Friday, May 18, 2012

=+=ድንግል ማርያም በቅ/ገብርኤል ሠላምታ (ክፍል ሁለት)=+=በመምህር ቃለአብ ካሳዬ=+=


ያለፈው ክፍል
ድንግል ማርያም በቅ/ገብርኤል ሠላምታ (ክፍል 1)

አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ

            ይህን የመልአኩን ቃል ቅ.ኤልሣቤጥም ሳትጨምር ሳትቀንስ ደግመዋለች (ሉቃ 1.47)። የድንግል ማርያም ከሴቶች ሁሉ ተለይቶ መባረክ በቅ.ገብርኤልና በቅ.ኤልሳቤጥ መመስከሩ ይህ እውነት በሠማይና በምድር የጸና መሆኑን ያሳያል። ገብርኤል ከሰማይ ኤልሳቤጥ ከምድር ለሆኑት ወኪል ናቸውና።

     አንዳንዶች ከሴቶች መካከል ማለት “እንደሴቶች ሁሉ” ወይም “ከእነርሱ እንደ አንዱ” ማለት ነው። ከዚህ ውጭ “ ተለይታ” የሚል ሐረግ ባለመኖሩ ከአማኞች ጋር የምትቆጠር አንድ ተራ ግለሰብ ናት ብለዋል። ታድያ እንደሌሎች ሴቶች ከሆነች ሌሎች ሴቶች ይህን ብሥራት ለምን አንደ እርሷ አልተቀበሉም?

  ከሴቶች ተለይታ የመባረኳ ምስጢር:-

  • ሌሎች ሴቶቸ ቢወልዱ፣ ፃደቃን ሰማዕታትን ነው ፣እርሷ ግን የወለደችው የእነርሱን ጌታ ነው።
  • ሌሎች ድንግል ቢሆኑ እስከጊዜው ነው፣ኋላ ተፈትሆ/ድንግልናን ማጣት/አለባቸው። እርሷ ግን በጊዜው ሁሉ ድንግል ናት።
             በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንዲህ የሚል ጽሑፍ አለ:-“እነዚህ ሁሉ ከሴቶችና ከኢየሱስ እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው በፀሎት ይተጉ ነበር።” (ሐዋ 1፡14) ጸሐፊው ሐዋርያው ሉቃስ የኢየሱስ እናት እንደሌሎች ሴቶች ብትሆን “ ከሴቶች ጋር” ይል አልነበረምን? ከሴቶችተለይታ የተባረከች በመሆኗ ግን “ ከሴቶችና ከኢየሱስ እናት” ብሎ ለይቶ ፃፈ።

አርሷም ባየቸው ጊዜ ከንግግሩ በጣም ደነገጠቸና ይህ አንዴት ያለ ሠላምታ ነው ብላ አሰበች ድንጋጤ የህሊና ፤ ፍርሃት የልቦና፣ ረዓድ የጉልበት ነው። ድንግል ማርያም የደነገጠችው ከመልአኩ ንግግር የተነሳ በመሆኑ“ ከንግግሩ በጣም ደነገጠችና” የሚል ቃል እናነባለን። የተነገረን ቃል ሁሉ እንደወረደ መቀበል ከቶ መንፈሳዊነት አይደለም። ይልቁንም“ይገባኛል ወይ?”   ማለት ይገባናል። በደነገጡበት ሰዓት ማሰብ ከባድ ቢሆንም ድንግል ማረያም ግን “ ……ብላ አሰበች” ይላል። ድንጋጤ የህሊና ነዉና በህሊናዋ ጠየቀች ማለት ነዉ።  እንግዲያውስ ድንጋጤዋ ከእምነት ማነስ ሳይሆን “እንዴት ያለ ሰላምታ ነው?” ከሚል ጥልቅ መገረም ነው። የሚገባትን የክብር ሰላምታ ቆም ብላ ከመረመረችው፣ የማይገባቸውን ምስጋና  ሳይመረምሩ ለሚቀበሉ፣ በአሚና ዝማሬ በደብተራ ቅኔ ለሚኮፈሱ ይህ ተግሣጽ  ነው።!

 መልአኩም እንዲህ አላት፡- ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አግኝተሻልና አትፍሪ!

ፍርሃት አርቆ መናገር ለመልአክ አዲስ ባለመሆኑ ሲሆን ዋናው ግን ነደ እሳትን ብሩህ መለኮትን ትሸከሚያለሽና አትፍሪ ሲላት ነው።

እነሆም ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅም ትወልጂያለሽ፣ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ !

ጸንሳ ወንድ ልጅ መውለዷ ቀድሞም በትንቢት በሰፊው ተጠቁሟል። (ት.ኢሳ.7፡14) (ት.ኢሳ 9/6)። መልአኩ ግን የዚህ ወንድ ልጅ ስሙ ኢየሱስ መሆኑን ነገራት። ኢየሱስ ማለት “መድሃኒት” ማለት ነው። መድሃኒትነቱ ለ^ጢአትም፣ ለሞትም ነው! ይህን ስም ተሸክሞ ታምሞ  የማይታከም፣ ሞቶ የማይነሳ ማንም የለም!

   ኢየሱስ የሚለው ክቡር ስሙ
  •  ከስም ሁሉ በላይ የሆነ (ፊሊ 2፡10)
  • ከሰማይ በታች እንድንድንበት ዘንድ የተሠጠ ( ሐዋ4፡12)
  • ጉልበት ሁሉ የሚሰግድለት (ፊሊ 2፡10)
  • ምላስ ሁሉ የሚመሰክርለት (ፊሊ2፡11)
  • ተጠርቶ የሚለመን (ዮሐ14፡14)
  • የ^ጢአት ሥርየት የሆነ (ሐዋ2.38) (ሐዋ3፡16)
  •  ብዙ መከራ የሚጠራ (ማቴ 5፡11)
  • ዘወትር የምናጌጥበት (ራዕ7:5)
  • እንዲሁም የሚያጸድቀን ነው (ሮሜ 10፡13)
እርሱም ታላቅ ይሆናል! የልዑል ልጅ ይባላል።

አርሱም ታላቅ ይሆናል:- እርሱ ቀድሞም ታላቅ ነው! ተንቆ የነበረው የእኛን ማንነት ሲዋሐድ ያገኘነውን ክብር ለመግለጽ ግን ታላቅ ይሆናል አለ!
የልዑል ልጅ ይባላል:- እርሱ ቀድሞም የልዑል ልጅ ነው፣ እርሱ የሰው ልጅ ሲሆን፣እኛም የልዑል ልጆች መሆናቸንን አረጋገጠልን። እርሱ እኛ ጋር ሲሆን እኛም እርሱ ጋር ሆነናልና ከራሱ ጋር ይጠራናል!

ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋነ ይሰጠዋል!

 የዳዊትን ዙፋን የማይሻ ፣የእሳት ዙፋን ጥሎ የመጣ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል ማለት አብ ክርቶስን የዳዊትን ሥጋ ያዋሕደዋል ማለት ነው። ክርሰቶስ በዳዊት ሥጋ የዳዊት ልጅ ነውና። አብ በማዋሐድ ፣ ወልድ በመዋሐድ፣ መንፈስ ቅዱስ በማጽናት በድንግል ማርያም ረቂቅ ሥራ ተፈጽሟል። መዝ (88)
በያዕቆብ ቤትም ለዘለዓለም ይነግሳል

       ያዕቆብ አስራኤል ተብሏል (ዘፍ 32:22)። ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል
       ዘሥጋ ለጊዜው በትንቢት፣ በእስራኤል ዘነፍስ  (በክርስቲያኖች) ላይ ግን በፍቅር    
       ለዘለዓለም ነግሷል።
      ለመንግሰቱም መጨረሻ የለውም

ይህ ቃል አሰቀድሞ በነቢዩ በዳንኤል “በወገኖችና አሕዛብ ላይ ልዩ ቋንቋም  የሚናገሩ ሁሉ ይገዙለት ዘንድ ግዛትና ክብር መንግስትም ተሰጠው፣ ግዛቱም የማያልፍ የዘለዓለም ግዛት ነው። መንግስቱም የማይጠፋ ነው”። ተብሎ ተነግሯል (ት.ዳን 7፡13-14)

ማርያምም መልአኩን ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል? አለችው።

በአካልም በአሳብም ወንድ የማታውቅ መሆኗን የሚያሳይ የከበረ ቃል ነው።እኔ አንዱንም ሳላሰብ አንተ ብዙ ነገረ አልከኝ፣ ምድር ያለ ዘር፣ ሴት ያለወንድ ዘር እንዴት ይሆናል? አለችው “ እንዴት?” ስትል መልአኩ እንደካህኑ ዘካርያስ አልገሠፃትም! ምክንያቱም:-

    1ኛ. ካህኑ ዘካርያስ ካረጀሁ በኋላ እንዴት አወልዳለሁ? ቢል ካረጀ በኋላ የወለደ
      አባቱ አብርሃም ነበረና ማመን ይገባው ነበር። ድንግል ማርያም ግን
      በድንግልና ወልዶ የታየ ምሳሌ የሌላት ከመሆኑም ባሻገር ይህ ነገር
      ከመልአኩ ዕውቀት በላይ በመሆኑ ነው።
     2ኛ. መልአኩ በፊቱ ቆሞ  የሚያገለግለውን ጌታ እርሷ ወልዳው ያገለግላታልና በማዕረግ ጉዳይ ያከብራታል (ሉቃ 1፡19)  (ሉቃ2፡51)።

  “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፣ የልዑልም ^ይል ይጸልልሻል፣ ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፣ እነሆ ዘመድሽ ኤልሣቤጥ እርሷ  ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ጸንሣለች። ለእርስዋ መካን ትባል ለነበረችው ይህ ሰደስተኛ ወር ነው።”

የመልአኩ መልእክት ለኤልሣቤጥ ባለፈ ሠዓት፣ በስተርጅናዋ ለማሀፀኗ ልጅን የሰጠ አንቺንም በድንግልና ሳለሽ ለማህጸንሽ ልጅ ይሰጣል የሚል ነው። የቅ.ኤልሳቤጥ በስተርጅና የድንግል ማርያም በድንግልና የመውለድ ጸጋ የሆነው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና

     ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና:-

የመልአኩ ማሳረጊያ ቃል፣ ማሸነፊያ ብርታት የሆነው ይህ ቃል ነው። ሰው የሚቻለውን ይችላል። አግዚአብሔር የማይቻለውን ይችላል። ሰው እግዚአብሔር አሰችሎት ይችላል። እግዚአብሔር ግን ማንም ሳያስችለው ይችላል!
ማርያምም እነሆኝ የጌታ ባርያ እንደቃልህ ይሁንልኝ
የጌታ ባርያ ነኝ የሚል ፈቃዱን በእግዚአብሔር ፈቃድ የሚለውጥ ነው። እንደቃሌ ሳይሆን እንደቃልህ፣ እንደወሰድሁት ሳይሆን እንደሰጠኸኝ፣ እንደአሳቤ ሳይሆን እንደ ፈቃደህ፣ እኔ ላድርግ ሳይሆን ይሁንልኝ፣ እንደመሰለኝ ሳይሆን እንደወሰንከው፣ ስማኝ ሳይሆን ልስማህን የሚያስቀድም ነው!
                                                                                                                          ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Thursday, May 17, 2012

ካህናተ ደብተራ በዲ/ን ዳንኤል ክብረት=+=


«እናንተ ደብተራ ከምትባሉት በቀር ይህንን ሁሉ ያደረገ ማነው?ታመሰግኑታላችሁ፣ ታወድሱታላችሁ፣ እንዳንተ ያለ ኀያል ማነው? ትሉታላችሁ፤እንዳንተ ያለ ድል አድራጊ፣ እንዳንተስ ያለ ለጋሥ በሁሉ ዘንድ ወዴት አለ?እንዳንተ ያለስ ምጽዋት ሰጭ የት አለ? ትሉታላችሁ፡፡ እንዲህ ስታመሰግኑትምበኀጢአት ላይ ኀጢአትን ይጨምራል፡፡»
ይህንን ቃል ከዛሬ ሰባት መቶ ዓመታት በፊት የተናገረው ታላቁ ተጋዳይ አባት አባ በጸሎተሚካኤል ዘደብረ ጎል ነው፡፡ ንጉሥ ዓምደ ጽዮን ከክርስትና ሕግ ውጭ የአባቱን ሚስትበማግባቱ እንደ ዮሐንስ መጥምቅና እንደ ዮሐንስ አፈወርቅ ሳይፈራና ሳያፍር ፊት ለፊትበመገሠፁ ብዙ መከራ ደረሰበት፡፡ ተገረፈ፤ ታሠረ፤ ተሰደደም፡፡
አስቀድማ የንጉሡ ሚስት የነበረች በኋላ ደግሞ ንጉሡ ለአንዱ ወታደሩ የሰጣት አንዲት ሴትነበረች፡፡ ይህቺ ሴት ይህንን ሕይወት ንቃ ንስሐ ገባችና ሥጋወደሙ ተቀበለች፡፡ ንጉሥዓምደ ጽዮን «ሂዳችሁ አምጧት፤ እኔም በመኝታዬ አረክሳታለሁ» ብሎ በድፍረት ተናገረ፡፡መልክተኛ ወደ ሴቲቱ ሲሄድ እርሷ ወደ አቡነ በጸሎተ ሚካኤል ዘንድ ላከች፡፡

አቡነ በጸሎተ ሚካኤል ልጆቹን እንዲህ አላቸው «ተነሡ እግዚአብሔር ሥራ እንዲሠራእንለምነው፡፡ ክውስጣዊ ልብሳችሁ በቀር ሌላውን አውልቁ፡፡ በፊቱም እያለቀስንእንለምነው»፡፡ ሌሊቱን ሙሉ በዕንባና በስግደት፣ በጸሎትና በማዕጠንት እግዚአብሔርንሲለምኑት አደሩ፡፡ ሲያለቅስ መሬቱ የሚረጥብ አለ፡፡ ሲሰግድ መሬቱ የሚጎደጉድ አለ፡፡ደረቱን ሲደቃ ውጭ ድረስ የሚሰማ አለ፡፡ ሲያጥን ዕንባው እሳቱን የሚያጠፋው አለ፡፡
ሌሊት ንጉሡ በከባድ ሕመም ታመመ፡፡ ነፍሱም ልትወጣ ደረሰች፡፡ ያን ጊዜ ባለሟሎቹቀረቡ፡፡ እርሱም «ይህ ሕመም በምን ምክንያት እንደ መጣ አውቄዋለሁ፤ ያቺን የበጸሎተሚካኤልን ልጅ ላረክሳት በመፈለጌ ነው፡፡ አሁንም ሂዱና ይቅር በለኝ በሉት» ብሎ በቤተመንግሥቱ የሚያገለግሉትን ካህናት ላካቸው፡፡
ካህናቱ ወደ አባ በጸሎተ ሚካኤል ሲደርሱ «ልጆቼ ተነሡ እግዚአብሔር ሰምቶናል፡፡ልብሶቻችሁን ልበሱ፤ መልክተኞችም መጥተዋል» አላቸው፡፡ እነርሱም ተነሥተው ከመቅደስሲወጡ የንጉሡን መልክተኞች አገኟቸው፡፡ መልክተኞቹም የንጉሡን መልክት ነገሩት፡፡ አባበጸሎተ ሚካኤልም «እግዚአ ብሔር ይቅር ይበልህ በሉት» አላቸው፡፡ የንጉሡን አገልጋይካህናት ግን እጅግ ወቀሳቸው፡፡
አባ በጸሎተ ሚካኤል የወቀሳቸው ካህናት በዚያ ዘመን «ካህናተ ደብተራ» ይባሉ ነበር፡፡ስማቸው የተወሰደው በንጉሡ ቤተ መንግሥት የምትገኘውንና በድንኳን ያለቺውን ቤተ ክርስቲያንስለሚያገለግሉ ነው፡፡ ነገሥታቱ በየሀገሩ ስለሚዘዋወሩ የድንኳን ቤተ ክርስቲያን ነበራቸው፡፡እዚያ ካህናት ይመደባሉ፡፡
የእነዚህ ካህናት ጠባይ በሌላው ቦታ ከነበሩት ካህናት ጠባይ ይለይ ነበር፡፡ ካህናተ ደብተራየሚታወቁባቸው ጠባያት ነበሯቸው፡፡ የመጀመርያው ጠባያቸው በገዳም ከሚኖሩት ቅዱሳንአበው ጋር አለመስማማታቸው ነው፡፡ ለእነርሱ ገዳማዊ ሕይወት ጊዜ ማጥፋትና ራስን ማሞኘትነው፡፡ በገዳም ያሉ አባቶቸንም በትኅትናቸው ምክንያት ይንቋቸው ነበር፡፡ እነርሱን ማሳጣትናመክሰስ ብሎም ከየገዳማቸው ማሳደድ የዘወትር ተግባራቸው ነበር፡፡ ገዳማቱ ሲፈቱና ማኅበረመነኮሳቱ ሲበተኑ ምንም ዓይነት ቁብ አይሰጣቸውም ነበር፡፡ እንዲያውም አንዳንድ ጊዜየንጉሡ ወታደሮች የሚያዝኑላቸውን ያህል ካህናተ ደብተራ ለገዳማውያን አባቶች አያዝኑም፡፡ ወደ ንጉሡ ዘንድ ደርሰው ጉዳያቸውን እንዳያስፈጽሙ ከጠባቂዎቹ ይልቅ የሚያስቸግሯቸውካህናተ ደብተራ ነበሩ፡፡
ሁለተኛው ጠባያቸው ደግሞ ማንኛውንም ነገር ከጥቅም ጋር ማገናኘታቸው ነው፡፡ የቤተክርስቲያን ሥርዓትና ሕግ፣ የእግዚአብሔር ቁጣና ቅጣት አይታያቸውም፡፡ ከንጉሡ ማዕድእየበሉና ፍርፋሪ እየለቀሙ፣ በንጉሡም ካባና ላንቃ እየተሸለሙ ስለሚኖሩ የሚሠሩትየሚገባቸውን ሳይሆን የሚያበላቸውን ነው፡፡ በቤተ መንግሥቱ ያገኙትን ክብርና ማዕድዳያጡ ሲሉ ማንኛውንም  ሃይማኖታዊ የሆነ ተግባር ከማድረግ አይመለሱም፡፡
በገድለ አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ሊባኖስ ላይ እንደ ተጻፈው ዓምደ ጽዮንንም ሆነ ልጁን ሰይፈአርእድን ትክክል ያልሆነ ትምህርት አስተምረው ያሳሳቱት ካህናተ ደብተራ ናቸው፡፡ አቡነፊልጶስ ዘደብረ ሊባኖስ ወደ ዓምደ ጽዮን ገብተው ለምን ይህንን ጥፋት እንዳጠፋና የአባቱንሚስት እንዳገባ ሲጠይቁት « ዐዋቂዎች የሆኑ ካህናት እርሷን ካላገባህ መንግሥትህ አይጸናምብለውኝ ነው» ነበር ያላቸው፡፡ ከካህናተ ደብተራ አንዱ የነበረው እወደድ ባዩ ዘአማኑኤልየተባለ ሰው ከንጉሥ ዓምደ ጽዮን በኋላ የነገሠውን ሰይፈ አርእድን በተመሳሳይ ስሕተትአሳስቶት ነበር፡፡ «ከጥቂት ጊዜም በኋላ ዘአማኑኤል የሚባል አንድ ሰው ተነሣ፡፡ ይህምበግብር ሳይሆን በስም ነው፤ እርሱ ንጉሡን እንዲህ ሲል አሳስቶታልና፡ አንተ ንጉሥ ነህናበአንዲት ሚስት ልትኖር አይቻልህም፤ ንጉሥማ ሦስት ሚስት እንዲያገባ ታዝዞለታል ብሎምአስተማረው» (ገድለ አቡነ ፊልጶስ፣ ገጽ 225)
ካህናተ ደብተራ ንጉሡን የሚያስደስትና ጥቅማቸውን የሚያስከብር ከመሰላቸው ከንጉሡ በላይምሄደው ግፍ ከመፈጸም አይመለሱም ነበር፡፡ በሰይፈ አርእድ ዘመነ መንግሥት ተመሳሳይስሕተት መሠራቱን አይተው አበው ከየአቅጣጫው መጥተው ሲገሥፁት አቡነ አኖሬዎስ ንጉሡንበኃይል ተናገረው፡፡ ይህንን ያየው የንጉሡ ማዕድ ባራኪ ካህን ወይም ቄስ ሐፄ ከወታደሮቹተሽቀዳደመና አቡነ አሮንን በጥፊ መታው፡፡ ለምን እንደ መታው ገድለ አቡነ አኖሬዎስ ሲናገር«በንጉሡ ዘንድ ሊመሰገን ሽቶ» ይለዋል፡፡ ያን ጊዜም አቡነ አኖሬዎስ «ለምን ትመታኛለህ?ለሰው ከማድላት ለእግዚአብሔር ማድላት አይሻልህም ነበር አለው ይላል፡፡ ቄስ ሐፄው ግንያሰበውን ምስጋና አላገኘም፡፡ በአበው ኀዘን ምክንያት ወዲያውኑ ሞተ፡፡
የካህናተ ደብተራ ሌላው ጠባይ ደግሞ ወተቱን ማጥቆር ከሉን ማንጣት ነው፡፡ እውነትንየሚመዝኗት ከጥቅማቸው አንፃር ብቻ ስለነበረ ኃጢአት ሲሠራ እያዩ ጽድቅ ነው፤ ግፍሲፈጸም እያዩ ቅድስና ነው ማለት ይወዱ ነበር፡፡ ነገሥታቱና መኳንንቱ በበደል ላይ በደልእንዲጨምሩ ያደርጓቸው የነበሩትም እነርሱ ናቸው፡፡ ለዚህ ነው አቡነ በጸሎተ ሚካኤል ወደእርሱ ለማማለድ የመጡትን ካህናተ ደብተራ «እናንተ ደብተራ ከምትባሉት በቀር ይህንን ሁሉያደረገ ማነው? ታመሰግኑታላችሁ፣ ታወድሱታላችሁ፣ እንዳንተ ያለ ኀያል ማነው?ትሉታላችሁ፤ እንዳንተ ያለ ድል አድራጊ፣ እንዳንተስ ያለ ለጋሥ በሁሉ ዘንድ ወዴት አለ)እንዳንተ ያለስ ምጽዋት ሰጭ የት አለ? ትሉታላችሁ፡፡ እንዲህ ስታመሰግኑትም በኀጢአት ላይኀጢአትን ይጨምራል፡፡» ያላቸው በዚህ ምክንያት ነው፡፡
አንዳንዶቹ የካህናተ ደብተራ ወገኖች ሹመት እንጂ እምነት አልነበራቸውም፡፡ በገድለ አቡነአኖሬዎስ ላይ እንደ ግብጦን በተባለ ቦታ ንቡረ እድነት የተሾመ አንድ የካህናተ ደብተራ ወገንነበረ፡፡ ይህ ሰው ምንም ሳያደርገው በቅድስናው ብቻ አቡነ አኖሬዎስን ይጠላው ነበር፡፡
አንድ ቀን «ምን እንደምትሠራ ለማየት እመጣለሁ» ሲል ላከበት፡፡ ይህ ሰው ሹመት ሽልማትፈልጎ ንቡረ እድ ሆነ እንጂ እግዚአብሔርን እንኳን የማያመልክ ሰው ነበረ፡፡ ገድለ አቡነአኖሬዎስ እንዲህ ይላል «ቅዱሱም በዚያ በገዳሙ እያለ ስሙ ጳውሎስ የሚባል አንድ ሰውበትዕቢት «መጥቼ ሥራህን አያለሁ» ብሎ ወደ እርሱ ላከበት፡፡ ያም በስም መነኩሴና ንቡረእድ የሆነ፣ ከንጉሡም ዘንድ የተሾመ ነበረ፡፡ እርሱም ቤተ ክርስቲያንን አጠፋት፡፡ምእመናንንም አሳዘናቸው፡፡ የተላከውም መልክተኛ ለአባታችን ይህንን ነገረው፡፡ አባታችንምይህንን ሰምቶ «ኃጥእን እንደ አርዘ ሊባኖስ ከፍ ከፍ ብሎ አየሁት፤» ብሎ ተናገረ፡፡ ወደእግዚአብሔርም ስለ እርሱ ጮኸ፡፡ ያም በትዕቢቱ ሞትን አገኘ፡፡ ለቅዱሱም እንደ ሞተነገሩት፡፡ እርሱም «በተመለስኩ ጊዜ ግን አጣሁት» አለ፡፡ እርሱም «በምን ሞተአላቸው፡፡ እነርሱም «ሌሎች አማልክትን ያመልክ ነበር» አሉት፡፡ ቅዱስ አባታችንም መራርልቅሶን አለቀሰ፡፡ «ፈለግኩ ቦታውንም አላገኘሁትም» አለ፡፡
አንዳንዶቹ ካህናተ ደብተራ ክህነትን ለእንጀራ ማግኛና ለክብር መሸመቻ እንጂ አምነውበትየሚያገለግሉበት አልነበረም፡፡ ርስት ጉልት ስላለ፣ በንጉሡ ማዕድ ለመቅረብ ስለሚያስችል፣ልብስና መዓርግም ስለሚያሰጥ ነበር ወደ ክህነቱ የገቡት፡፡
ካህናተ ደብተራ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ለእንጀራና ክብር ማግኛ ብቻ እንጂ ለድኅነትስለማይ ጠቀሙበት አንዳንድ ጊዜ ነገሥታቱን ከአምልኮ እግዚአብሔር ወደ ጥንቆላ ይከቷቸውየነበሩት እነርሱ ነበሩ፡፡ በዐፄ ዳዊት ዘመን አባ ጊዮርጊስ ሲከራከራቸው የነበሩትና በኋላምበንጽሕናው ምክንያት ተመቅ ኝተው ወደ ዳሞት እንዲጋዝ ያደረጉት በጥንቆላ ሥራ ተሠማርተውየነበሩት ካህናተ ደብተራ ነበሩ፡፡
ካህናተ ደብተራ በዕውቀትና በቅድስና የሚበልጧቸውን አባቶችና ሊቃውንት አይወዷቸውም፡፡ቤተ ክርስቲያንን ለማበልጸግ፤ ለማደራጀትና ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት የሚጥር ሁሉጠላታቸው ነው፡፡ ግብጻዊው ጳጳስ አቡነ ያዕቆብ አቡነ ፊልጶስን ኤጲስ ቆጶስነት ሊሾመው ሲነሣበዋናነት የተቃወሙት ካህናተ ደብተራ እንደነበሩ ገድለ አቡነ ፊልጶስ ይነግረናል «እንደዚህአታድርግ፤ በአንድ ሀገር ሁለት ኤጲስ ቆጶስ ይሆናልን? ሕዝቡ ይከፋፈላል፤ የአንተም ክብርህይጠፋል፤ ምድረ ሼዋኮ ከፊል መንግሥት ናት፤ እንዴት እንደዚህ ትላለህ? ከኛ በኋላየሚመጣ ትውልድም ይህንን አይፈቅድም፤ ከኛም አስቀድሞ እንዲሁ ነበረ፡፡ እኛስ ከኛበፊት የነበሩ አበው ጳጳሳት ያላደረጉትምን አናደርግም፣ አንናገርምም» (ገድለ አቡነ ፊልጶስ፣ገጽ 197)
በወቅቱ የነበረውን የደቡቡን ክፍል ከአሥራ ሁለት ከፍሎ አሥራ ሁለት ወንጌላውያንን የሾመውንበሰሜኑ ክፍልም ሐዋርያትን ያሠማራውን ግብፃዊውን አቡነ ያዕቆብን ካህናተ ደብተራአልወደዱትም፡፡ የስብከተ ወንጌል መስፋፋትና የሕዝቡ ማወቅ ለእነርሱ የግብዝነትናየኃጢአት ሥራ ዕንቅፋት ይሆናል ብለው አሰቡ፡፡ በዚህም የተነሣ ይህንን የስብከተ ወንጌልአደረጃጀትና ሥምሪት ማጥፋት እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ በዚህም ምክንያት ዘአማኑኤል ንጉሡአቡነ ያዕቆብን ወደ ግብጽ እንዲመልሰው መከረው፡፡ አቡነ ያዕቆብ ስላወገዘውም በለምጽተመትቶ ሞተ፡፡ አቡነ ያዕቆብም ወደ ግብጽ ተመለሰ፡፡
በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ የእውነተኞቹ አባው፣ ሊቃውንትና ካህናት አገልግሎትና ትሩፋትለቤተ ክርስቲያን ብልጽግና እንዳይሰጥ ሲያሰናክሉና ለእውነት ዕንቅፋት ሲሆኑ የኖሩት ካህናተደብተራ ናቸው፡፡ እንክርዳዱ ከስንዴው ጋር አብሮ እስከ መከር ይኖራልና የካህናተ ደብተራጠባይና አሠራር ዛሬም ቤተ ክርስቲያንን ሲያውካት ይኖራል፡፡ እንደ አቡነ አሮን፣ እንደ አቡነበጸሎተ ሚካኤል እንደ አቡነ ፊልጶስና እንደ አቡነ አኖሬዎስ ያሉ ጀግኖችን እስክታገኝድረስ::  
(Source: danielkibret.com)

FeedBurner FeedCount