Thursday, January 2, 2014

ነቢዩ ዕንባቆም

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ ፲፰ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡-በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ዕንባቆም ማለት ማቀፍ ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔርን በጸሎት አቅፎታልና እንዲኽ ተብሏል፡፡ ሊቃውንት እንደሚመሰክሩት ነቢዩ ዕንባቆም ያላ ገባ ድንግል ሲኾን የቤተ መቅደስ ዘማሪ ነበር /ዕን.፫፡፩/፡፡

Thursday, December 26, 2013

ነቢዩ ናሆም

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ ፲፯ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
“ናሆም” ማለት “መጽናናት” ማለት ነው፡፡ ብዙዎቹ ነቢያት የተላኩት መንፈሳዊነት በቀዘቀዘበት ወራት ነው፡፡ የሕዝቡ ኃጢአት ጽዋው ሞልቶ ነበር፡፡ የነቢያቱ መምጣት ዋና ዓላማም ሕዝቡ ከዚኽ ኃጢአት ለመመለስና ካልተመለሰ ግን እግዚአብሔር በእነርሱ ላይ ሊያመጣ ያለውን ፍርድ ለማስታወቅ ነው፡፡ ጨምረዉም ግን “አጽናኑ ሕዝቤን አጽናኑ” ተብሎ እንደተጻፈ /ኢሳ.፵፡፩/ ለሕዝቡ ተስፋ ድኅነትን ይሰጡ ነበር፡፡ ናሆምም ይኽን የነቢያት ተልእኮ የሚያሳይ ስም ነው፡፡ ምክንያቱም በመጽሐፉ ምንም እንኳን ሕዝቡ ለመጥፋት ሳይኾን ለቁንጥጫ ወደ ምርኮ እንደሚኼዱ ፈቃደ እግዚአብሔር ቢኾንም እግዚአብሔር ራሱ ጠላቶቻቸውን አጥፍቶ እንደሚያድናቸውም ጨምሮ ተናግሯል፡፡ “ለደም ከተማ ወዮላት!” /፫፡፩/፤ “እነሆ የምስራችን የሚያመጣ ሰላምንም የሚያወራ ሰው እግር በተራሮች ላይ ነው” በማለት የገለጻቸው ቃላት ይኽን የሚያስረዱ ናቸው፡፡

Tuesday, December 24, 2013

ነቢዩ ዮናስ

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ ፲፮ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 “ዮናስ” ማለት “ርግብ” ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም እንደ ቅዱስ ጀሮም ትርጓሜ “ስቃይ” ተብሎም ይተረጐማል፡፡ ይኸውም ተልእኮውን የሚገልጥ ነው፡፡ ነቢዩ ዮናስ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በዓሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ አድሮ እንደ ወጣ ኹሉ፥ የደቂቀ አዳምን ሕማም ለመሸከም መጥቶ የተሰቃየው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር አድሮ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷል፡፡ ስለዚኽ የነቢዩ ዮናስ እንዲኽ በዓሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት መቆየት የጌታችንን ሞትና ትንሣኤ በጥምቀት ተካፋዮች ለሚኾኑ ኹሉ በርግብ የተመሰለውን መንፈስ ቅዱስ እንደሚቀበሉና ለዚያ የተዘጋጁ እንዲኾኑ ማዘጋጀት ማለትም ማወጅ ነበር ማለት ነው /ማቴ.፲፪፡፴፱-፵/፡፡
 ነቢዩ ዮናስ ነገዱ ከነገደ ይሳኮር ወገን ሲኾን አባቱ አማቴ እናቱም ሶና ይባላሉ፡፡ በአይሁድ ትውፊት እንደሚነገረው ደግሞ ዮናስ ነቢዩ ኤልያስ ከሞት ያስነሣው የሠራፕታዋ መበለት ልጅ ነው /፩ኛ ነገ.፲፰፡፲-፳፬/፡፡ 

ነቢዩ አብድዩ

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ታኅሳስ ፲፭ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 “አብድዩ” ማለት “ገብረ እግዚአብሔር - የእግዚአብሔር አገልጋይ” ማለት ነው፡፡ ይኽ ስም በዘመኑ የታወቀ ስም ነበር፡፡ ነቢዩ አብድዩ ነገዱ ከነገደ ኤፍሬም ሲኾን አባቱ አኪላ እናቱም ሳፍጣ እንደሚባሉ የቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ያስረዳል፡፡
 ነቢዩ አብድዩ የአክአብ ቢትወደድ ነበር፡፡ ኤልዛቤል ነቢያት ካህናትን ስታስፈጃቸው ኃምሳውን በአንድ ዋሻ ኃምሳውን በአንድ ዋሻ አድርጐ ልብስ ቀለብ እየሰጠ ይረዳቸው የነበረውም ይኸው ነቢይ ነው /፩ኛ ነገ.፲፰፡፫-፲፫/፡፡ አክዓብ ሞቶ አካዝያስ ከነገሠ በኋላም አብድዩ ቢትወደድ ኾኖ ኖሯል፡፡
 የመጽሐፉ የአንድምታ ትርጓሜ መቅድም እንደሚነግረን ነቢዩ አብድዩ ከጨዋነት ወደ ነቢይነት የተመለሰው በነቢዩ ኤልያስ አማካኝነት ነው፡፡ በመጽሐፈ ነገሥት ካልዕ ምዕራፍ ፩ ከቊጥር ፲፫ ላይ የተጠቀሰውና ንጉሥ አካዝያስ የላከው ሦስተኛው አለቃም ይኸው አብድዩ ነው፡፡

FeedBurner FeedCount