Thursday, May 3, 2012

=+= “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ”=+=

በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 4 የምናገኛት ሳምራይቱ ሴት ውኃ ልትቀዳ ወደ ያዕቆብ ጕድጓድ እንደመጣች እንመለከታለን፡፡ ነገር ግን የክብር ንጉሥ፣ የዓለሙ መድኃኒት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ልቧ ሰተት ብሎ ሲገባ “ማድጋዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች”፡፡ መጽሐፍ “ሊከተለኝ የሚወድ እርሱ መስቀሉን ተሸክሞ ይከተለኝ” ይላል፡፡ በእውነቱ ሐዋርያት መረባቸውን፣ መንጠቆዋቸውን ትተው የምሥራችን ለዓለም ለመንገር እንደወጡ ይህቺ ሴትም ማድጋዋን ትታ በሐሴት ሠረገላ ተጭና ወንጌሉን ለመንገር ስትሯሯጥ እናያታለን፡፡ “ለሰዎችም ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” እያለች መላ ከተማውን ጠራርጋ ታመጣቸው ነበር። የሚገርመው ሴቲቱ የምታመጣቸው ሰዎች እንደ እንድርያስ ወይም ደግሞ እንደ ፊሊጶስ አንድ ወይም ሁለት ሰዎች ብቻ አይደሉም፡፡ መላ ከተማውን እንጂ፡፡ ትጋቷም ከኒቆዲሞስ በላይ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በወልደ እግዚአብሔር ቢያምንም እንደ እርሷ ግን በግልጥ ለመመስከር አልወጣም፡፡ ሐሳብዋን ብቻ ይግለጥላት እንጂ እንዴት እንደምትነግራቸው የቃላት ምርጫ አታደርግም፡፡ እናም “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” ትላቸዋለች፡፡ ተጠራጥራ አይደለም፤ መጥተው ራሳቸው ለራሳቸው እንዲወስኑ እንጂ፡፡ ስለዚህም “ኑና እዩ፤ አይታችሁም እመኑ” እያለች ከነፍሳቸው እረኛ ጋር እንዲገናኙ ትፈልጋቸው ነበር፡፡ ሰዎቹም የምትነግራቸውን ነገር ለማየት “ከከተማ ወጥተው ወደ ጌታችን ይመጡ ነበር”። ይህች ሴት በጠዋት አዋልደ ሰማርያን ላለማየት ብላ በጠራራ ፀሐይ ውኃን ለመቅዳት የመረጠች ሴት ነበረች፡፡ አሁን ግን እውነተኛው ፀሐይ ሲነካት ሐፍረቷ እንደ በረዶ ተኖ ጠፋ፡፡ ስለዚህም ቀድሞ ወደምታፍራቸው ሰዎች በመሄድ “አንድ ነብይን ትመለከቱ ዘንድ” ሳይሆን “ያደረግሁትን ሁሉ፣ ምሥጢሬን ሁሉ የነገረኝን ሰው ትመለከቱ ዘንድ ኑ” እያለች ሕዝቡን ጠራቻቸው፡፡ እነርሱም መጡ፡፡ ትጋቷ እንዴት ድንቅ ነው? ቅናቷ እንዴት ግሩም ነው? ዛሬ የዚህችን ሴት ዜና መዋዕል ከመናገር በላይ እኛ ምን እንማራለን? ምን ያህል ቀናተኞች እንሆን? የራሳችንን ጨምሮ ምን ያህል ነፍሳት በእጃችን እንዳሉ እናውቅ ይሆን? ወንድሞቼ “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን፤ ያደረግሁትን ሁሉ የፋቀልኝን፤ በነጻ ሥርየተ ኃጢአት የሰጠኝን፤ በነጻ ልጅነት የሰጠኝን፤ በነጻ የራሱን ሥጋና ደም የሰጠኝን… ትመለከቱ ዘንድ ኑ” ብለን የምንመሰክር ስንቶች እንሆን? መክሊታችንን የቀበርን ስንቶች እንሆን? … መጽሐፍ “ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ?” ይላል… ወንድም እኅቶቼ! የምናውቃትን ያህል ከመመስከር ወደኋላ አንበል፡፡ የታመመን ሰው ሕክምና መውሰድ ያለብንን ያህል እንዲሁ ራሳችንን ጨምሮ ብዙዎችን ከመድኃኒተ ነፍሳቸው ጋር ልናገናኛቸው ያስፈልጋል፡፡ ይህን እንድናደርግ እኛን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount