Tuesday, July 17, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- የመጨረሻው ክፍል (ክፍል አምስት)!


      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  ተወዳጆች ሆይ! እንደ እግዚአብሔር ሐሳብ ለመማማር የጀመርነው ርእስ የሚያልቅ ስላልሆነ እናንተ በይበልጥ ከሊቃውንት ከመጻሕፍት እንድታዳብሩት እየጋበዝኩኝ እኛ ዛሬ እንጨርሳለን፡፡ መልካም ንባብ፡፡
1. ደሙ ከሞተ ሥራ ሕሊናን የሚያነጻ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት መሥዋዕቶች የጊደሮች፣ የኮርማዎች፣ የፍየሎች የሆነ ደመ እንስሳ ነበር፤ የዘመነ ሐዲስ ግን በደመ ክርስቶስ የተደረገ ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ መሥዋዕቶች ያለ ፈቃዳቸው ያለ ውዴታቸው የሚሞቱ እንስሳት ነበሩ፤ የዛሬው ግን ሞት ይሁንብኝ ይደረግብኝ ብሎ ያለ ኃጢአቱ እንደ ኃጢአተኛ ተቈጥሮ በፈቃዱ እስከ ሞት ድረስ የታዘዘ የእግዚአብሔር በግ ነው፡፡ የእነዚያ መሥዋዕት ነውርና ነቀፋ ባለባቸው አገልጋዮች የሚቀርብ ነበር፤ የሐዲስ ኪዳን መሥዋዕት ግን ነውርና ነቀፋ በሌለበት በንጹሑ ኢየሱስ የተከናወነ ነው፡፡ የእነዚያ መሥዋዕት ሞት በሚይዛቸው በእንስሳት ደም የሚከናወን አገልግሎት ነበር፤ የሐዲስ ኪዳኑ መሥዋዕት ግን ትንሣኤና ሕይወት በሆነው በክርስቶስ የተከናወነ አገልግሎት ነው፡፡ የመጀመርያው ኪዳን ለጊዜው የሆነ ንጽሕናን የሚሰጥ ነበር፤ የሊቀ ካህናችን የኢየሱስ ክርስቶስ አገልግሎት ግን ከጊዜና ከቦታ ቀመር ውጪ (Beyond Time) የሆነ ዘለዓለማዊ ንጽሕናን የሚሰጥ አገልግሎት ነው፡፡ የቀደመው ኪዳን በምሳሌና በጥላ በሆነ በደመ እንስሳ የሚከናወን ነበር፤ የዛሬው ግን አማናዊ በሚሆን በንጹሑ በደመ ክርስቶስ ተደርጓል፡፡ የቀደመው መሥዋዕት እሳት አንድዶ እንጨት ማግዶ የሚሠዋ ነበር፤ የዛሬው ግን በመንፈስ ቅዱስ እሳትነት የተደረገ ነው፡፡ እንዲህም ስለ ሆነ የእነዚያ መሥዋዕት ደመ ነፍስን (ሥጋን) ብቻ የሚቀድስ ነበር፤ የዛሬው ግን… ደመ ክርስቶስ ግን ሕያው መሥዋዕት ስለሆነ ሁለንተናን ሕያውና ቅዱስ የሚያደርግ ነው፤ ሕሊናን ከሞተ ሥራ የሚያነጻ ልዩ መሥዋዕት ነው፡፡ ሐዋርያው እንዲህ ይላል፡- “ደመ ላህም ደመ ጠሊ የጊደርም አመድ ሥጋዊ ኃጢአትን የሚያነጻ ከሆነ፣ በኃጢአት ያደፉትን የሚያከብራቸው ከሆነ በመንፈስ ቅዱስ እሳትነት ራሱን ለእግዚአብሔር ነውር ነቀፋ የሌለበት የዘለዓለም መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ የኢየሱስ ክርስቶስ ደምማ ከኦሪት፣ ከኃጢአት፣ ከፍዳ፣ ከፍቅረ ንዋይ ልቡናችንን እንደምን ያህል ያነጻ ይኾን?” /የዕብ.9፡13-14 ትርጓሜው፣ገጽ.441/፡፡  ስለዚህ ደሙ ከሞተ ሥራ ሕሊናን የሚያነጻ ሊቀ ካህናት አለን፡፡
2. የሐዲስ ኪዳን መካከለኛ (ምርጥ) ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያው “ስለዚህም የፊተኛው ኪዳን ሲጸና ሕግን የተላለፉትን የሚቤዥ ሞት ስለ ሆነ፥ የተጠሩት የዘላለምን ርስት የተስፋ ቃል እንዲቀበሉ እርሱ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ ነው ይላል /ዕብ.9፡15/፡፡ እውነት ነው! ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለወንጌል መምህር ለመንግሥተ ሰማያትም አስታራቂ የሐዲስ ኪዳን ብቸኛው መካከለኛ ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን ክፍል በተረጐመበት አንቀጽ ምን ማለት እንደሆነ እንዲህ ያብራራልናል፡- “መካከለኛ ማለት ምን ማለት ነው? መካከለኛ መካከለኛ ለሆነለት ነገር ባለቤት (ተጠቃሚ) አይደለም፡፡ ለምሳሌ አማጭ (መካከለኛ) ለሚያገባ ሰው ሚስት ለማግባት አጋዥ ይሆነዋል እንጂ እርሱ የሚያገባ ሙሽራ አይደለም፡፡ በጌታም ዘንድ እንዲህ ነው (የተሠዋው እጠቀም ብሎ አይደለም)፡፡ ወልድ ዋሕድ ጌታ በአባቱና በእኛ መካከል አስታራቂ ሆነ፡፡ አብ በሠራነው ኃጢአት ፈርዶብን መንግሥቱን ሊያወርሰን አልወደደም ነበርና ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው የባሕርይ ልጁ በእርሱና በእኛ መካከል አስታራቂ ሆነ፡፡ እርሱንም ደስ አሰኘው፡፡ ከዚያም እኛን ወደ ልጅነት ልጅነትንም ወደ እኛ ጠራ፤ በሞቱ ከአብ ዘንድ መንግሥተ ሰማያትን አስገኘልን፡፡ ሕጉን በማፍረስ በነበርን ጊዜ ሞት ተገባን፤ እርሱ ግን ስለ እኛ በሞተ ጊዜ ሳይገባን ለመንግሥተ ሰማያት የበቃን አደረገን፡፡ አባት ለልጁ እንደሚሰጥ ቀድሞ ልጅነትን ሳንጥር ሳንግር እንዲያው ሰጠን”  /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.16፡33-48/፡፡ አዎ! በበደልነው ጊዜ ሕጉ (ኦሪት) እንደ ፍርድ ሆነብን (የሚያስፈርድብን ሆነ)፡፡ ለማዳን የሚሞት አንድ ስንኳ ጠፋ፡፡ ሊቀ ካህናችን ግን ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከራሱና ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያስታርቀን ዘንድ የባርያውን መልክ ይዞ (የእኛን ባሕርይ ነሥቶ) ትምክህታችን ከምትሆን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ሰው ሆነ፤ አምላክ የሆነ ሰው ሰውም የሆነ አምላክ (መካከለኛ) ሆነ፤ በተዋሕዶ አንድ አካል አንድ ባሕርይ የሆነ ሥግው ቃል (Incarnated Word)፣ አምላክ ወሰብእ (መካከለኛ) ሆነ፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው በሥግው ቃልነቱ ስለ እኛ ባይሞት ኖሮ ኦሪት ደካማ ከመሆኗ የተነሣ ባልዳንን ነበር፡፡ ስለዚህ እንደ ሰውነቱ ዘመዳችን እንደ መለኰትነቱ ፈጣርያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዲስ ሕግ ለወንጌል መምህር ለመንግሥተ ሰማይ አስታራቂ ሆነ፤ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ያለ ብቸኛ መካከለኛ ሆነ፡፡
3. ራሱን በመሠዋት ኃጢአትን የሻረ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ደጋግመን እንደተናገርነው የቀደመው ሊቀ ካህናት ብዙ ጊዜ ብዙ መሥዋዕት ሠዋ፤ ሊቀ ካህናችን ግን አንድ ጊዜ ራሱን ሠዋ፡፡ የቀደመው ሊቀ ካህናት ገንዘቡ ባይደለ በሌላ ደም አገለገለ፤ የዛሬው ግን እውነት ገንዘቡ በሚሆን በራሱ ደም አስታረቀ፡፡ ምሥዋዑ እርሱ ነውና፤ የሠዋው እርሱ ነውና፤ የተሠዋውም እርሱ ነውና በራሱ ደም አገለገለ፡፡ ፈቃዱን እንደ ካህን ሥጋው እንደ መንበር አድርጎ ነፍሱን አንድ ጊዜ ሠዋ፡፡ አሁን ግን በዓለም ፍጻሜ (ኑሮ ኑሮ አምስት ሺ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም) ራሱን በመሠዋት ኃጢአትን ሊሽር (ያጠፋት ዘንድ) አንድ ጊዜ ተገልጦአል” /ዕብ.9፡26/ ተብሎ እንደተጻፈ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ኃጢአት ያስወገደው ራሱን በመሠዋት እንጂ የጊደርና የኮርማ ደም በማፍሰስ አይደለም፡፡
4. ያዳናቸውን ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመውሰድ ሁለተኛ የሚገለጥ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያው እንዲህ ይላል፡- “ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው፥ እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፥ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል” /ዕብ.9፡27-28/፡፡ ምን ማለት ነው? ውሎ ውሎ ከቤት ኑሮ ኑሮ ከመሬት እንዲሉ ለሰው ኑሮ ኑሮ ሞት እንዲቆየው ኋላም መቃብር እንዲከተለው ሁላችንም ከፊት የሚጠብቀን አንድ ጊዜ “መሞት” አለ፡፡ ሆኖም ግን ይህ “ሞት” ክርስቲያኖች ለምንሆን ለእኛ ከድካማችን ዕረፍት እንጂ እውነተኛ ሞት አይደለም፤ ሞት የሚሠለጥንብን አይደለም፡፡ ሞትስ ሰው የኃጢአቱን ትብትብ ተሸክሞ ሳለ ሥርየተ ኃጢአትን ሳያገኝ መንግሥተ ሰማያትን ሲያጣ ነውና፡፡ ስለዚህ ከድካም ካረፍን በኋላ የዘለዓለም ሕይወት አለን፡፡ ክርስቶስም የብዙዎችን ሰዎች ኃጢአት ያስተሠርይ ዘንድ ኑሮ ኑሮ አምስት ሺ አምስት ዘመን ሲፈጸም አንድ ጊዜ ራሱን ሠዋ፡፡ አዎ! በአዳም ምክንያት የመጣው ሞት ሁሉን ለማጥፋት መጣ፡፡ ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይሁንና ጌታችንም ኃጢአት ሳይኖርበት ስለ እኛ ኃጥእ አሰኘ፡፡ እርሱ ንጹሕ ሲሆን “ከኃጥአን ጋር ተቈጠረ” /ኢሳ.53፡12/፤ የእኛን ኃጢአት የራሱ እንደ ሆነ ቈጥሮ ወደ መስቀል ወጣ /2ቆሮ.5፡21/፡፡ ማመንን ደኅንነትን ለወደዱም አዳናቸው፡፡ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ብሎ /ሉቃ.23፡34/ ሥርየተ ኃጢአትን ሰጣቸው፤ ይቅር አላቸው፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ግን የሰውን ኃጢአት ለመሸከም ሳይሆን ያዳናቸውን ወደ አዘጋጀላቸው ርስት ወደ ሀገራቸው ለመውሰድ ይመጣል፡፡ የዘይት ማሰሮአቸውን ሞልተው ተስፋ ለሚያደርጉት፣ ለሚጠባበቁት ለሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል፤ ይመጣላቸዋል፡፡ ዓለምን ለማሳለፍ፣ ጻድቃንን ለማወደስ፣ ኃጥአንን ለመውቀስ፣ ሞትንና ዲያብሎስን ወደ ጥልቁ በመጣል ለመደምሰስ፣ መንግሥቱንም ለምእመናን ለማውረስ ይመጣል፡፡ ወንድሜ!... እኅቴ!... የኢየሱስን መምጣት ትጠባበቃለህን/ ትጠባበቂያለሽን? እንግዲያው ከወንጌላዊው ጋር፡- “ይህን የሚመሰክር አዎን በቶሎ እመጣለሁ ይላል፤ አሜን ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና” እንበል /ራዕ.22፡20/፡፡

      ስናጠቃልለው ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ እንዲደርሱ የሚወድ ደግሞም  የምናመልከው እግዚአብሔር አንድ ነው፡፡ እንዲያድነንና ወደ እውነት (ወደ ራሱ) ሊመራን ቤዛም ሊሆነን በተለየ አካሉ ትምክሕታችን ከምትሆን ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሥጋንና ፍጹም ነፍስን ተዋሕዶ የመጣም አንዱ እውነት እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እንዲህ ስለሆነም መካከለኛ መባልን ተገባው፡፡ “እግዚአብሔር አባቴ ነው”፤ “በአባቴ ስም መጣሁ”፤ “እኔና አብ አንድ ነን” ብሎ የመሰከረውን ምሥክርነት ያልተቀበሉት ባይቀበሉትም በገዛ ዘመኑ (በመዋዕለ ሥጋዌው) ምስክርነቱ ነበረ /1ጢሞ.2፡4-6/፡፡ እኛም ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ሆነን ይህን እውነት እንናገራለን፤ አንዋሽም፡፡ ብዙዎች ሌላ መካከለኛ እንዳለን አድርገው ቢከሱንም “ከአንዱ ሊቀ ካህናችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ውጪ ሌላ መካከለኛ የለንም” ብለን እንመሰክራለን፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የታረቅንበት የመንግሥተ ሰማያትን መንገድ በደሙ የመረቀልን ሊቀ ካህናችን አንድ ነው፤ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ይባላል ብለን እንመሰክራለን፡፡ የቅዱሳንን ምልጃ ከኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህንነት ጋር ፈጽሞ የማይገናኝ ነውና “ሌላ መካከለኛ” የለንም ብለን እንመሰክራለን፡፡
አኰቴት ወክብር ለሊቀ ካህንነ ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስለ አቡሁ ወምስለ መንፈሲሁ እስከ ለዓለም አሜን!! 

Monday, July 16, 2012

ጌታ ሆይ ከአንተ ወደ ማን እንሄዳለን?-የዮሐንስ ወንጌል የ31ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.6፡53-ፍጻሜ)!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
   ስለ ሰማያዊ ነገር፣ ስለ መንፈሳዊ ቃል በምንናገርበት ጊዜ አፍአዊ ምድራዊ የሆኑ አስተሳሰቦችን ሁሉ ከእኛ ዘንድ የራቁ መሆን ይገባል፡፡ ወደ አንድ ምድራዊ ንጉሥ በቀረብን ጊዜ ሐሳባችን ልባችን ሁሉ በምንም ነገር እንደማይባክን መንፈስ ቅዱስ ሲናገረንም ከዚሁ በበለጠ በአርምሞና በአንቃዕዶ ሆነን ልንቀርብ ልናደምጥ ይገባናል፡፡ ዛሬ የምንማማረው ትምህርትም ይህን የመሰለ ልብ የሚጠይቅ የሚፈልግ ነው፡፡ የአይሁድ ሰዎች አቀራረባቸው ሁሉ እንዲህ አፍአዊ፣ ሥጋዊና ደማዊ ስለ ነበረ ጌታችን በሚነግራቸው የሕይወት ቃል ግራ ሲጋቡ፣ ሲጨቃጨቁ፣ ሲያንጐራጕሩ እንመለከታቸዋለን፡፡ “ይህ ሰው ሥጋዉን እንበላ ዘንድ እንደምን ሊሰጠን ይችላል? አንዳንድ ጉርሻስ እንኳ ይደርሰናልን? ደግሞስ ዕሩቅ ብእሲ ሥጋዉን ቢበሉት ደሙንም ቢጠጡት ደዌ ይሆናል እንጂ ሕይወት ይሆናልን?” እያሉ ሲታወኩበት፣ ሲከራከሩበት እናስተውላቸዋለን /ቁ.52/፡፡ ጌታችን ግን “የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ” በማለት  ሥጋዉን ሊበሉት ደሙንም ሊጠጡት መስጠት የሚቻል ብቻ ሳይሆን ይኸን ሰማያዊ መብል ይኸን ሰማያዊ መጠጥ አለመብላት አለመጠጣትም ዘለዓለማዊ ሕይወትን የሚያሳጣ እንደሆነ ይነግራቸው ያስረዳቸው ነበር /ቁ.53/። ንግግሩንም በዚህ ያበቃ አይደለም፤ ጨምሮም፡-ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው፤ ከገቡ መውጣት ካገኙ ማጣት የሌላት የማታልፍ መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳል፥ እኔም በመጨረሻው ቀን በዕለተ ምጽአት በክብር አስነሣዋለሁ፤ አድነዋለሁ” አላቸው እንጂ /ቁ.54፣ St. John Chrysostom, Hom.47./ 

   ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ገና ወንጌሉን ሲጀምርልን “ቃልም ሥጋ ነሣ” በማለት ነገሩን ያቆመ አይደለም፡፡ ፍጹም ተዋሕዶአቸውን ለማሳየት “ቃልም ሥጋ ሆነ” አለን እንጂ /ዮሐ.1፡14/፡፡ ይህን ሲልም ከእግዚአብሔር ዘንድ የነበረው ቀዳማዊ ቃል ባሕርይውን ለውጦ ሥጋ ሆነ ማለቱ አይደለም፡፡ ሥጋም ወደ መለኰትነት ተለወጠ አላለንም፡፡ ቃል የቃልነት ባሕርይውን ሥጋም የሥጋ ባሕርይውን ይዞ በፍጹም ተዋሐደ እንጂ፡፡ ሕይወትን ላጡ ፍጥረታት ሕይወትን የሚሰጥ ቀዳማዊ ቃል የሰው ልጆች ሊረዱት ሊመረምሩት ከሚችሉት በላይ በሆነ በተዋሕዶ ምሥጢር የፈጠረውን ሥጋ ተዋሐደ፡፡ ለሥጋም የመለኰትን ባሕርይ ሰጠው፡፡ ሥጋም የመለኰትን ባሕርይ ገንዘብ አደረገ፡፡ በእኛ ተፈጥሮ ውስጥ የነበረውን ሞት በእርሱ ባሕርይ አጠፋልን፤ ሥጋ በባሕርዩ ሕይወት የሆነ ቃልን ተዋሕዷልና የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን የሚበላ ክቡር ደሙን የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው፡፡ እንዲህም ስለሆነ ጌታችን “በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ” በማለት ተናገረ፡፡ ሆኖም ግን “ሥጋዬ ያስነሣዋል” አላለም፤ “ሥጋዬን የበላውን ደሜንም የጠጣውን ሰው አስነሣዋለሁ” እንጂ፡፡ ከተዋሕዶ በኋላ ምንታዌ የለምና፡፡… ስለዚህ ምንም እንኳን ሞት የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሳ አንበሳ በዙርያችን ቢዞርም ሥጋችንንም ልናስወግደው ወደማንችለው መበስበስ ሊቀይረው ቢሞክርም ክርስቶስ በእኛ እኛም በክርስቶስ ከሆንን ግን በእርግጠኝነት (ለክብር ለሕይወት) እንነሣለን፡፡ ሥጋው እስራኤል ዘሥጋ ጊዜአዊ የሥጋን ረሀብ እንዳስታገሰላቸው መና ያይደለ ዘላለማዊ ሕይወትን የሚያድል እውነተኛ መብል ነውና፤ ደሙም እስራኤል ዘሥጋ በገዳም ጊዜአዊ የሥጋ ጥማቸውን እንዳረካላቸው ውኃ ያይደለ እውነተኛ መጠጥ ነውና /ቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ፣ በዲ/ን ታደለ ፈንታው ገጽ 154/፡፡ 

