍ ወንድሞች እርሱን ከመፍራታቸው የተነሣ ፊቱን እንኳን ማየት አልቻሉም፡፡ መልካም ስናደርግ ከቃላችን በላይ ድርጊታችን ይናገራል፡፡ ዛሬ በኃጢአት ምክንያት ከእኛ አውጥተን የሸጥነውን ዮሴፋዊ ማንነታችን “እኔ ነኝ” ሲለን ዳግም በፍቅር ልንቀበለው ያስፈልጋል፡፡ ይኸንን ለማድረግም ፈጽመን አንፍራ፡፡ እግዚአብሔር የሚያየው የትላንቱ ኃጢአተኛ ማንነታችን ሳይሆን የዛሬውን የይቅርታ፤ የንስሐ እና እርሱን የፈለግንበት ልባችንን ነውና፡፡ ዮሴፍ ወንድሞቹ ያደረጉበትን ሳይሆን እግዚአብሔር ለምን ዓላማ ወደዚያ ሀገር እንዳመጣው ይነግራቸው ነበር፡፡ ስለ ተቀመጠበት ወንበርም ዓላማውን ይነግራቸው ነበር እንጂ ከዚያ የተነሣ በወንድሞቹ ላይ ድሮ እነርሱ እንዳሰቡት ክፋትን አላሰበም፡፡ እርሱ የይቅርታ እንጂ የበቀል ልብ የለውምና፡፡ ወንድሞቼ እና እኅቶቼ!! አንድ ነገር ልንገራችሁ? የዮሴፍ አምላክ የእኛም አምላክ ነው፡፡ ከእኛ ፈቃድን ብቻ ይሻል፡፡ እኛን የመለወጥ ኃላፊነት የእርሱ እንጂ የእኛ አይደለም፡፡ ስለዚህ “ጌታ ሆይ እኔ መለወጥ እፈልጋለሁ፡፡ የመለወጥ ኃይል ግን የለኝም፡፡ ስለዚህ ለብዙ ዘመናት ‘ልጄ ሆይ ልብህን ስጠኝ’ ያልከኝን ልቤን ውሰድና ያንተው ምርጥ ዕቃ አድርገኝ” እንበለው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋራ መጣበቅን እንውደድ፤ አላስፈላጊ መድሐኒቶችን እና መጠጥን አቁመን ጓደኞቻችንን እንምረጥ /1ቆሮ.15፡33፣ ምሳሌ.13፡20/፡፡ የደስታ ምንጭ መንፈስ ቅዱስ እንጂ እነዚህ ሱሶች አይደሉምና፡፡ ወደ ቤቱ መመላለስን እንለማመድ፡፡ በኋላ በክርስቶስ ፊት ከምናፍር ዛሬ ከእርሱ ጋር ሁነን ደስ ይበለን፡፡ አይዟችሁ እርሱ ከእኛ በላይ ለእኛ ቅርብ ነው፡፡ ሊረዳንም ዝግጁ ነው፡፡ እንበርታ፤ እንጨክን፡፡ እርሱ በእጃችንን ሲይዘን እኛም “አንለቅህም” ብለን እንያዘው፡፡ ዲያብሎስን ግን፡- “ከአሁን በኋላ የጌታየ እንጂ ያንተው አይደለሁም፤ እስከ ዛሬ ድረስ ላታስተኛኝ ተኛ ያልከኝን ይበቃሀል” እንበለው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በጉብዝናችን ወራት ከቅናት የጸዳን፣ ንጽህናን ገንዘብ ያደረግን፣ አገልግሎታችንም ሁሉ በትሕትና እና በይቅርታ የተመላ ያድርግልን፡፡ አሜን!!

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount