Wednesday, May 2, 2012

=+=እናንተ ደካሞች… /በቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ/=+=

እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡- “እናንተ ኃጢአት ሸክም የሆነችባችሁ፣ እናንተ ጭንቀት አላኖር አላስቀምጥ ያላችሁ፣ እናንተ ሐዘን የደቆሳችሁ፣ እናንተ ትእዛዛቴን በመተላለፍ ቅስማችሁ የተሰበራችሁ፣ እናንተ በሐፍረት ካባ ተከናንባችሁ የምቆዝሙ፣ እናንተ ከእንግዲህ ወዲህ አበቃልኝ በቃኝ ብላችሁ ያንገሸገሻችሁ፣ እናንተ… እናንተ ለመናገር እንኳን ድፍረት ያጣችሁ… ምንም እንኳን ዝሙት ብትሠሩም፣ ምንም እንኳን ዋሽታችሁ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን ሰርቃችሁ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን መናገር የማትችሉት ከባድ የምትሉት ኃጢአት ብትሠሩም፣ ምንም እንኳን “ከእንግዲህ ወዲህ በቃ እግዚአብሔር ይቅር አይለኝም” ብትሉም የእኔ ፍቅር፣ የእኔ ቸርነት ይህን ሁሉ ኃጢአታችሁ - ይህን ሁሉ ሸክማችሁ - ይህን ሁሉ ሐዘናችሁ - ይህን ሁሉ ከባድ የምትሉትን ነገራችሁ መደምሰስ የሚችል ነውና ኑ፡፡ ኑና ላሳርፋችሁ፤ ኑና ስለ እናንተ የቆሰለውን እጄ ተደገፉ፤ ኑና ፍቅሬን ቅመሱ፤ ኑና ቸርነቴን አጣጥሙ፤ ኑና ሸክማችሁን ሁሉ በእኔ ላይ አራግፉ፡፡ ብቻ እናንተ ፈቅዳችሁ ኑ እንጂ ከእኔ ዓቅም በላይ የሆነ ሸክም የለባችሁምና አትስጉ፡፡ ኑና ሥርየተ ኃጢአትን ልስጣችሁ፤ ኑና ዕረፍተ ነፍስን ሰጥቼ ላሳርፋችሁ፤ ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንኳ እንደ አመዳይ አነጻላችኋለሁ፤ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ አጠራላችኋለሁ፡፡ ስለዚህ ኃጢአታችሁን እየቆጠራችሁ ከምትቆዝሙ ቀና በሉና ወደ እኔ ኑ፡፡ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና ልጆቼ ወደ እኔ ቅረቡ፡፡ እኔም ልቅረባችሁ፡፡ “ቀንበሬን ተሸከሙ” ስላችሁ በሩቁ አትፍሩኝ፡፡ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀሊል ነውና፡፡ ደግሞም ይህ ቀንበር አንገታችሁን ለማለዘብ (ለመላጥ) ሳይሆን በቀጭኒቱ መንገድ ወደ ግራም ወደ ቀኝም ሳትሉ እኔ ወዳዘጋጀሁላችሁ ርስት መንግሥት የምታደርስ ናትና በሩቁ አትፍሯት፡፡ ስለዚህ እናንተ ደካሞች፣ እናንተ ዓቅመ ቢሶች፣ እናንተ ከእኔ ውጪ ምንም ማድረግ የማትችሉ በገዛ ደሜም የገዛኋችሁ ልጆቼ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም ማዳን ብቻ ሳይሆን አሳርፋችኋለሁ፡፡”

1 comment:

FeedBurner FeedCount