    ስለዚህም ነው በሰዋዊ አመክንዮ ሲታወኩ ለነበሩ አይሁድ፡- ሥጋዬ እውነተኛ (የማያልፍ፣ የማይሻር፣ የማይለወጥ )መብል ነው፤ ደሜም እውነተኛ (የማያልፍ፣ የማይሻር የማይለወጥ) መጠጥ ነው፡፡ የዚህ ዓለም መብል እውነተኛ አይደለም፡፡ ማታ ተበልቶ ጧት ይርባልና፤ ጧት ተበልቶ ማታ ያስፈልጋልና፡፡ ኃላፊ ጠፊ ስለሆነም በቀን ብዙ ጊዜ ይበላል፡፡ እኔ የምስጣችሁ መብል፣ እኔ የምሰጣችሁ መጠጥ ግን በኃጢአት ካላሳደፉት በቀር ቀዋሚ ዘላለማዊ ነው፡፡ በአሚን በንጽሕ ሆኖ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ ግን በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ (በልግስና በጸጋ) ተዋሕጄው እኖራለሁ” የሚላቸው /ቁ.55-56/። አዎ! ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ብቻ ሳይሆን ከውጪ ያሉትንም በክርስቶስ አምነውና በስሙ ተጠምቀው ወደዚሁ ቅዱስ ምሥጢር እንዲቀርቡ እንዲቀበሉትም የምታበረታታቸው ስለዚሁ ነው፡፡ መዝሙረኛው እንደተናገረ፡- “ደሙ የሰውን ነፍስ ደስ የሚያሰኝ መጠጥ፣ ሥጋዉም ኃይለ ነፍስን የሚያፀና መብል ነውና” /መዝ.104፡15 ትርጓሜው፣ Saint Ambrose, On the Mysteries 9:55, 58. /፡፡

  ጌታችን አሁንም ከማር የጣፈጠ ሕይወትም የሆነ ቃሉን ይቀጥልና እንዲህ ይላቸዋል፡- “ሕያው አብ (ለተዋሕዶ) እንደ ላከኝ እኔም ከአብ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ ስለተወለድኩ ሕያው ነኝ፥ እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ (በጸጋ ስለምዋሐደው) ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል። አባቶቻችሁ መናውን በገዳም በልተው እንደ ሞቱ ያይደለ ከሰማይ የወረደ ኅብስት ይህ ነውና (ሥጋዬ ነውና)፡፡ ይህን እንጀራ የሚበላም ለዘላለም ሕያው ሆኖ ሞተ ነፍስ (ትንሣኤ ዘለሐሳር) ሳይኖርበት በተድላ በደስታ በሕይወት ይኖራል”/ቁ.57-58፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታው ገጽ 488/፡፡

  ነቢዩ ሚልክያስ እንደተናገረው ይህ የአይሁድ ዓይነት ቁርባን ያይደለ ንጹሕ የዘለዓለምንም ሕይወት የሚሰጥ ቁርባን ነው /ሚል.1፡10-11,St. Irenaeus Adv. Haer. 4:17:5, 6./፡፡

    በነቢዩ ኢሳይያስ “በስውር ወይም በጨለማ ምድር ስፍራ አልተናገርሁም” /ኢሳ.45፡19/ እንዳለ በቅፍርናሆም ባለ በምኵራብ ሲያስተምራቸው ይኸን (በምሳሌ ሳይሆን በግልጥ እውነተኛ ሥጋዬ ነው፤ እውነተኛ ደሜ ነው እያለ ስለ ሥጋወደሙ) ነገራቸው፤ አስተማራቸው” /ቁ.59/ ተወዳጆች ሆይ! ሥጋዉንና ደሙን ምሳሌ አለማለቱን እናስተውል፡፡ አምሳል አምሳል እንጂ እውነተኛ አይደለምና፡፡ አንድ ሰው መታሰብያን ብቻ ተቀብሎ ለዘለዓለም በሕይወት ከእግዚአብሔር ጋር መኖር አይችልምና፡፡ ለአማናዊው የክርስቶስ ጥምቀት ምሳሌ የነበረችው የኦሪት የውኃ መታጠብ የዘለዓለም ድኅነት መስጠት የማትችል ይልቁንም ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ የምታስቀር እንደሆነች ሁሉ “ሥጋውና ደሙ እውነተኛ መብል አይደለም፤ ምሳሌ መታሰብያ እንጂ” የሚሉም የዘለዓለም ሕይወት የሌላቸው ይልቁንም ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ የቀሩ የወጡ ናቸው፡፡

  ጌታችን ስለ ሁለት ምክንያት በምኵራብ አስተማራቸው፡፡ አንደኛ ብዙ ሕዝብ ባለበት ቦታ በማስተማሩ ምክንያት ብዙዎች በእርሱ ያምናሉና፡፡ ሁለተኛ እርሱ ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ጋር ፍጹም ተቃርኖ እንደሌለው እነርሱም (አይሁድም) እንደሚያስቡት እርሱ የእግዚአብሔር ተቃዋሚ እንዳልሆነ ያስረዳቸው ዘንድ በምኵራብ አስተማራቸው /St.John Chrysostom, Ibid/፡፡

   ከደቀ መዛሙርቱም ብዙዎች ይኸን (የምሥጢረ ቁርባኑን ትምህርት) በሰሙ ጊዜ ረቀቀባቸው ራቀባቸውና፡-ይህ የሚያስጨንቅ ንግግር ነው፤ ማን ሊሰማው ማንስ ልብ ሊለው ይችላል? የሰው ሥጋስ እንደምን ሕይወትን ሊሰጥ ይችላል?አሉ /ቁ.60, St. Augustine,On the Gospel of St. John, tractate 27:1./። ልብ ያመላለሰውን ኩላሊት ያጤሰውን የሚያውቅ /ዕብ.4፡12/ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ደቀ መዛሙርቱ በዚህ ምክንያት እንደታወኩ በልቡ አውቆ፡-ይህ ያሰናክላችኋልን? እንግዲህ ወልደ እጓለ እመሕያው (የሰው ልጅ- ክርስቶስ) ቀድሞ ወደ ነበረበት (ያስተውሉ! እንዲህ ማለቱ ሥጋ ከጥንት ነበረ ከሰማይም ይዞት ወረደ ማለት ሳይሆን ቀዳማዊ ከሆነው ቃል ጋር በተዋሕዶ አንድ ባሕርይ አንድ አካል መሆኑን መግለጽ ነው!)ሲያርግ ብታዩ እንደምን ደንቃችሁ ይሆን?  ሥጋዬ ሕይወትን እንደሚሰጥ በነገርኳችሁ ጊዜ ልባችሁ ከታወከ ሳርግ ብታዩኝ ‘ማ ምን ልትሉ ነው? ዕሩቅ ብእሲ ሲሆን እንደምን እንደ ወፍ ወደ ላይ ሊበር ሊወጣ ቻለ ልትሉ ነውን? ይህ ግን ለዕሩቅ ብእሲ የማይቻል ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህን አፈር የነበረው ሥጋ እንዲህ በተዋሕዶ አክብሬ የባሕርይ አምላክ እንዳደረግኩት ሁሉ ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ያደረኩትም እኔ ነኝ፡፡ የእኔን ሰው የመሆን ምሥጢር (ምሥጢረ ተዋሕዶን) በመረመራችሁ ባስተዋላችሁ ጊዜ ሰው የሆንኩት እኔ የሚያድን መለኰት እንደሆንኩ፤ ዕሩቅ ብእሲ ግን አንዳች እንደማይጠቅም (ሕይወትን እንደማይሰጥ) ትገነዘባላችሁ፡፡ ስለዚህ እኔ የነገርኋችሁ ቃልም መንፈስ (ረቂቅ) ነው፤ ሕይወትም ነውና በግዙፍ አእምሮ (እኔን ወልደ ዮሴፍ በሚል ልቡና) ሳይሆን በውስጣችሁ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ተረዱት፤ በእምነትም ተቀበሉት። ይህ ሥጋ አስቀድሜ እንደነገርኳችሁ ሕይወት የሆንኩትን እኔን (ዮሐ.1፡5) ተዋሐዷልና ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው፡፡ ነገር ግን ከእናንተ ይህን የማያምኑ አሉ” አላቸው /ቁ.61-63፣ St.Cyril Of Alexandria, Ibid/።

  ጌታችን የማያምኑት እነማን እንደ ሆኑ (አይሁድ ፈሪሳውያን እንደሆኑ) አሳልፎ የሚሰጠውም ማን እንደ ሆነ (ይሁዳ እንደሆነ) ከጥንት ጀምሮ ያውቅ ነበርና እንዲህ አላቸው /ቁ.64፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ፣ ገጽ 489/።

  አሁንም ጨምሮ እንዲህ አላቸው፡- እስራኤል ዘሥጋ ባለማመናቸው ምክንያት ዕረፍተ ፍልስጥኤምን ሳይወርሱ እንደቀሩ ሁሉ አንድ ሰው በልቡ ፈቅዶ ወዶ ከዚያምዕውቀቱ ከአባቴ (ረድኤተ እግዚአብሔር) የተሰጠው ካልሆነ በቀር ወደ እኔ ሊመጣ በእኔም ማመን የሚቻለው የለም፤ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያትን መውረስን አይቻለውም ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ”። እንዲህ ስላላቸውም ከሕዝቡ ወገን ብዙዎች ወደ ኋላ ተመለሱ፤ ወደ ፊትም ከእርሱ ጋር አልሄዱም። በጌታ ማመን ምርጫቸው አልነበረምና “ጽድቅ በዕድል ከሆነስ እንግዲያ ምን ያደክመናል?” በማለት የራሳቸውን አመክንዮ በመስጠት ጌታን ከመከተ ቀሩ /ቁ.65-66/፡፡ ማየት የተሳናቸው ሰዎች ከብርሃን ይለቅ በጨለማ መቀመጥን ይወዳሉ፤ ዓይነ ልቡናቸው ከማመን የታወሩ ሰዎችም ከፀሐይ ከክርስቶስ ርቀው በጨለማ መኖርን ይመርጣሉ /ቅ.ቄርሎስ ዘእስክንድርያ፣ ዝኒ ከማሁ/፡፡

   ጌታችንም ሰዎቹ በፍቃዳቸው ወደ ኋላ እንደተመለሱ አይቶ ለአሥራ ሁለቱ ደቀመዛሙርቱ (ያለፈቃዳቸው ይነዳሉ የሚል ነገር እንዳይኖርና ወደው ፈቅደው ሊከተሉት እንደሚገባ ሲያስረዳቸው)፡-እናንተም ልትሄዱ ትወዳላችሁን?” አላቸው /ቁ.67፣ Cyprian the Martyr Letter 59 to Cornellius: 7./። ስምዖን ጴጥሮስ ግን፡-ጌታ ሆይ! የዘላለም ደኅንነት የሚሰጥ ትምህርት ከአንተ ዘንድ እያለ ወደ ማን እንሄዳለን? ከሕይወትስ ወጥተን ወዴት እንሄዳለን?  እኛስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጁ ክርስቶስ እንደ ሆንህ አምነንብሃል፤ የዘላለምን ሕይወትም በቅዱስ ሥጋህና በክቡር ደምህ ልትሰጠን እንደመጣህ አውቀናል ተረድተናልም” ብሎ መለሰለት /ቁ.68-69፣ Saint Augustine,27:9/። ጌታችንም፡-እናንተ እንድታውቁት ብዬ እንጂ አሥራ ሁለታችሁንማ እኔስ ከፍጹም ፍቅሬ የተነሣ የመረጥኋችሁ አይደለምን? ነገር ግን ከእናንተ አንዱ የእኔን ፍቅር ያላስተዋለ ሰይጣን (መስተቃርን መስተጻርር) ነው” ብሎ መለሰላቸው /ቁ.70/።

 ይህን ነገር (እስከሚያሲዘው ድረስ በግልጽ ሳይሆን በምሥጢር) የተናገረ ስለ ስምዖን ልጅ ስለ አስቆሮቱ ይሁዳ ነው፤ ከአሥራ ሁለቱ አንዱ የሆነ እርሱ አሳልፎ ይሰጠው ዘንድ አለውና /ቁ.71/፡፡ ጌታችን እንዲህ ስላለም ከሁሉም ይልቅ ጴጥሮስ በእጅጉ ታውኮ ነበር /ዮሐ.13፡24/፡፡ ይህም የሆነው ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ አስቀድሞ ጌታን “ጌታ ሆይ! መከራ መስቀል ከቶ አይሁንብህ” ሲለው “ወደኋላዬ ሂድ አንተ ሰይጣን” ብሎት ስለነበር አሁንም ከእናንተ አንዱ ሰይጣን ነው ሲል “እኔ እሆንን?” በማለት ነበር /St.John Chrysostom, Ibid/።

   ወዬ አባት ሆይ! በሲና በረሐ ምድራዊ መብልን በልተው ምድራዊ መጠጥንም ጠጥተው እንደሞቱ እንደነዚያ እንዳንሞት ሰማያዊ መብል ሰማያዊ መጠጥ ሆነህ መጥተህ ሳይገባን ስለ ሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ ከመጀመርያው አዳም ጋር እንዳንሞት ይልቁንም ከሁለተኛው አዳም (ከአንተ ጋር) የዘለዓለም ሕይወት እንዲኖረን ራስህን መብልና መጠጥ አድርገህ ስለሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ እንግዲያውስ አባት ሆይ! ከምድራዊ መብል ጋር ስንታገል ካዘጋጀህልን ሰማያዊ ማዕድ (ከቅዱስ ሥጋህና ከክቡር ደምህ) የራቅን እንዳንሆን ይልቁንም በፍርሐትና በረዐድ ሆነን እንድንቀርብ እንድንቀበል እርዳን፡፡ ይህን ሥጋህን በልተን ይህንንም ደምህን ጠጥተን አንተ በእኛ እኛም በአንተ እንድንኖር እንድትዋሐደን እርዳን፡፡ አባት ሆይ! ሕይወት የሆነውን፣ ደኅንነትም የሚገኝበትን ቃልህን ሰምተናል፡፡ መድኃኒታችን ሆይ! ታድያ ከአንተ ወዴት እንሄዳለን? ፍቅር ከሆንከው ከአንተ ርቀንስ ምን ሕይወት አለን? ቅዱስ አባት ሆይ የቸርነትህን ሥራ ሥራልን አሜን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!


Thursday, July 12, 2012

.......ብርሃናተ ዓለም......





ማነው በሁለት እግሩ ዓለምን የዞረ
ጽፎ ተናግሮ ዘክሮ ወንጌል የነገረ?
ይህች አለት ናት የቤቴ መሠረት
በሷ ቤቴን ሰራሁ ኮኩሐ ሐይማኖት

አባቴ ዼጥሮስ ...
እስኪንገረኝ...
የቱ ይበልጣል?
መረብ በባህሩ መወርወር
ወንጌል ለዓለሙ መናገር ?
ዓሣን ....ማደን
ሕዝብን ማዳን?
የቱ ይበልጣል አባቴ ...?
በጀልባ መዋሉ
ጌታን ማገልገሉ?

ተወው ዼጥሮስ ...
ለካ እኔ ሞኙ
ያልገባኝ ምስጢሩ
የበለጠውን በተግባር ነግረኸኝ
ዓለምን ተፍተህ ሞተህ አሳየኸኝ

ወዮ!......ወዮ!...
ወዮልሽ ሮም!
የኒሮን ዓለም
የቄሳሮች ሃገር
የግፍ ድንበር
የደም ባህር

ወዮልሽ ሮም ...
የዼጥሮስ ስቅለት ክስ ይሁንብሽ
የቅዱሱ ችንካር ምስክር ይጥራብሽ
በእጇ ያለ ወርቅ
............ሮም አልደመቀችበት

Wednesday, July 11, 2012

በዓለ ዕረፍቶሙ ለቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በታናሽ ኤስያ እየዞረ በቃሉ እያስተማረ በመልእክትም እየጻፈ ምእመናን በሃይማኖት እንዲጸኑ በመከራም እንዲታገሱ እየመከረ ካጽናናቸው በኋላ በሮሜ ለክርስቶስ መስክሮ እግዚአብሔርን የሚያመሰግንበት ዘመኑ ሲደርስ በ67 ዓ.ም ወደ ሮሜ ገብቶ ያስተምር ጀመር፡፡

