Sunday, October 4, 2015

የዘመናችን አጥማቂ ነን ባዮች፡- የሐሳዊው መሲሕ መንገድ ጠራጊዎች



በዲ/ን ዳንኤል ክብረት
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 23 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ክፍል አንድ
በዚህ ዘመን በተደጋጋሚ ከሚነሡ መንፈሳውያን ጥቄዎች መካከል አንዱ የጥምቀትና አጥማቂዎች ጉዳይ ነው፡፡ ጥምቀት(የክርስትና ጥምቀትን አይመለከትም) በብሉይና በሐዲስ ኪዳን ምእመናን ፈውሰ ሥጋ ፈውሰ ነፍስ እንዲያገኙባቸው ከእግዚአብሔር ከተሰጡ ጸጋዎች አንዱ ነው፡፡(2 ነገሥት 5 ዮሐ. 5፣ዮሐ. 9)፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክም ውስጥ በልዩ ልዩ ገድላተ ቅዱሳን ላይ እንደምናነበው በጠበል ሕዝቡን ሲፈውስ ኖሯል፡፡ ሕዝብ ፈውስ የሚያገኝባቸው እንደ ሰሊሆምና እንደ ቤተ ሳይዳ የታወቁ የቃል ኪዳን ቦታዎችም ነበሩ፡፡
አሁን በያዝነው ዘመን አያሌአጥማቂ> የሚባሉ ሰዎች ተነሥተዋል፡፡ ክብራቸውን የሚገልጥ ማስታወቂያ ያስነግራሉ፣ መቁጠሪያ ይሸጣሉ፣ ቅባት ይቀባሉ፣ አዳራሽ ከፍተው ወይም ሕዝብ በሜዳ ሰብስበው እንፈውሳለን ይላሉ፤ ሰይጣን ተናገረ የሚባለውን በካሴት ቀድተው ይሸጣሉ፡፡ ከዚህ ቀጥዬ በማቀርባቸው አሥር ምክንያቶች እነዚህን ሐሳውያን መቀበል የለብንም ብዬ አምናለሁ፡፡


1.      በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ገዳማዊ ሕይወት፣ ክህነታዊ ሕይወት፣ የጸሎት ሕይወት ወይም ሌላ አንዳች ተጋድሎ ሳይኖረው ማጥመቅ ብቻ ሥራው የነበረ ክርስቲያን የለም፡፡ ሀብተ ፈውስ የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች የሌላው መንፈሳዊ ሕይወታቸው ውጤት ወይም ነጸብራቅ ነበር እንጂ ሥራቸው እየዞሩ ማጥመቅ አልነበረም፡፡ የሐዋርያት ሥራን ብናነብ ሐዋርያት ለወንጌል አገልግሎት ሲሠማሩ በአንድ በኩል አሕዛብን ወደ ክርስቶስ ለመጥራት በሌላ በኩል የአንደበት ትምህርታቸውን በእጃቸው ተአምር ለማጽናት  ተአምራትን ያደርጉ ነበር እንጂ በአንድ ከተማ ውስጥ ሲያጠመቁ ውለው ያደሩበት፣ ወይም ከወንጌል አገልግሎት ተለይተው አጥማቂ ብቻ የሆኑበት፣ ወይም ደግሞ በዚህ ቦታ ፈውስ እንሰጣለንና ተሰብሰቡ ብለው ያስነገሩበት አንድም ማስረጃ የለም፡፡ በገድለ ቅዱሳንም ቅዱሳን ጸጋ እግዚአብሔር ሲያድርባቸው፣ ሥጋቸውንና ሰይጣንን ድል ሲነሡ፣ በክርስትናቸው ሲበስሉ ተአምራት ይከተሏቸዋል እንጂ እንዲሁ ማጥመቅና መፈወስ ብቻ ሕይወቱ የነበረ ቅዱስ የለም፡፡ ሰው ያለ ተጋድሎ እንዴት ጸጋ ያገኛል፡፡ በአሁኑ ዘመን ግን ከተራ ሰዎች የተለየ መንፈሳዊ ሕይወት የሌላቸው ሁሉ እየተነሡ አጥማቂ ሊሆኑ የቻሉበት አሳማኝ ምክንያት የለም፡፡
2.     በገድለ ቅዱሳን ውስጥ ቅዱሳን በገዳማዊ ሕይወት፣ በሰማዕትነት፣ በክህነታዊ አገልግሎት ሲሠማሩ እግዚአብሔር ምእመናንን ለመጥቀም ወይም ክብረ ቅዱሳንን ለመግለጥ በእነርሱ ላይ ተአምራትን ያደርጋል፡፡ እነርሱ ግን ይህ ክብር እንዳይገለጥባቸው ሲሸሹ፣ እኔ አላደረግኩም ሲሉ ወይም ስለራሳቸው ደካማነት ሲነገሩ እናያለን እንጂ እንፈውሳችኋላንብለው ዐዋጅ ሲናገሩ አይተንም፣ አንብበንም አናውቅም፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከአባ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም ወጥተው ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ  ገዳም የሄዱበት ዋናው ምክንያት በገዳሙ እያሉ በፈወሱት አንድ በሽተኛ ምክንያት ስማቸው ከፍ በማለቱ፣ ብዙ ሰዎችም በመሰብሰባቸው የተነሣ ነው፡፡ ታላቁ አባት መቃርዮስ ገዳሙን ትቶ ወደ አንዲት መንደር መጥቶ የኖረው በገዳሙ ክብሩ በመገለጡና ተአምራቱ በመታየታቸው ከከንቱ ውዳሴ ለማምለጥ ነበር፡፡ ስምዖን ጫማ ሰፊው አካባቢውን ትቶ የጠፋው ተአምር አድራጊነቱ በመታወቁ ምክንያት ነበር፡፡ አሁን ግን ከዚህ በተቃራኒው ሰዎች እናጠምቃለን፣እንፈውሳለን ብለው ማስታወቂያ የሚያስነግሩበት፣ ካሴት የሚሸጡበት፣ ፖስተር የሚሰቅሉበት ዘመን ነው፡፡
3.      ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ ማን እንደሆነ፣ ድንግል ማርያም ማን እንደሆነች፣ ቅዱሳን መላእክት ማን እንደሆኑ ሌሎቹም ቅዱሳን ማን እንደሆኑ ጠንቅቃ ታውቃለች፡፡ የእግዚአብሔርን ክብር ለሰዎች ሰጥታ አታውቅም፡፡ ቅዱሳንን ከፈጣሪ አስበልጣ አታወቅም፡፡ የቅዱሳን መገኛና መሠረት በባሕርዩ ቅዱስ የሆነው እግዚአብሔር መሆኑን ታምናለች፣ታስተምርማለች፡፡ ለእግዚአብሔር የማይቻል ለቅዱሳን ይቻላል፣ በእግዚአብሔር የማይሠራ በቅዱሳን ይሠራል ብላ አታምንም፣ አታስተምርም፡፡ በዘመኑ አጥማቂዎች ዘንድ የምናየው ግን ከዚህ በተቃራኒው ነው፡፡ በክርስቶስ ስም የማይወጣው ሰይጣን የቅዱስ ሚካኤልን ስም ሲጠሩበት ይወጣል፡፡ በክርስቶስ ስም የሚያሾፍ ሰይጣን የድንግል ማርያምን ስም ሲጠሩበት ተቃጠልኩ ይላል፡፡  ይኼ ፈጽሞ ክህደት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንም ትምህርት አይደለም፡፡ ‹‹በስመ ሥላሴ እቀጠቅጥ ከይሴ›› ብላ ያስተማረች ቤተ ክርስቲያን ላይ ‹‹በክርስቶስ ስም አንወጣም፣ በማርያም ስም ግን እንወጣለን›› እያለ አጋንንት ወጣ የሚል ትምህርት ማስፋፋት ክህደት ነው፡፡
4.     መቁጠሪያ በቤተ ክርስቲያናችን ለጸሎት መቀስቀሻና ማስታኮቻ የሚውል ነው፡፡ ምእመናን እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ፣ በእንተ ማርያም መሐረነ ክርስቶስ፣ ኪርኤ አላይሶን የተባሉትን የምሕላ ጸሎቶች በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የተመደበላቸውን ቁጥር ሳይስቱ እንዲጸልዩ የተሠራ ሥርዓት ነው፡፡ በጸሎት ጊዜ ዝንጋኤ እንዳይገጥማቸው ኅሊናቸውን ለመሰብሰብም ይረዳል፡፡ አንድ ቅዱስ ለብዙ ዘመን የጸለየበት መቁጠሪያ፣ የተደገፈበት መቋሚያ፣ የቆመበት ምድር፣ የለበሰው ልብስ፣ የተጠቀመበት መጽሐፍ ተአምራት ቢያደርግ አይገርምም፡፡ ቅዱሳን የነፍሳቸው ቅድስና ለሥጋቸው፣ የሥጋቸውም ለልብሳቸው፣ የልብሳቸው ለጥላቸው ተርፎ አይተን እናውቃለንና(የሐዋ. 512-17 19 11-12)ከዚህ ውጭ ግን የሚሸጥ መቁጠሪያ ሰይጣን የሚያስወጣበት፣ ሰው ራሱን በመቁጠሪያ ስለደበደበ ከዲያብሎስ እሥራት የሚፈታበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ ሰይጣን በጾምና በጸሎት እንጂ በመቁጠሪያ ድብደባ አይለቅም(ማቴ.1721)፡፡ መቁጠሪያ ተአምር የሚሠራ ቢሆን እንኳን አንድ ቅዱስ የተጋደለበት፣ ከዚያ ቅዱስም በረከት ያተረፈ መሆን አለበት፡፡ ልክ የቅዱስ ጳውሎስ የጨርቁ እራፊ ይፈውስ እንደነበረው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክም የትኛውም አባት መቁጠሪያ ሲያድልና በመቁጠሪያ ሰይጣን ታወጣላችሁ ብሎ ሲያስተምር አልታየም፡፡
5.      ጌታችን በሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ አስተምሯል፡፡ በጌንሳሬጥ ምድር አምስት (ማቴ 1413-21) በገሊላ ባሕር አጠገብ አራት (ማቴ 1532-39) ይህ ሁሉ ሕዝብ የቃሉን ትምህርት የእጁን ተአምራት አይቶ ይኼድ ነበር እንጂ ሰይጣን አድሮበት በአንድ ጊዜ የጅምላ ጩኸት ሲጮህ ታይቶ አይታወቅም፡፡ የተወሰኑ ሰዎች ግን እየቀረቡ ፈውሰ ሥጋ ፈውሰ ነፍስ አግኝተዋል፡፡ በዚህ ጊዜም ቢሆን መድኃኒት ያደረገብሽ፣ ድግምት ያስደገመብህ፣ መተት ያስመተተብህ እገሌ ነው የሚል ሰይጣን አልተሰማም፡፡ ዛሬ ግን በአንድ ቦታ ለጥምቀት የሚሰበሰቡ ሰዎች አብዛኞቹ ይጮኻሉ፡፡ ሁሉም በሰይጣን ተይዘዋል ይባላሉ፣ ሁሉም ድግምት፣ መተት፣ መድኃኒት፣ ጥንቆላ እንደተደረገባቸው ይነገራቸዋል፡፡ ሰይጣንን አምነው ከባሎቻቸው፣ ከሚስቶቻቸው፣ ከእኅት ወንድሞቻቸው፣ ከጎረቤቶቻች፣ ከሥራ ባልደረቦቻቸው ይጣላሉ፡፡ ከባቴ አበሳነትን ፈጽሞ የረሳ፣ ከፍቅር ይልቅ ጠላትነትን ለማስፈን የመጣ፣ ሰዎች እግዚአብሔርን አምነው ከመፋቀር ይልቅ ሰይጣንን አምነው እንዲጣሉ የሚያደርግ የሰይጣን አሠራር ነው፡፡ ለመሆኑ ይህንን ሁሉ ሕዝብ ሰይጣን ሲቆጣጠረው ክርስቶስ የለምን? የተጠመቅነው የልጅነት ጥምቀት፣ የቆረብነውስ ቁርባን አይሠራምን? ገና ወደ ክርስትና ያልመጡ የገሊላ ክርስቲያኖች እንኳን በጩኸት አልተደበላለቁም እንኳን እኛ በክርስቶስ ክርስቲያን በወልድ ውሉድ የተባልነው፡፡ ይህ አሠራር የክርስቶስን ነገረ ድኅነት የሚፃረርና ከማዳን ሥራውም የወጣ ነው፡፡ ከክርስቶስ ክብርና ኃይል ይልቅ የሰይጣንን ኃይል ለማሳየት የሚሠራም ነው፡፡ 
