Monday, August 3, 2015

ሆስፒታልና ቤተ ክርስቲያን በንጽጽር ሲታዩ



በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 28 ቀን 2007 ዓ.ም.):- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
እግዚአብሔር የሚወዳችሁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ልጆቼ! ተጠራርታችሁ ወደ አባታችሁ ቤት ለመምጣት ያደረጋችሁትን ቅንአት ተመልክቼ ደስ ተሰኝቼባችኋለሁ፡፡ እኔም ይህን ቅንአታችሁን አይቼ ስለ ነፍሳችሁ ጤና ይበልጥ እንዳስብ አድርጎኛል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ቀዶ ጥገና የሚደረግባት ሐኪም ቤት ናት፡፡ የሥጋ ቀዶ ጥገና ግን አይደለም፤ የነፍስ ቀዶ ጥገና ነው እንጂ፡፡ የምናክመው የሥጋን ቁስል አይደለም፤ መንፈሳዊ ቁስልን እንጂ፡፡ መድኃኒቱም ቃለ እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህ መድኃኒት በምድር ላይ ከሚበቅሉት ዕፅዋት የተቀመመ አይደለም፤ ከሰማያት ከሚመጣው ቃል እንጂ፡፡ ይህን መድኃኒት በቁስል ላይ ለመጨመር ሐኪሞች አያስፈልጉም፤ የሰባክያነ ወንጌል አንደበት እንጂ፡፡ ቀዶ ጥገናውን ለማከናወን ብዙ ሰዓታትን አይፈጅም፡፡ ቀዶ ጥገናው ላይሳካ ይችላል ተብሎ የሚጠረጠር አይደለም፡፡ ከጊዜ በኋላ ወይም በሌላ ሕመም ምክንያት የተደረገው ቀዶ ጥገና ሊከሽፍ ይችላል ተብሎም አይገመትም፡፡ ሐኪሞች የሚሰጡን መድኃኒት እንዲህ ዓይነት ችግር ሊያጋጥመው ይችላል፡፡ ሐኪሞች የሚሰጡን መድኃኒተ ሥጋ ለጊዜው ብርቱ ነው፤ ሰውነታችን እያረጀ እንደሚሔደው ኹሉ መድኃኒቱም በጊዜ ሒደት ብርታቱን እያጣ ይሔዳል፡፡ ሌላ ደዌ ዘሥጋ ሲገጥመንም መቋቋም የሚችል አይደለም፡፡ ምክንያቱም መድኃኒቱን የቀመሙት ሰዎች ስለኾኑ፡፡ ከእግዚአብሔር የሚሰጠን መድኃኒት ግን እንደዚህ አይደለም፡፡ ምንም ያህል ጊዜ ቢቆይም አይበላሽም፤ ጊዜው አያልፍበትም፤ ኃይሉም ብርታቱም ያው ነው አይቀንስም፡፡

Friday, July 31, 2015

የዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም መምህራንና ቀሳውስት ማሠልጠኛ መንፈሳዊ ት/ቤት ትናንት፣ ዛሬና ነገ



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 24 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው የታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም መምህራንና ቀሳውስት ማሠልጠኛ ተቋም ከተመሠረተ ከ82 ዓመታት በላይ ኾኖታል፡፡ በእነዚህ አገልግሎት ዘመናቱም በርካታ ታላላቅ የሃይማኖት አባቶች ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቤተክርስቲያን ሊቃውንት፣ አባቶች መምህራንና ካህናትን አፍርቷል፡፡ ማሠልጠኛው ጥንታዊው የሀገራችን ቋንቋና ፊደል ግእዝና ትምህርቱ ተጠብቆ እንዲቆይ ለትውልድም እንዲተላለፍ በማድረግ በኩል ታላቅ ድርሻ አለው፡፡ የቤተክርስቲያን አባቶችና ምእመናን ኹሉ የቤተ ክርስቲያን አለኝታና ቅርስ መኾኑን በኩራት የሚናገሩለት ተቋም ነው፡፡
ይኼው ማሠልጠኛ በረጅም ጊዜ አገልግሎት ለቤተክርስቲያንም ኾነ ለሀገር ከፍተኛ አገልግሎትና ጥቅም የሰጠ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የዚህን ት/ቤት ትናንት የነበረውን ገጽታ ዛሬ ያለበትንና ወደፊት የሚጠበቅበትን በዚህች አነስተኛ ጽሑፍ እንዳስሳለን፡፡

Sunday, July 26, 2015

....... ሰላም ገብርኤል.......



በልዑል ገ/እግዚአብሔር
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 19 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!


ሰላምታየሰላማዊ አካል ስጦታ
................
በጎነት አክብሮት ምሣሌው
የታላቅነት ትርጓሜ የሰሪውን ማንነት
...........
አንድ የመሆን ምስጢር ሲለው

ሰላም...!
ነገረ ፈጅ የእስራኤል ባለጠጋ
.........
መመረቅ መርገም ቢችልበት
ባላቅ ደስ ሊለው...
የፀጋውን ስጦታ ቅዱሱን ሊረግምበት
..............
አህያውን ይዞ ተጓዘበት

Tuesday, July 21, 2015

ትምህርተ ሃይማኖት (ክፍል ዐሥራ ሦስት)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ 14 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የእሑድ ሰዓተ መዓልት ፍጥረታት
ሀ) በአንደኛው ሰዓተ መዓልት፡- እግዚአብሔር በዚህ ጊዜ “ብርሃን ይኹን” ብሎ ብርሃንን በስተምሥራቅ በኩል ፈጠረ፡፡ ከዚህም በኋላ መንፈስ ቅዱስ ዓለምን እንደ እንቁላል በክንፉ ዕቅፍ አድርጐ ለመላእክት ታያቸው፡፡ መላእክቱንም እንዲህ ሲል ጠየቃቸው፡- “ይህ ኹሉ ሰማይ የእኔ ነው፡፡ ታዲያ ከቤቴ ማን አገባችሁ? ከወዴትስ መጣችሁ?” መላእከቱም፡- “አቤቱ ከግሩማን በላይ ያለህ ግሩም አንተ ነህ፡፡ በዚህን ያህል ድንጋፄ ያራድከን ያንቀጠቀጥከን እናውቅህ ዘንድ አንተ ማን ነህ?” አሉት፡፡ መንፈስ ቅዱስም “ሰማይን፣ ምድርን፣ እናንተንም ለፈጠረ ለአብ ሕይወቱ ነኝ” አላቸው /ኄኖክ.13፡21-22/፡፡ መላእክትም “አቤቱ ጌታችን የፈጠረንንስ፣ ያመጣንንስ ከቤትህስ ያገባንን አንተ ታውቃለህ እንጂ እኛ ምን እናውቃለን” ብለው ፈጣሪነቱ የባሕርዩ እንደኾነ አመኑለት፤ መሰከሩለት፡፡
ሳጥናኤልም መላእክትና መንፈስ ቅዱስ ሲነጋገሩ ቢሰማ ደነገጠ፤ ሐሳቡ ከንቱ ስለኾነበትም አፈረ /ኢሳ.14፡12-16/፡፡ ወዲያውም ያ በምሥራቅ የተፈጠረ ብርሃን እንደ ምንጭ እየፈሰሰ እንደ ጐርፍ እየጐረፈ ደርሶ አጥለቀለቃቸው፤ ዋጣቸው፡፡ ብርሃኑ የመጣው እግዚአብሔር ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ አንዲቱ ማለትም እሳቲቱን ብርሃን ውለጂ ብሎ ሲያዝዛት ነው፡፡ ከዚያም በኋላ ብርሃኑን መዓልት ብሎ ጠራው፡፡ ከዚያ በፊት ተፈጥሮ የነበረው ጨለማውን ደግሞ ሌሊት ብሎ ጠራው /ዘፍ.1፡5-6/፡፡ በዚሁም የብርሃንን ሥራና የጨለማ ሥራ ለይተን እንኖር ዘንድ ሲያስተምረን ነው፡፡

FeedBurner FeedCount