ኔሮን ቄሳርም በዚያ ዘመን በክርስቲያን ላይ የሚቃጠለው የቁጣ እሳት ገና አልበረደለትም ነበርና ቅዱስ ጴጥሮስን አሲዞ አሰረው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ግን በምሴተ ሐሙስ ጌታው በተያዘ ጊዜ ስለ ደረሰበት ፈተና ጌታዉን አላውቀዉም ብሎ መካዱ ብቻ ትዝ እያለው ያዝን ነበር እንጂበመታሰሩ አላዘነም ነበር፡፡…

ኔሮን ቄሳርም ቅዱስ ጴጥሮስን አሲዞ ካሰረው በኋላ ወደ አካይያ ዘምቶ ነበርና በዘመቻው ድል አድርጎና ደስ ብሎት ወደ ሮሜ ሲመለስ አረማውያን የሆኑ መኳንንቱን ደስ ለማሰኘትና አማልክቱን ለማክበር ሲል በቅዱስ ጴጥሮስና በሌሎችም ክርስቲያኖች ሁሉ የሞት ፍርድ ፈረደባቸው፡፡ የቅዱስ ጴጥሮስም ሞት በመስቀል እንዲሆን ታዘዘ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት መፈረዱን በሰማ ጊዜ ጌታችን ወአመሰ ልሕቅ ባዕድ ያቀንተከ ሐቄከ ወይወስደከ ሀበ ኢፈቀድከ ብሎ የነገረው ቃል ትዝ አለውና አላውቀውም ብዬ መካዴን ሳያስብብኝ በዚህ ፍጹም ይቅርታ ያደርግልኛል በማለት እጅግ ደስ አለው፡፡

የሚቀልበትም ሰዓት በደረሰ ጊዜ ከግዞት ቤት አውጥተው ሲወስዱት ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ እኩል እንዳልሆን ራሴን ወደ ታች ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ ብሎ ለመነ፡፡

በሮማውያን ሥርዓት ቅጣት የተፈረደበት ወንጀለኛ የሮሜ ተወላጅ የሆነ እንደሆነ የወንጀሉ ትልቅነት እየታየ ግርፋት ወይም ሞት ይፈረድበታል እንጂ በአንድ ወንጀል ሁለት ቅጣት አይፈረድበትም፡፡
የውጭ ሀገር ወንጀለኛ እንደሆነ ግን ቅጣቱ ግርፋት እንደሆነገርፈው እስራት ይጨምሩበታል፡፡ ቅጣቱ ሞት እንደሆነ ግን አስቀድመው ገርፈው በኋላ በመስቀል ወይም በሌላ መሣርያ ይገድሉታል፡፡…

ስለዚህ ቅዱስ ጴጥሮስንም እንደ ሥርዓታቸው አስቀድመው ገርፈው በኋላ ራሱን ወደ ታች እግሩን ወደ ላይ አድርገው ሰቅለው ገደሉት፡፡ የተሰቀለውም በሐምሌ 5 /68 ዓ.ም ነው፡፡

ከሞተም በኋላ መርቄሎስ የሚባለው ደቀ መዝሙሩ ከመስቀል አውርዶ እንደ ሀገሩ ልማድ ሬሳውን በወተትና በወይን አጥቦ ሽቱ ቀብቶ በነጭ ልብስ ገንዞ ማር በተመላ ሣጥን ውስጥ አግብቶ አሁን ዛሬ ቫቲካን በሚባለው ሥፍራ ቀበረው፡፡
በረከቱና ረድኤቱ አይለየን!
+++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++
ቅዱስ ጳውሎስና ኔሮን ቄሳር በማናቸውም ነገር የማይስማሙ አጥፊና ጠፊ ነበሩ፡፡ ኔሮን ቄሳር ክፉና ዐመጸኛ ነበር፤ ቅ/ጳውሎስ ግን ደግና ፈቃደኛ ነበር፡፡ ኔሮን ቄሳር ከሐዲና ጨለማ በቃኝ የማይልንፉግ የሰይጣን ማደርያ ነበር፤ ቅ/ጳውሎስ ግን ሃይማኖታዊና ብርሃን በቃኝ የሚል ቸር የመንፈስ ቅዱስ ማደርያ ነበር፡፡

እነዚህ ሁለቱ ተጻራሪዎች በተገናኙና በተያዩ ጊዜ አንዱ የአንዱን ነገር አያስተውለውም ነበር፡፡ ስለዚህ ቅ/ጳውሎስ ወደ ፍርድ ሸንጎ ከቀረበ በኋላ ይፈታ ወይም ይቀጣ ሳይባል ወደ ግዞት ቤት መለሱት፡፡

ነገር ግን በሮሜ ከተማ ቅ/ጳውሎስ አስቀድሞ ያሳመናቸው ክርስቲያኖች እየበዙ ትምህርታቸውም እየበዛ መሔዱ በቅ/ጳውሎስ ምክንያት መሆኑን ኔሮን ቄሳር ስለተረዳው ይልቁንም ከቤተ መንግሥቱ ሹሞች ወገን ብዙ ሰዎች በክርስቶስ ስለ አሳመነበት የቤሮን ቄሳር ቁጣው ተመለሰበትና ጳውሎስን እንደገና ወደ ፍርድ ሸንጎ አቅርቡት ብሎ

FeedBurner FeedCount