Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ25ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts
Showing posts with label የዮሐንስ ወንጌል የ25ኛ ሳምንት ጥናት. Show all posts

Wednesday, May 30, 2012

አብ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድ ደግሞ ይህን እንዲሁ ያደርጋል- የዮሐንስ ወንጌል የ25ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.5፡18-28)=+=


     ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እነርሱ መዳን ብሎ ወደ ቤታቸው ቢመጣም፣ በኃይልና በሥልጣን የሚያደርገውን ሁሉ ሲያደርግ ቢመለከቱትም መጻሕፍትን ከመመርመር ይልቅ፣ ትንቢተ ነብያትን ከማገናዘብ ይልቅ አይሁድ የራሳቸውን ወግ በመጥቀስ ሊገድሉት ይፈልጉ ነበር፡፡ የሚናገረውን እንኳን ባያምኑ የሚያደርገውን አይተው ወደ እርሱ እንዲመጡ በተገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ይባስኑ ውስጣቸው በቅናት ይቆስል ነበር፡፡ ስለዚህም “ሰንበትን ስለሻረ ብቻ ሳይሆን ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር ስለሚያስተካክል ይህ ሰው ከእግዚአብሔር አይደለም” ለማለት ደፈሩ /ቁ.18/፡፡ ጌታችን ግን አንዳንድ ልበ ስሑታን እንደሚሉት “ስለምን ልትገደሉኝ ትፈልጋላችሁ? እኔ ከአብ ጋር የተካከልኩ አይደለሁም” ወይም “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል እኔም አገለግላለሁ” ሳይሆን “አባቴ እስከ ዛሬ (ቅዳሜ ቅዳሜ) ይሠራል (አንዳንድ ድውይ ይፈውሳል) እኔም እንዲሁ እሠራለሁ (መጻጉዕን ፈወስኩ)” ይላቸዋል /ቁ.17/፡፡ ወንጌላዊው እዚህ ጋር የአይሁዳውያኑ አባባል ትክክል ስለነበረ በሌላ ቦታ /ዮሐ.2፡19/ እንደሚያደርገው ማስተካከያ አላደረገበትም፤ ከዚህ በፊት እንዳደረገውም “አይሁድ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር እንዳስተካከለ ቢያስቡም ክርስቶስ ግን እንዲህ ማለቱ ነበር” አይልም /Saint John Chrysostom Homilies on St. John, Hom 38./፡፡

   ከዚህ በኋላ ስለ ሰው ልጆች መዳን አብዝቶ የሚሻ ጌታችን እንዲህ ይላቸዋል፡- “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም” /ቁ.19/፡፡ ምን ማለት ይሆን? እውነት “ነፍሴን ላኖራትም ላነሣትም ሥልጣን አለኝ” ያለው ጌታ ምንም ሊያደርግ አይችልምን? /ዮሐ.10፡18/፡፡ ወንድሞቼ ይህን በጥንቃቄ ልናስተውለው ይገባል፡፡ ይህ መለኰታዊ ቃል አንዳንዶች እንደሚያስቡት ሳይሆን እንዲህ ማለቱ ነው፡- “እኔ ከራሴ ብቻ አንቅቼ ምንም ምን ሥራ አልሠራም፤ ከአብ በሕልውና ያየሁትን በህልውና ያገኘሁትም እሠራለሁ እንጂ፡፡ የአብ ፈቃድ የእኔ ፈቃድ ናት፤ የአብና የእኔ ፈቃድ እርስ በእርሷ የምትለያይ አይደለችም፡፡ እስከ ዛሬ አብ የወደደውን ሲያደርግ እንደነበረ እኔም እንዲሁ (በተመሳሳይ ሥልጣን በተመሳሳይ ዕሪና) የወደድኩትን አደርጋለሁ፡፡ አብ ይፈውስ እንደነበረ እኔም እፈውሳለሁ፡፡ ስለዚህ አብ አባቴ ነው ስላልኳችሁ አትደነቁ፤ ከአባቴ ጋር የተካከልኩ ነኝ ስላልኳችሁ አትበሳጩ፡፡ እናንተን ለማዳን ብዬ ምንም ከአባቴ ጋር ያለኝን መተካከል እንደመቀማት ሳልቆጥረው የእናንተ የባርያቼን መልክ ብይዝም አብ የሚያደርገውን ሁሉ እኔ ደግሞ ይህን እንዲሁ አደርጋለሁና /ፊል.2፡6/፤ የአብ የሆነ ሁሉ የእኔ ነውና፤ የእኔም የሆነ ሁሉ የአብ ነውና /ዮሐ.17፡10/፡፡ የሆነው ሁሉ በእኔ የሆነው አብ መፍጠር የማይችል ሆኖ ሳይሆን በሥላሴ ዘንድ የፈቃድ ልዩነት ስለሌለ ነው” /ዮሐ.1፡3 Saint AmbroseOf the Holy Spirit Book 2:8:69/። በእርግጥም ክርስቶስ አልዓዛርን ከሞት ሲያስነሣው አብ ምንም አላደረገም አይባልም /ዮሐ.11፡42/፤ ክርስቶስ የዓይነ ሥውሩን ብርሃን ሲመልስለት መንፈስ ቅዱስ ምንም አላደረገም አይባልም /ዮሐ.9፡3/፡፡ የሥላሴ ሥራ በአንድነት በአንድ ፈቃድ የሚደረግ እንጂ በተናጠል የሚደረግ አይደለምና /Saint Augustine. Sermon on N.T. Lessons, 76:9/፡፡

FeedBurner FeedCount