6.     ለመሆኑ ስመ እግዚአብሔርን የሚጠራ ሁሉ ትክክለኛ ነውን? አንዳንድ ምእመናን እንዲህ ይላሉእግዚአብሔርን ይጠራሉ፣ እመቤታችንንም ያከብራሉ››፡፡ ልክ ነው ሰይጣን ለአመሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ ይጠቅሳል ይባላል፡፡ ሰይጣን ምንም እንኳ የሐሰት አባቷ ቢሆንም (ዮሐ. 844) ሙሉ ውሸት ግን አይናገርም፡፡ በከፊል እንጂ፡፡ ሔዋንንንግሥተ ሰማይ ወምድርሲላት ከፍሎ ነው የዋሻት፡፡ ንግሥተ ምድር ናት፤ ንግሥተ ሰማይ ግን አልነበረቺም፡፡ በወንጌል ውስጥ አጋንንት ስመ እግዚአብሔርን ጠርተው ያውቃሉ፡፡ ሰይጣን ጌታን ሲፈትነው ከቅዱሳት መጻሕፍት ጠቅሶ ነው(ማቴ 4) ጌታችን በጌርጌሴኖን ያገኛቸው አጋንንት ያደሩባቸው ሰዎችየእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ሆይብለው ነበር የተናገሩት፡፡ ንግግራቸው ልክ ነው፡፡ እነርሱ ግን አጋንንት ናቸው፡፡ ጌታም አስወጣቸው እንጂ ማን ድግምት እንዳደረገባቸው አላናዘዛቸውም፡፡ በሌላ ቦታም በምኩራብ ሲያስተምር አንድ ሰይጣን ያደረበትን ሰው አመጡለት፡፡ ሰይጣኑም ‹‹የናዝሬቱ ኢየሱስ ሆይብሎ ነበር የጠራው፡፡ ጌታ ግንዝም ብለህ ወጣአለው እንጂ መድኃኒት ማን እንዳደረገ ተናገር አላለውም(ማር. 121-28)፡፡ የናዝሬቱ ኢየሱስ ስላለውም ሰይጣንነቱን አልቀየረውም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስተምር ፊልጵስዩስ የተባለ ከተማ ደረሰ፡፡ በዚያም አንዲት በርኩስ መንፈስ የተያዘች ሴት እየተከተለቺው ‹‹የመዳንን መንገድ የሚነግሯችሁ እነዚህ ሰዎች የልዑል አምላክ ባሪያዎች ናቸው›› አለች፡፡ ሴትዮዋ የተናገረቺው ምንም ስሕተት የለውም፡፡ እነ ቅዱስ ጳውሎስ የመዳንን መንገድ ያስተምራሉ፡፡ የልዑል አምላክ ባሪያዎችም ናቸው፡፡ ይህ ትክክል ስለሆነ ግን ቅዱስ ጳውሎስ ዝም አላለም፡፡ መንፈሱን አስወጣው እንጂ(የሐዋ.1616-18)፡፡ እነዚህ ሁሉ የሚነግሩን አንድ ሰው ስመ እግዚአብሔርን ወይም ስመ ቅዱሳንን ስለጠራ ብቻ ትክክል መሆኑን እንደማያሳይ ነው፡፡ እርስ በርሱ የማይጣረስ ርቱዕ የሆነ እምነትም ያስፈልገዋል፡፡ ርቱዕ የሆነ ሕይወትም ያሻዋል፡፡ በክርስትና አንድ ሰው መንገዱ ትክክል ሳይሆን ውጤቱ ትክክል ሊሆን አይችልም፡፡ ያለ ትክክለኛ እምነት፣ ያለ ትክክለኛም መንፈሳዊ ሕይወት ትክክለኛ ተአምራት ሊኖረው አይችልም፡፡ በሲኦል በኩል ወደ ገነት ሊገባ አይችልምና፡፡ 
