Wednesday, May 23, 2012

ከሁሉ በታች ቁጫጭ ስንሆን ከሁሉም በላይ አደረገን=+=



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ጸሐፊ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ እንደሚነግረን አሁን ካሣው ተከፍሏል፤ አናቅጸ ሲዖል ተሰባብሯል፣ የሰው ልጅም እንደ ድሮ በዕዳ በቁራኝነት ከመያዝ ነጻ ወጥቷል፤ ጌታችንም ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷል፡፡ እንዴት ያለ ፍቅር ነው?
 ተነሥቶም ለአርባ ቀናት ያህል ደቀመዛሙርቱን ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ምሥጢር ሲነግራቸውና ሲያስረዳቸው ቆየ /ሐዋ.1፡3/፤ [ይህ ትምህርት ሊቃውንቱ እንደሚነግሩን መጽሐፈ ኪዳን ይባላል!] “ልባችሁ አይታወክ በእግዚአብሔር እመኑ በእኔም ደግሞ እመኑ፡፡ በአባቴ ቤት ብዙ መኖርያ አለ፡፡ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበረ፡፡ ሥፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና” እያለ ከዚህ በፊት የነገራቸውን እየደገመ የደቀመዛሙርቱን ልብ ሰማያዊውን ሕይወት እንዲናፍቅ ያደርገው ነበረ /ዮሐ.14፡1/፡፡ ሆኖም ግን እየተገለጠላቸው እንጂ ከዚህ በፊት ሲያደርገው እንደነበረ ቀንና ሌሊት ሁሉ ከእነርሱ ጋር በመዋልና በማደር አልነበረም፡፡ አሁን ስለ እኛ ብሎ ዝቅ ያለበት ያ ደካማ ማንነቱ የለምና፤ አሁን ያ የለበሠው ባሕርያችን በአዲስ መንፈሳዊ አካል ተነሥቷልና፡፡ 

Monday, May 21, 2012

የገብረ ንጉሡ ልጅ መፈወስ- የዮሐንስ ወንጌል የ22ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡43-ፍጻሜ)!!


  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


“ከሁለቱ ቀኖችም በኋላ፣ ሳምራውያኑ ከእኛ ጋር ሁን ብለውት ለሁለት ቀናት ቃለ እግዚአብሔርን ሲያስተምራቸው ከቆየ በኋላ፣ እነርሱም የአይሁድ ወይም ደግሞ የሳምራውያን ብቻ ሳይሆን የዓለም ሁሉ መድኃኒት መሆኑን ካመኑና ለሴቲቱ ከነገሯት በኋላ ጌታችን ከዚያ ወጥቶ ወደ ገሊላ ሄደ” /ቁ.43/። ከተመቸን ብላችሁ በአንድ ቦታ አትኑሩ፤ ወጥታችሁ ወርዳችሁ አስተምሩ እንጂ ብሎ አብነት ለመሆን ከሰማርያ ወደ ገሊላ ሄደ /ወንጌል ቅዱስ አንድምታ ገጽ 476/፡፡ 


 ነገር ግን ብዙ ጊዜ ወደ ተመላለሰባት በኋላም አልቀበል ሲሉት “አንቺ ቅፍርናሆም እስከ ሰማይ ከፍ አልሽን? ወደ ሲዖል ትወርጃለሽ“ ብሎ ወደ ተናገረላት ወደ ቅፍርናሆም አልሄደም /ማቴ.11፡23/፤ ምክንያቱም “ነቢይ በገዛ አገሩ እንዳይከበር ኢየሱስ ራሱ መስክሮአልና” /ማቴ.13፡57/ /ቁ.44፣ ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ Homily On The Gospel of John Hom.35/።
 “ወደ ገሊላም በመጣ ጊዜ፥ የገሊላ ሰዎች ራሳቸው ደግሞ ለገቢረ በዓል ወጥቶ ሳለ በኢየሩሳሌም ያደረገውን ተአምራት ሁሉ አይተዋልና አመኑበት” /ቁ.45፣ ዮሐ.2፡23/። እነዚህ ገሊላውያን ምንም እንኳን እንደ ሳምራውያን ያለ ምልክት ባያምኑም ቃሉም ሰምተው ገቢረ ተአምራቱንም አይተው ካላመኑት የአይሁድ ሰዎች ግን ይሻላሉ /ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ ዝኒ ከማሁ/፡፡ 

በእውነት ክርስቶስ የዓለሙ መድኃኒት እንደ ሆነ ዓወቅን፤ አምነንበታልም - የዮሐንስ ወንጌል የ21ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡27-42)


ሰላመ እግዚአብሔር ይብዛላችሁ፡፡
 ደቀ መዛሙርቱ ምግብ ሊገዙ ወደ ከተማ ሄደው ነበር ብለናል /ዮሐ.4፡8/፡፡ አሁን ግን “መጡና ከአንዲት ደሀ ብቻ ሳይሆን ከሳምራይት ሴት ጋር ዝቅ ብሎ በመነጋገሩ ተደነቁ፤ ነገር ግን በግሩም ትሕትናው ስለተደነቁ ምን ትፈልጊያለሽ? ወይም ስለ ምን ትናገራታለህ? ያለ ማንም አልነበረም” /ቁ.27፣ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ Homily On John,Hom.33:3/።
  ወንጌላዊው እንደነገረን ሴቲቱ ውኃ ልትቀዳ ወደ ያዕቆብ ጕድጓድ መጥታ ነበር፡፡ ነገር ግን የክብር ንጉሥ ወደ ልቧ ሰተት ብሎ ሲገባ “ማድጋዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች” /ቁ.28/፡፡  በሐሴት ሠረገላ ተጭናም ወንጌሉን ለማፋጠን ተሯሯጠች፡፡ “ለሰዎችም ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” እያለች መላ ከተማውን ጠራርጋ ታመጣቸው ነበር። የሚገርመው ሴቲቱ የምታመጣቸው ሰዎች እንደ እንድርያስ ወይም ደግሞ እንደ ፊሊጶስ አንድ ወይም ሁለት ሰዎች ብቻ አይደሉም፡፡ መላ ከተማውን እንጂ፡፡ ትጋቷም ከኒቆዲሞስ በላይ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በወልደ እግዚአብሔር ቢያምንም እንደ እርሷ ግን በግልጥ ለመመስከር አልወጣም፡፡ በእውነት ይህች ሴት ከሐዋርያት ጋር ብትተካከል እንጂ አታንሥም፡፡ ሐሳብዋን ብቻ ይግለጥላት እንጂ እንዴት እንደምትነግራቸው እንኳን የቃላት ምርጫ አታደርግም፡፡ እናም “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?”  ትላቸዋለች፡፡ ተጠራጥራ አይደለም፤ መጥተው ራሳቸው ለራሳቸው እንዲወስኑ እንጂ፡፡ ስለዚህም “ኑና እዩ፤ አይታችሁም እመኑ” እያለች ከነፍሳቸው እረኛ ጋር እንዲገናኙ ትፈልጋቸው ነበር፡፡ ሰዎቹም የምትነግራቸውን ነገር ለማየትከከተማ ወጥተው ወደ ጌታችን ይመጡ ነበር” /ቁ.29-30/። የሚገርመው ደግሞ ይህች ሴት አዋልደ ሰማርያን ላለማየት ብላ በጠራራ ፀሐይ ውኃን ለመቅዳት የመረጠች ሴት ነበረች፡፡ አሁን ግን እውነተኛው ፀሐይ ሲነካት ሐፍረቷ እንደ በረዶ ተኖ ጠፋ፡፡ ስለዚህም ቀድሞ ወደምታፍራቸው ሰዎች በመሄድ “አንድ ነብይን ትመለከቱ ዘንድ” ሳይሆን “ያደረግሁትን ሁሉ፣ ምሥጢሬን ሁሉ የነገረኝን ሰው ትመለከቱ ዘንድ ኑ” እያለች ሕዝቡን ጠራቻቸው /St.John Chrysostom, Hom.34:1/፡፡
 ይህም ሲሆን ሳለ ደቀ መዛሙርቱ “ጌታችን ብዙ መንገድ በመሄድ ደክሟልና፤ ደግሞም ጠራራ ፀሐይ ነውና

የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ- የዮሐንስ ወንጌል የ20ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.4፡16-26)!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
ሳምራይቱ ሴት ያንን የሕይወት ውኃ፣ ያንን ዳግመኛ የማያስጠማ ምንጭ፣ ያ በደስታ የሚቀዱት መለኰታዊ ማየ ሕይወት ለመጠጣት ጎምጅታለች፡፡ ከወራጁ ውኃ ይልቅ ዕለት ዕለት ከሚፈልቀው ማየ ገነት፣ ከጸጋ መንፈስ ቅዱስ ትጠጣ ዘንድ ቸኩላለች፡፡ ስለዚህም፡- “ከዚህ አንተ ከምትለኝ ውኃ እንዳልጠማ ስጠኝ፤ ከእንግዲህ ወዲህ አባቴ ያዕቆብ ካስረከበኝ ጕድጓድ ይልቅ አንተ ከምትሰጠኝ ምንጭ እጠጣ ዘንድ እሻለሁ” ትሏለች፡፡ እንዴት ያለች ጥበበኛ ሴት ነች? እንዴት ያለች የምትደንቅ ሴት ነች? እንዴት ያለች እውነትን የተጠማች ነፍስ ነች? የጥበብ ባለቤት የሆነው ጌታችንም ሴትዮዋ ይበልጥ ኃጢአቷን እንድትናዘዝ፤ እንደ አለላ የሆነው ማንነቷ እንደ አመዳይ ነጽቶላት የሰላሙን ንጉሥም በልቧ ትሾመው ዘንድ በጥበብ ፡-“ሂጂና ባልሽን ጠርተሽ ወደዚህ ነዪ” ይላታል/ቁ.16፣ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ Homily.32/።
 
 ስለዚህም ሴቲቱባል የለኝም” ስትል ያለሐፍረት ትናገራለች፡፡ ጌታችንም ወደሚፈልገው አቅጣጫ ስለመጣችለት የሕይወቷን ምሥጢር፡- “ባል የለኝም በማለትሽ ውሸት አልተናገርሽም፤ ከዚህ በፊት አምስት ባሎች ነበሩሽና፡፡  አሁን ከአንቺ ጋር ያለው እንኳን ባልሽ አይደለም፤ በዚህስ እውነት ተናገርሽ” በማለት ይነግራታል /ቁ.18፣ አባ ሄሮኒመስ, Letter 108፡13/፡፡ እንዲህ ማለቱ ነበር፡- “ልጄ! እንዲህ በማለትሽ እውነት ተናግረሻል፡፡ ምክንያቱም አንቺ የምትመኪባቸው አምስቱ የሙሴ መጻሕፍት ድኅነተ ነፍስን ሊሰጡሽ አልቻሉምና፤ ጽምዓ ነፍስሽን ሊያረኩልሽ አልቻሉምና፡፡ እነርሱ ብቻ ሳይሆኑ በዚህ በሰማርያ የምታመልኪው ስድስተኛው ጣዖትም ሊያድንሽ አልቻለም፡፡ ስለዚህ እነዚህን ሁሉ ትተሸ፣ ከእነዚህ ሁሉ ጋር ተፋተሽ ከነፍስሽ እጮኛ ከእኔ ጋር መጋባት ይኖርብሻል”፡፡

FeedBurner FeedCount