Saturday, May 19, 2012

የዮሐንስ ወንጌል የ8ኛው ሳምንት ጥናት (ዮሐ.1፡35-42)!!

“በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር፥ ኢየሱስን ሲሄድ አይቶት፡- እነሆ የእግዚአብሔር በግ አለ።” /ቁ.35-36/
 የሰው ልጅ በባሕርይው ሐዋርያው፡- “ስለ አንድ ነገር መልሼ ልጽፍላችሁ አይታክተኝም፤ እናንተን ያበረታችኋልና” እንዳለው ተደጋግሞ ካልተነገረው በቀር ተሎ አይገባውም /ፊል.3፡1/፡፡ ለዚህም ነው መጥምቁ ከዚህ በፊት የተናገረውን ቃል መልሶ የሚነግራቸው፡፡ ሲነግራቸውም መንደሩ እየዞረ ሳይሆን ሁሉም ወደ ባሕረ ዮርዳኖስ እንዲመጡ በማድረግ ነበረ፡፡ “ለምን እንዲህ አደረገ?” ብለን ስንጠይቅም አንደኛ ሌሎች እርሱን የሚመስሉ ሐሰተኞች ዮሐንሶች በተነሡ ነበር፤ ሁለተኛ ሕዝቡ ሁሉም በተሰበሰበበት ሁኔታ “እነሆ የነገርኳችሁ በግ” ቢላቸው የበለጠ ታማኝነትን ያገኛል፤ ሦስተኛ ምስክነቱ እውነት እንደሆነ (ከዝምድናው የተነሣ እንዳልሆነ) አብም መንፈስ ቅዱስም ሲያረጋግጡት ሕዝቡ የበለጠ ያምናል፤ አራተኛ አይሁድ ክርስቶስ ሕግ አፍራሽ ነው ብለው ላለማመናቸው ምክንያት እንዲያጡ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ነበረበት፡፡ ነብያትን መታዘዝ ጽድቅ ነውና፡፡ ስለዚህ ሚዜው ሙሽራይቱን ከሙሽራው ጋር ለማገናኘት አሁንም ከወንዙ ዳር ቆሞ “እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ በግ” እያለ ይጮኽ ነበር /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐ. ወንጌል ትርጓሜ ድርሳን 18፣ ድርሳን በእንተ ጥምቀት/፡፡
  ከዚህ በኋላ ሁሉም ሳይሆኑ “ሁለቱም ደቀ መዛሙርት ዮሐንስ ይህን ሲናገር ሰምተው ኢየሱስን ተከተሉት።” /ቁ.37/ እውነት ነው! ፀሐይ ከወጣች በኋላስ የሻማ ጥቅሙ ምንድነው? የዮሐንስ ጥምቀትስ የክርስቶስ ጥምቀት ከመጣች በኋላ ምን ረብሕ አላት? /ቅ.ኤፍሬም ሶርያዊ Commentary on Tatians Diatessaron 4:17/፡፡
ክርስቶስም ሲከተሉት አይቶ በልባቸው ምን እንደሚፈልጉ ስለማያውቅ ሳይሆን ፈቃደኝነታቸውን ለመጠየቅ “ምን ትሻላችሁ?” አላቸው /ቁ.38/፡፡   እነርሱም “ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ?”  በማለት የሚፈልጉት እንዲያስተምራቸው እንደሆነና ወዴት እንደሚኖር በግልጽ ነገሩት፡፡ እርሱም “መጥታችሁ እዩ” አላቸው። መጥተውም ለቀበሮዎች ጕድጓድ ለሰማይም ወፎች ማረፍያ ጐጆ እንዳላቸው ክርስቶስ ግን ራሱን የሚያስጠጋበት እንደ ሌለው አዩ፤ በዚያም ቀን እስከ አሥር ሰዓት ድረስ በእርሱ ዘንድ ሲማሩ ዋሉ /ቁ.39፣ ሉቃ.9፡58/፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ሆነው ሄደውም እስራኤል ዘነፍስ ተባሉ /ቴዎዶር ዘሜውፕሳስትያ Commentary on John 1:1:38/፡፡
 “ከዮሐንስ ዘንድ ሰምተው ከተከተሉት ከሁለቱ አንዱ የስምዖን ጴጥሮስ ወንድም እንድርያስ ነበረ” /ቁ.40/፡፡ ምንም እንኳን ስሙ የተጠቀሰው እንድርያስ ብቻ ቢሆንም ሁለተኛው ግን ወንጌላዊው ዮሐንስ ራሱ ነበር፡፡ “እንዴት ይታወቃል?” ቢሉ ወንጌሉን ሲጽፍ የተለያየ ቦታ ስለ እርሱ የሚነገሩትን “ጌታ ይወደው የነበረ ደቀ መዝሙር” ይላል እንጂ በሙሉ ስለ ትሕትና ብሎ ስሙን አይጠቅስምና /ዮሐ.19፡26፣ ቴዎዶር ዘሜውፕሳስትያ ዝኒ ከማሁ/፡፡
“እንድርያስም አስቀድሞ የራሱን ወንድም ስምዖንን አገኘውና፡- መሢሕን አግኝተናል አለው፤ ትርጓሜውም ክርስቶስ ማለት ነው። ወደ ኢየሱስም አመጣው” /ቁ.41/፡፡ የሚገርም ነበር! ሰብአ ሰገል “የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው?” ብለው ጠይቀው ለራሳቸው አግኝተውት ስለሄዱ አሁን እንድርያስ ሲያገኘው በጣም ነበር የተደሰተው፡፡ ምክንያቱም መጥምቁ የሚጠበቀው መሲሕ እርሱ መሆኑን ነግሮዋቸዋል፤ መንፈስ ቅዱስ ሲመሰክር አይተዋል፡፡ ክርስቶስም እርሱ ማን እንደሆነ ነግሮታል፡፡ እንድርያስ ያልተማሩና የተናቁ የገሊላ ሰዎች በመሆናቸው መሲሑን ሲያገኘው በጣም ተደስቷል፡፡ “በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን ወጣለት” የሚለው የነብዩ ቃል ሲፈጸምለት በዓይኑ አይቷል /ኢሳ.9፡1/፤ “ምናምንቴዎችን መረጠ” የሚለው ቃል ሲፈጸምለት የማይደሰትስ ማን ነው? /1ቆሮ.1፡27፣ ኤፍሬም ሶርያዊ ዝኒ ከማሁ/፡፡ የሚደንቀው ደግሞ እንድርያስ እዚያ ተቀምጦ አልቀረም፤ ወንድሙን ይጠራ ዘንድ ተፋጠነ እንጂ፡፡ በሰዓታት ጊዜ ውስጥ ተምሮና አምኖ “መሲሕን አግኝተናል” እያለ ወንድሙን ለመስበክ ተቻኮለ፡፡ በጣም በጉጉት ሲጠብቀው እንደነበረም ያመለክታል /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ድርሳን 19/፡፡
 “ኢየሱስም ስምዖንን ተመልክቶ። አንተ የዮና ልጅ ስምዖን ነህ፤ አንተ ኬፋ ትባላለህ አለው፤ ትርጓሜው ጴጥሮስ ማለት ነው” /ቁ.42/፡፡ ጴጥሮስ ለመጀመርያ ጊዜ ስሙ የሚቀየረው በዚሁ ሰዓት ነው፡፡ ጴጥሮስ ማለት ዐለት ማለት ነው፡፡ ይህም የቤተ ክርስቲያን መሠረት ጽኑ እና የማይነዋወጥ መሆኑን ያመለክታል /ማቴ.7፡24፣ ማቴ.16፡18፣ አውግስጢኖስ ዝኒ ከማሁ 7፡14/፡፡
 “ክርስቶስ ለአንዳንዶቹ ሐዋርያት ስማቸውን የሚቀይርላቸው ለምንድነው?” ብለን ስንጠይቅም በብሉይ ኪዳንም አብራምን አብራሃም፣ ሦራን ሣራ፣ ያዕቆብን እስራኤል ያለ አምላክ እርሱ እንደሆነ እንገነዘብ ዘንድ ነው /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡
 ሳንወደው ለወደደን ከዲያብሎስ መንጋጋ አላቅቆም ወዳጆቹን ላደረገን ለእግዚአብሔር ዛሬም ዘወትርም ስሙ የተመሰገነ ይሁን አሜን!!

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount