Monday, June 25, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል ሁለት!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
    በክፍል አንድ ትምህርታችን ከሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ስለ ሊቀ ካህናት በስፋትና በጥልቀት የጻፈልን የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ እንደሆነ፤ የዚህ ምክንያትም ምን እንደሆነ እና  ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህን ትምህርት አብዝታ እንደምታስተምር ከአዋልድ መጻሕፍቶቿ ጠቅሰን ነበር ያቆምነው፡፡ ለዛሬ ደግሞ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ እግዚአብሔር ሥርዓት ከሰዎች ተመርጠው ከሚሾሙት የብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናት ፍጹም የሚለይባቸውን ነጥቦች ማሳየት እንጀምራለን፡፡ አንባብያን ትምህርቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር እያመሳከሩ ቢያነቡት የበለጠ ይጠቀማሉ፡፡

1. የሚምር ሊቀ ካህናት ነው፡፡ መጽሐፍ ይህን ሲመሰክር፡- “የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም፡፡ ስለዚህ የሕዝብን ኃጢአት ለማስተስረይ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ የሚምርና የታመነ ሊቀ ካህናት እንዲሆን በነገር ሁሉ ወንድሞቹን መምሰል ተገባው” ይላል /ዕብ.2፡16-17/፡፡ አዎ! የዘመናት ጌታ እንደ ሰዎች ዘመን ተቈጠረለት፤ በልደት በሕማም በሞት ወንድሞቹን መምሰል ተገባው፡፡ ባሕርያችንን የተዋሐደው ሌላ ምንም ምን ምክንያት የለውም፡፡ እኛን ከማፍቀሩ የተነሣ ዘመድ ሊሆነን አንድም እኛን ይቅር ለማለት ኃጢአታችንንም ለማስተስረይ እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል፡- “ተመለከተን፤ እነሆም ጠላቶቹ ሆነን ተገኘን፡፡ ወደ እርሱ ያቀርበን ዘንድ የሚችል ኪዳንም ቢሆን መሥዋዕትም ቢሆን ፈጽሞ አልነበረንም፡፡ ስለዚህም አዘነልን፤ ራራልን፡፡ ከመላእክትም ይሁን ከኃይላት ወገን ሊቀ ካህናት አልሾመልንም፤ እርሱ አንዱ ወደዚህ ዓለም ወርዶ ባሕርያችንን ባሕርይ አድርጐ የሚምር ሊቀ ካህናት (አስታራቂ) ሆነን እንጂ” /ሃይማኖተ አበው 62፡13/፡፡ ይህም በመዋዕለ ሥጋዌው ተመልክተነዋል፡፡ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ሲፈርዱባቸው የነበሩ ሰዎች፣ “Public Sinners” ብለው ከማኅበረሰቡ ያገለሉዋቸውን ሰዎች አዛኙ ሊቀ ካህናችን ሲያገኛቸው ግን “እኔም አልፈርድብሽም”፤ “ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል” ይላቸዋል /ዮሐ.8፡11፣ ሉቃ.7፡48/፡፡ ስለዚህ ሊቀ ካህናችን መሓሪ ነው፡፡

2. የታመነ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ሊቃነ ካህናት ይጐድላቸው ከነበረው ነገር አንዱ ታማኝነት ነበር፡፡ ለምሳሌ አሮንን ብንመለከት በእግዚአብሔር ፊት ታማኝነት ይጐድለው ነበር፡፡ መጽሐፍ ይህን ሲመሰክር፡- “እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን። በእስራኤል ልጆች ፊት ትቀድሱኝ ዘንድ በእኔ አላመናችሁምና ስለዚህ ወደ ሰጠኋቸው ምድር ይህን ጉባኤ ይዛችሁ አትገቡም አላቸው” ይላል  /ዘኅ.20፡12/፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የእኛን ኃጢአት ለማሥተስረይ ነውርን ንቆ መከራውን አቃሎ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ ሐፍረተ መስቀልን ይሁንብኝ ብሎ የተቀበለ ታማኝ ሊቀ ካህናት ነው /ዕብ.12፡2/፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ይህን ሲያብራራው፡- “በእውነት የአብርሃምን ባሕርይ ነሣ እንጂ የነሣው የመላእክትን አይደለም።  ስለዚህ የሕዝብን ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የሚምርና የታመነ ሊቀ ካህናት እንዲሆን በነገር ሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል ተገባው።  መከራ የሚቀበሉትን ሕዙናነ ልብ ይረዳቸው ዘንድ እርሱ ራሱ ተፈትኖ መከራን ተቀበለ። ስለዚህ፥ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ፥ የሃይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ፤ እርሱ ለሾመው የታመነ ነበረና” ይላል /Discourses against Arians, 2:8/፡፡

3. በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት የሚገቡት ወደ ምድራዊት ድንኳን ነበር፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በሰማያት ያለፈ (ውሳጤ መንጦላዕት የገባ) ትልቅ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ኢያሱ ወልደ ነዌ ሊቀ ካህናቱና ሌዋውያን ካህናቱ ከፊት ቀድመው ታቦቱ ሕጉን ተሸክመው ባይቀድሙ ኖሮ ሕዝቡን ፈለገ ዮርዳኖስን አሻግሮ ዕረፍተ ፍልስጥኤምን ባላወረሳቸው ነበር /ኢያሱ.3፡13/፡፡ ታላቁ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ደግ አስታራቂ ይሆነን ዘንድ ወደ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያትም ይዞን ለመግባት እንደ እነዚያ (የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት) ታቦት ሕጉን መሸከም አላስፈለገውም፡፡ እንደ ባሕርይ አምላክነቱ ወደ ገጸ አብ፣ ወደ እዝነ አብ አቀረበን እንጂ /ዕብ.4፡14/፡፡

4. በድካማችን የሚራራልን ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ለሚስቱት ሰዎች የሚራሩላቸው ራሳቸው ደግሞ በስንፍናቸው ኃጢአት ስለሚሠሩ ነው፤ የሰውን ድካም በራሳቸው ድካም ስለሚረዱት ነው /ዕብ.5፡2-3/፡፡ እንደዚያ ካልሆነ ግን ሰዎች ናቸውና ስሕተት የሠራው ሰው ኃጢአቱን ካልነገራቸው በቀር ምን ምን በደል እንደሠራ ማወቅ አይቻላቸውም፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ደክመን ለሠራነው ኃጢአት የባሕርይ አምላክ እንደመሆኑ ምን ምን ድካም እንዳለብንም ስለሚያውቅ ይራራልናል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን እነዚህን ሁሉ ሰው ሆኖ በገቢር አይቶአቸዋል፡፡ የእኛን ስደት ተሰዶ አይቶታል፤ የእኛ መሰደብ ተሰድቦ አይቶታል፤ የእኛ መወቀስ ተወቅሶ አይቶታል፤ የልጆቹ መገረፍ ተገርፎ ብቻ ሳይሆን ተሰቅሎ አይቶታል፡፡ “ስለዚህ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም” /ዕብ.4፡15/፡፡

       ይቆየን! (ሳምንት ይቀጥላል!)

Saturday, June 23, 2012

“የታመነ፣ የከበረና የተመሰገነ ስለሚሆን ስለ ዮሴፍ የምንናገረውን እንወቅ!” ቅዱስ ኤራቅሊስ

የታመነ፣ የከበረና የተመሰገነ ስለሚሆን ስለ ዮሴፍ የምንናገረውን እንወቅ፡፡ እርሱ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም የሚፈጸመውን ምሥጢር አላወቀምና፡፡
አገልጋይ የሆነለት ምሥጢር ምን እንደ ሆነ አላወቀም፤ ለእርሱ ከታጨችለት ከድንግል ነቢያት ስለ እርሱ የተናገሩለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ዘር እንዲወለድ አላወቀም፤ በነቢይ እንደ ተናገረ ሕፃን ያለ አባት ከድንግል እንዲወለድ አላወቀም፡፡ /ኢሳ.714 96-7 ዮሐ.146/
ከንጹህ ዘር የተፈጠረች ድንግል የእግዚአብሔር ማደርያ እንድትሆን አላወቀም፤ ዘላለም መለወጥ የሌለበት ዳግማይ አዳም ክርስቶስ ድንግልና ካላት ገነት እመቤታችን እንዲገኝ አላወቀም፡፡ /ዘፍ.927 መኃ.412/
ፍጡራንን ሁሉ የፈጠረ ክርስቶስ ያለ ዘር እንዲወለድ አላወቀም፤በምድራችን ታየተብሎ በነቢይ እንደ ተነገረና ዳግመኛም ምድር ፍሬን ትሰጣለች ተብሎ እንደ ተነገረ፡፡ ኢሳ.321-2 ዮሐ.14 ቆላ.115-18/
የድንግል ሆድዋ ገፋ፤ ያለ ዘር የፀነሰች የድንግልን የሆድዋን መግፋት ባየ ጊዜ የዮሴፍ ልቡ አዘነ፤ የንጽህት እመቤታችንን ምሥጢሯን ፈጽሞ መረመረና በማያውቀው ምሥጢር ፀንሳ ቢያገኛት በጽኑ ሐሳብ በማውጣት በማውረድ ተያዘ፡፡
ፀንሳ አገኛት፤ በዘር የፀነሰችም መሰለው፤ ከእርሷ የሚወለደው በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነውና አንተም እንደምትጠራጠረው አይደለምና ዮሴፍ አትፍራ ብሎ ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ እስኪነግረው ድረስ፡፡
ዮሴፍም ይህን በሰማ ጊዜ ለድንግል ሰገደ፤ ንጽህናዋንም አመነ፤ ነቢዩ አሳይያስ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙም አማኑኤል ይባላል ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ባሕርይ ጋር አንድ ሆነ ማለት ነው ብሎ የተናገረላት ድንግል እርሷ እንደ ሆነች አወቀ፡፡ /ማቴ.118-25 ሉቃ.126-39 ኢሳ.714/
(
ምንጭ፡ ሃይማኖተ አበው.4829-35)

Friday, June 22, 2012

“እኔ ነኝ አትፍሩ!” - የዮሐንስ ወንጌል የ28ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.6፡16-21)!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  ሕዝቡ ከበሉና ከጠገቡ በኋላ “ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነብይ ነው” ብለው ነበር /ቁ.14/፡፡ ስለዚህም የመሲሑ ክርስቶስ ዓላማ ስላልተረዱ ሊያነግሡት አስበው ነበር፡፡ እንደ እነርሱ ሐሳብ ያከበሩትና ከፍ ከፍ ያደረጉት መስለዋቸው ነው፡፡ እርሱ ግን እከብር አይል ክቡር፣ እነግሥ አይል ንጉሥ፣ ዓለምን በእጁ የጨበጠ፣ በፍቅሩም የሚመግባት፣ የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜም ሰውን ከወደቀበት ለማንሣት የባርያውን መልክ ይዞ የመጣ ልዑለ ባሕርይ ነው /መዝ.24፡1/፡፡ ስለዚህም በኃይል ነጥቀው ሊያነግሡት እንደ ፈለጉ አውቆባቸው ብቻውን ወደ ተራራ ፈቀቅ ሊል ወደደ፡፡ በክፍል 27 እንደተነጋገርነውም ፈቀቅ ማለቱ ፈርቶ አልነበረም፡፡ ይልቁንም “ሰው የማያነግሠኝ ልዑለ ባሕርይ ነኝ፤ አመጣጤም እናንተን ልጆቼና ብልቶቼ አድርጌ ወደ ሰማያዊው ቤታችሁ ለመውሰድ፤ ወደ ጥንተ ተፈጥሮአችሁ ለመመለስ እንጂ እዚህ ምድር ላይ ለመንገሥ አይደለም፤ እኔስ ከዓለም አስቀድሜ ንጉሥ ነኝ” ሲላቸው እንጂ /መዝ. 73፡12፣ Saint Augustine, On the Gospel of St. John, tractate 25:1-2/፡፡


  ከዚህ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ከዚህ አስተሳሰብ ይወጡ ዘንድ “በታንኳ ገብተው ወደ ማዶ እንዲቀድሙት ግድ አላቸው” /ማቴ.14፡22/፡፡ እርሱም ሕዝቡን አሰናብቶ ወደ ተራራ ፈቀቅ አለ፡፡ “በመሸም ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ወደ ባሕር ወረዱ፤ በታንኳም ገብተው በባሕር ማዶ ወደ ቅፍርናሆም ይመጡ ነበር፡፡ አሁንም ጨልሞ ነበር፤ ኢየሱስም ገና ወደ እነርሱ አልመጣም ነበር” /ቁ.16-17/፡፡ ወንጌላዊው የጊዜው መጨለም የጌታችንም አለመምጣት የሚነግረን ያለምክንያት አይደለም፡፡ ይልቁንም የደቀ መዛሙርቱ ታዛዥነት ለማሳየት እንጂ፡፡ ከእናንተ መካከል “ስለምንስ እስከ አሁን ማለትም እስኪጨልም ድረስ ወደ ደቀ መዛሙርቱ ሳይመጣ ቆየ?” ብሎ የሚጠይቅ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- “አንደኛ ደቀ መዛሙርቱ ፈተና መቋቋምን መለማመድ ነበረባቸው፤ ሁለተኛ እርሱ ልዑለ ባሕርይ መሆኑንና ሙሴ ቅሉ እንደ እኔ ያለ ነብይ ያስነሣላችኋል ቢልም ክርስቶስ እርሱ ዕሩቅ ብእሲ አለመሆኑንና ከጥንት ጀምሮ ንጉሥ ሰውም የማያነግሠው ልዑለ ባሕርይ መሆኑን ማወቅ መረዳት ነበረባቸው” /Saint John Chrysostom, Homilies on St. John, Hom. 43:1./፡፡

   ከዚህ በኋላ፣ ደቀ መዛሙርቱ በታንኳአቸው መጓዝ ከጀመሩ በኋላ “ብርቱ ነፋስ ነፈሰ፤ ባሕሩም ተናወጠ፡፡ ሀያ አምስት ወይም ሠላሳ ምዕራፍ ከቀዘፉ በኋላም፥ ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ ታንኳይቱ ሲቀርብ አይተው ፈሩ” /ቁ.18-19/። አዎ! ሰዓቱን ቢያስቡት አራተኛው ሰዓተ ሌሊት ላይ ነው፣ ቦታውን ቢያዩት ገና ማዕከለ ባሕሩ ላይ ናቸው፤ ዋኝተው እንዳይሄዱ የብሱ ሩቅ ነው፤ ባሕሩን ቢመለከቱት ንውጽውጽታው ጨምሯል፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ኢየሱስ እርሱ መሲሑ ማዕበሉን እየተረገጠ ቢመጣ ምትሐት መሰላቸው፡፡ ስለዚህም ፈሩ፤ ደነገጡ /ማቴ.14፡26፣ ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡

   ፍርሐትን የሚያርቅ ከዐቅማችንም በላይ እንድንፈተን የማይሻ ጌታ ግን፡-እኔ ነኝ፤ አትፍሩ” አላቸው፤ ሰላማቸውን መለሰላቸው፤ እንደፈለጉትም ዕረፍት ሆነላቸው፡፡ ድንቅ ነው! ፈተና ውስጥ ስንገባ፣ የመቻል አቅማችን የመጨረሻውን ጠርዝ ሲደርስ፣ ተስፋችንም ሲሟጠጥ ክርስቶስ ይደርሳል፡፡ ደርሶም ሰላማችንን ይመልሳል፤ ፍርሐታችንን ያርቃል፤ ተስፋችንን ይቀጥላል፤ አያልፍም ያልነውን አሳልፎም ውስጣችን በሐሴት ይሞላዋል፤ የሕይወታችንን ማዕበል እየረገጠ መጥቶም ነፋሱን (የሚያውከንን ሁሉ) ጸጥ ያደርገዋል፡፡ ሆኖም ግን ደቀ መዛሙርቱ ጌታችንን “በታንኳይቱ ሊቀበሉት ወደዱ” እንዲል በማዕበል ስንናወጥ ወደ መርከባችን (ወደሚነዋወጠው ሕይወታችን) ለመግባት ውዴታችንን ይጠብቃል፡፡  ስንፈቅድ ግን፤ እግዚኦ አድኅነኒ- አቤቱ አድነን ስንለው ግን ፈጥኖ እጁን ይዘረጋል፤ ያወጣንማል፡፡ ከአሸናፊውም ጋር እናሸንፋለን፡፡ ማዕበል ውስጥ ሆነን (ከእነ ድካማችን በእርሱ እርዳታ!) ማሸነፋችን ደግሞ  እግዚአብሔርን የበለጠ እንድናመሰግነው ይረዳናል፡፡ ይህን ጕዞ እስከ ሕይወታችን ፍጻሜ ድረስ ይቀጥላል፡፡ በመጨረሻው ግን ሙሽራው ይመጣል፡፡ እንግዲያውስ አማኞች ሆይ! አትፍሩ! ማዕበል ንውጽውጽታ የሌለው የብሱ (ርስታችን መንግሥተ ሰማያት) ቅርብ ነውና /ቁ.20-21፣ St. Cyril of Alexandria, Commentary on the Gospel of John/፡፡

  
   “ሰው ዝም ብሎ የእግዚአብሔርን ማዳን ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው” /ሰቆ.ኤር.3፡26/፡፡
  ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!


Tuesday, June 19, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል አንድ!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!   
    ከሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ስለ ሊቀ ካህናችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ በስፋትና በጥልቀት የምናገኘው በዕብራውያን መልእክት ነው፡፡ ሐዋርያው መልእክቱን የጻፈበት ዓላማም በአጭሩ እንዲህ ቀርቧል፡- በይሁዳ ሀገርና በብሔረ አሕዛብ ሁሉ ያሉ ዕብራውያን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንና ደቀ መዛሙርቱን ወንጌልን በማስተማራቸው አጽንተው ይጠልዋቸው ነበር፡፡ ጌታ ካረገ በኋላ ግን በሐዋርያት ቃል የሚደረገውን ተአምራት ባዩ ጊዜ ከእነርሱ ብዙዎች በጌታችን ስም አመኑ /ሐዋ.2 ሙሉውን ይመልከቱ/፡፡ ሆኖም ግን ሕገ ኦሪትን ከሕገ ወንጌል ይልቅ አብልጠው መጠበቃቸው አልተዉም፡፡ በሌላ አገላለጽ ሕገ ወንጌልን ለሕገ ኦሪታቸው ተጨማሪ ሕግ አድርገዋት ነበር፡፡

  ሐዋርያትም ሃይማኖተ ወንጌል በዓለሙ ሁሉ እስኪስፋፋ ድረስ ኦሪትን ከወንጌል ጋር እንዲጠብቁ ተዋቸው እንጂ “ኦሪታችሁን ፈጥናችሁ ልቀቁ” አላልዋቸውም ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ አይሁድ አሕዛብን ለጓደኝነት ይጸየፍዋቸው ምግባቸውም ከመብላት ይከለከሉ ነበር፡፡  ሐዋርያት ወንጌልን ሲያስተምርዋቸው ተአምራት ሲያደርጉላቸው አይተው ቢያምኑም ተገዘሩ፤ ሕገ ኦሪትን ጠብቁ ስላላልዋቸው ፍጹም ቅናት አደረባቸው፡፡ የኦሪታቸውና የሌዋውያን ክህነት የላሙን፣ የበሬዉን፣ የበጉን፣ የፍየሉን መሥዋዕትና በጠቅላላው የአባቶቻቸውን ሥርዓት ማለፍ ባሰቡ ጊዜ እጅግ አዘኑ፡፡ ከጥንት ጀምሮ ለእነርሱ ብቻ ይነገር የነበረው ተስፋ ለሁሉም እንደሆነ ባሰቡ ጊዜ እጅግ ታወኩ፡፡ ከዚህ በኋላ በአንድነት መከሩና ከአሕዛብ ወገን በወንጌል ያመኑትን “ወንጌል ያለ ኦሪት ጥምቀት ያለ ግዝረት አትረባምና ተገዘሩ ሕገ ኦሪትንም ጠብቁ” እያሉ ዓለምን የሚያውኩ ሐሰተኛ ወንድሞችን ወደ አንጾክያ ሰደዱ፡፡ የግብረ ሐዋርያት ጸሐፊ “ከይሁዳ ሀገርም የወረዱ ሰዎች እንደ ሙሴ ሕግ ካልተገዘራችሁ ልትድኑ አትችሉም እያሉ ወንድሞችን ያስተምሩ ነበር” እንዲል፡፡

  ስለዚህም በአንጾክያ ያሉ አሕዛብ እጅግ ታውከው ጳውሎስንና በርናባስን ተከራከሯቸው፡፡ ስለዚህ ክርክር ጳውሎና በርናባስ ከእነርሱም አንዳንዶች ሌሎች ሰዎች ወደ ሐዋርያት ወደ ቀሳውስትም ወደ ኢየሩሳሌም ይወጡ ዘንድ ተቈረጠ።

  ወደ ኢየሩሳሌምም በደረሱ ጊዜ ቤተ ክርስቲያንና ሐዋርያት ቀሳውስትም ተቀበሉአቸው፤ እግዚአብሔርም በአሕዛብ ዘንድ ተአምራት እንዳደረገላቸው አሕዛብም ሳይገዘሩ መንፈስ ቅዱስ እንደ ወረደላቸው ቢነግሯቸው ሐዋርያትና ቀሳውስቱ እጅግ ደስ አላቸው፡፡

  ከፈሪሳውያን ወገን አምነው የነበሩ አንዳንድ ሰዎች ግን ተነሥተው ወደ ሐዋርያት ሔዱና “ከአሕዛብ ያመኑትን ትገርዙአቸው ዘንድና ሕገ ኦሪትንም እንዲጠብቁ ታዙአቸው ዘንድ ይገባል” አሏቸው፡፡ ሐዋርያትና ቀሳውስት ግን በክርስትናው ታሪክ የመጀመርያው በሆነው በዚሁ ጉባኤያቸው “ከጣዖት ወደ ወንጌል በተመለሱ አሕዛብ ሸክም አታክብዱ፤ ሁላችንም በጸጋ እግዚአብሔር በወንጌል አንድ እንሆናለን እንጂ አባቶቻችን እኛም ያልቻልነውን ጽኑ ሸክም አታሸክሟቸው፡፡ ለጣዖት የተሠዋውን፣ ሞቶ ያደረውን፣ በደም የታነቀውን ከመብላትና ከዝሙት

FeedBurner FeedCount