7.     ተአምራት ማድረግ ብቻውን የቅድስና ማሳያ አይደለም፡፡ ተአምራት ከመንፈሳዊ ሕይወት ብቃት ሲመነጩ እንጂ፡፡ ተአምር ከመንፈሳዊ ሕይወት ብቃት የመጣ ሲሆንስም በመንግሥተ ሰማያት በመጻፉ እንጂ በድንቅ ነገር ማንም ደስ አይለውም››(ሉቃ. 10 17-20)፡፡ ተአምራትን ሲከተሉ መኖርም የአሕዛብነት ምልክት እንጂ የክርስትና ምልክት አይደለም(ማቴ. 12 39)፡፡ የክርስትና ዋና መሠረቱ ክርስቲያናዊ ትምህርት፣ ክርስቲያናዊ እምነትና ክርስቲያናዊ ሕይወት ናቸው፡፡ አንዳንዶች በማርቆስ ወንጌል መጨረሻ ላይ(ማር 16) ‹‹ያመኑት እነዚህ ምልክቶች ይከተሏቸዋል›› የሚለውን ይጠቅሳሉ፡፡ እዚህ ላይ ያመኑት የተባሉትየበቁትማለት ነው፡፡ ያማ ባይሆን ኖሮ ሁላችንም ተአምር ስናደርግ መኖራችን ነበር፡፡ አምነናልና፡፡ ደግሞም ያመኑት የሚለው ለሁላችንም ይሠራል ካልን እስኪ መርዝ ጠጥተን ምንም ሳንሆን ፣እባብም ጨብጠን ስንተርፍ እንየው፡፡ ይህ ሁሉ ግን በእመነት ለበሰሉ የሚቻል ነው፡፡ በሐዋርያት ሥራም በሐዋርያት እጅ ያመኑት ሁሉ ተአምር ሲሠሩ አናይም፡፡ በሐዋርያት ሥራ ድንቅ ሲሠሩ የምናያቸው ክርስቲያኖችም በጸሎት የተጉ፣ በሐዋርያነት አገልግሎት ሰማዕትነት የከፈሉ፣ በገድል የተቀጠቀጡ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ራሱ ሕይወቱ በተአምራት ከመገለጡ በፊት በሱባኤ የተወሰነ ነበረ(የሐዋ. 13 1-3) የዛሬ አጥማቂዎች ግን ማጥመቅ ፕሮፌሽናቸው እንጂ የመንፈሳዊ ሕይወታቸው መገለጫ አይደለም፡፡ እንዲህ ባለው ገዳም በገድል የኖሩ፣ እንዲህ ያለ መሥዋዕትነት ለክርስትና የከፈሉ ወይም ለምእመናን አርአያ የሚሆን እንዲህ ያለ መንፈሳዊ ሕይወት የነበራቸው ናቸው ተብሎ የማይመሰከርላቸው ራሳቸውን በራሳቸው የሾሙ ናቸው፡፡
8.     የሰይጣን ምትሐትም አለ፡፡ የሙሴ ጸጋና ሕይወት ድል እንዲሆኑ ባያደርጋቸው ኖሮ የፈርዖን ጠንቋዮች ብዙ አስደናቂ ነገር ሠርተው ነበር(ዘጸ. 78- 13)፡፡ በዘመነ ሳዖል የነበረቺው ሟርተኛም የሙታንን መንፈሶች ትጠራ ነበር(1 ነገሥት. 28 8-24)፡፡ አይሁድም አጋንንትን ያወጡ ነበር(የሐዋ. 1913)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የሐሳዊ መሲሕን አመጣጥ ሲያስተምረን ‹‹የእርሱ መምጣት በተአምራት ሁሉና በምልክቶች፣ በሐሰተኞች ድንቆችም በዓመጽም ማታለል ሁሉ እንደ ሰይጣን አሠራር ነው›› ይላል (1 ተሰ. 29)፡፡ ይህም  ከመንፈሳዊ ብቃት የማይመጣ ተአምር፣ ድንቅና ምልክት ምንጩ ከሰይጣን እንደሆነ ይጠቁመናል፡፡ ዛሬ በእነዚህ ይህንን ያህል የምንታለል ከሆነ ነገ ሐሳዊ መሲሕ ከዚህ የሚበልጡ አስደናቂ ተአምራትን ሲያደርግ ጨልጠን ገርኝተን መከተላችን የማይቀር ነው፡፡ ‹‹የተመረጡትን እንኳን እስኪያስት ድረስ›› ተብሏልና፡፡
9.      ምሥጢረ ቀንዲል መሠረቱን መጽሐፍ ቅዱስ ያደረገ(ያዕቆብ. 513) ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንዱ ነው፡፡ የሚፈጸመው በካህናት ሲሆን የራሱ የሆነ የጸሎትና የመቀባት ሥርዓት አለው፡፡ ለዚህም መጽሐፈ ምሥጢረ ቀንዲልን ማንበብ ይጠቅማል፡፡ አሁን የምናየው ግን በጀሪካል ቅባት ይዞ ማከፋፈል፣ ምእመናን ከአጥማቂዎችቅብዐ ቅዱስወስደው እንዲጠጡና እንዲቀቡ ማድረግ፣ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያልነበረ፣ በምሥጢረ ቀንዲል ያልተፈቀደና በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም ውስጥ የሌለ ነው፡፡ አንዳንድ አጥማቂዎችም ‹‹ከኢየሩሳሌም የመጣ ነው›› ይላሉ፡፡ ከኢየሩሳሌም የሚመጣ የተለየ ቅባት የለም፡፡ አንድን ቅባት ቅዱስ የሚያደርገው ጸሎቱና ሥርዓቱ አንጂ የተሠራበት ከተማ አይደለም፡፡ ኢየሩሳሌም ውስጥ ግሪክ ኦርቶዶክሶች፣ ካቶሊኮች፣ የይሖዋ ምስክሮች፣ ፕሮቴስታንቶች፣ ሌሎችም አሉ፡፡ ከኢየሩሳሌም የመጣ ማለት ከየት የመጣ ነው? ምእመናን ለኢየሩሳሌም በጎ ኅሊና ስላላቸው ‹‹ከኢየሩሳሌም ተባርኮ የመጣ ›› ይባላል፡፡ ማን ባረከው? ብሎ የሚጠይቅ የለም፡፡
10.    ከአክባሪው ይልቅ ከባሪው፣ከሰጭው ይልቅ ተቀባዩ፣ከጌታው ይልቅ አገልጋዩ የሚከብርበት ሥራ የእግዚአብሔር አይደለም፡፡ መንፈሳዊ አገልግሎት ዓላማው እግዚአብሔርን ማክበር፣ አሕዛብም እግዚአብሔርን እንዲያውቁ ማድረግ፣ ከመንገድ ጠራጊውም ይልቅ መንገዱን እንዲያገኙት ማስቻል ነው፡፡ አሁን የምናያቸውአጥማቂዎችእናተአምራትአድራጊዎች ግን ራሳቸውን የሚያከብሩ፣ እግዚአብሔርን የሚሸፍኑ፣ ሕዝቡ ቅዳሴና ትምህርት እየተወ እነርሱን በየሜዳው እንዲከተል የሚደርጉ፣ ሕዝቡ ንስሐ መግባት፣ ሥጋወ ደሙ ከመቀበል ይልቅ የእነርሱ አድናቂና ካዳሚ እንዲሆን የሚስቡ ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ስለ ራሱ ሲናገርእኔ ዝቅ ዝቅ ልል፣ እርሱም ከፍ ከፍ ሊል ይገባል›. ነበር ያለው (ዮሐ. 329)፡፡ ለእነ ቅዱስ ጳውሎስም በልስጥራ እግሩ የሰለለውን ሰው በፈወሰው ጊዜ ሕዝቡ ተደንቆ  እንደ አምላክ ሊሠዉላቸው ወድደው ነበር፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ግንእንደ እናንተ ሰዎች ነን›. እያለ ለምኖ አስተዋቸው፡፡ ሕዝቡንም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መለሳቸው፤ የእግዚአብሔርም ስም እንዲከብር አደረገ(የሐዋ 148-18)፡፡
በእነዚህና ቤሎችም ምክንያቶች በዘመናችን የተነሡትንአጥማቂ ነን ብለው ማስታወቂያ የሚያስነግሩትን፣ መቁጠሪያና ቅብዐ ቅዱስ የሚያከፋፍሉትን፣ በየሜዳው ሕዝብ ሰብስበው ምትሐት የሚሠሩትን ሰዎች መቀበል አለብን ብዬ አላምንም፡፡ ቤተ ክርስቲያን የጸጋው ግምጃ ቤት ናት፡፡ በጸሎት የሚተጉ፣በእምነት ሕይወት ያሉ ክርስቲያኖች በየምሕረት አደባባዮች ምሕረትን ያገኛሉ፡፡ በቤተ ሳይዳ መልአኩ ውኃውን ይባርከው እንደነበር ሁሉ የጠበል ቦታዎችን ራሱ እግዚአብሔር በቃል ኪዳኑ ባርኳቸዋል፡፡ የተለየ አጥማቂ አያስፈልገቸውም፡፡ የክህነት አገልግሎት የሚሰጥ ሰው እንጂ፡፡ ደግሞም ሁሉም ሕመም መዳን የለበትም፡፡ ደዌ ዘእሴት(ለበጎ የሚሰጥ ሕመም) አለ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ የብዙዎችን ሰይጣን እያስወጣ እርሱን ግን የሚጎስመው ሰይጣን ነበረው፡፡ ጌታን ሲለምንም ‹‹ተወው›› ነው የተባለው(2ኛቆሮ. 12 7)፡፡ የዛሬ አጥማቂ ነን ባዮች ግን ሁሉም ሕመም ይድናል ይላሉ፡፡ ለቅዱስ ጳውሎስ ያልተቻለ ተቻላቸውን? ከሐዋርያት አንዱ የነገረው ያዕቆብ እግረ በሽተኛ ነበር(ዜና ሐዋርያት፣ በእንተ ያዕቆብ ሐዋርያ) እርሱ ግን ብዙዎችን ይፈውስ ነበር፡፡ ከእግዚአብሔር ምሕረት አገኘን የምንለውም ስንፈወስ ብቻ መሆን የለበትም፤ የምንታገሥበት ዐቅም ስናገኝም ጭምር እንጂ፡፡ ልመናችንም ለፈውስ ብቻ ሳይሆን ለመታገሥ ዐቅም እንዲሰጠን መሆንም አለበት፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ለመፈውስ የሚችል ቢሆንም ሁሉንም ግን አይፈውስም፡፡ ለበረከት፣ ለተግሣጽ፣ ከከንቱ ውዳሴና ከትዕቢት ለመከላከል የሚፈቅደው ደዌም አለ፡፡ ያዕቆብ ወልደ ይስሐቅ ይህ ተሰጥቶት ነበር(ዘፍ. 3231)፡፡ ክርስትና በመንፈሳዊ ሕይወት በመኖር፣ በንስሐ መንገድ በመመላለስ፣ በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን በመሳተፍ እንጂ በድንቅና በተአምራት የሚኖር አይደለም፡፡
አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ‹‹ገንዘብ ይሰበስባሉ፣ ገቢ ያስገኛሉ›› ብለው እነዚህን ሐሳውያን እንደሚደግፉ ይታወቃል፡፡ ምእመናንም ‹‹ታድያ አቡነ እገሌ ለምን ፈቀዱ›› ይላሉ፡፡ እኛ ግን መሠረት ማድረግ ያለብን የቅዱሳት መጻሕፍትን ትምህርት፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን፣ታሪከ ቤተ ክርስቲያንን፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ነው፡፡ ማንም ከዚህ የወጣ ቢኖር ትምህርቱን ለመቀበል አንገደድም፡፡ ታላቅነት በእምነት እንጂ በሥልጣን አይገኝምና፡፡ ታላቁ አባት ዲዮስቆሮስ 451 ዓም የኬልቄዶን ጉባኤ የልዮንን የሁለት ባሕርይ ትምህርት አልቀበል ሲል የሮም ባለ ሥልጣናት ‹‹እርሱኮ በቅዱስ ጴጥሮስ መንበር የተቀመጠ የሮም ፖፕ ነውና አለቃህ ነው›› ባሉት ጊዜ ‹‹ሰይጣንም ለቅዱስ ሚካኤል አለቃው ነበረ›› ብሎ ነው የመለሰላቸው፡፡
Source:- www.danielkibret.com 

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount