Wednesday, September 9, 2015

ዘመን እና ሰው

ከዲ/ን ብርሃኑ አድማስ የፌስ ቡክ ገጽ የተወሰደ

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፥ ጳጉሜ 4 ቀን፥ 2007 ዓ.ም.)፦ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ሁለት ዓይነት ጊዜ እንዳለ ቅዱሳት መጻሕፍት ይናገራሉ፡፡ አንደኛውና ይህ ዛሬ "እንኳን ከዘመን ዘመን... " የምንባባልበትና ፍጥረትና ድርጊቱ በቅደም ተከተል የሚሰነዱበት ጊዜ ነው፡፡ ይህንን ጊዜ ከዚህ በኋላ " የፍጥረት ጊዜ" ወይም ታሪካዊ ጊዜ (Historical time) የምንለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከሥነፍጥረትም በፊት በፍጥረትም ጊዜ ከፍጥረት ማለፍም በኋላ የሚኖረውና በፈጣሪ ሕልውና የሚለካው (አስተውሉ እርሱ ራሱ ይለለካል እንጂ የፈጣሪን ድርጊት የሚለካ አይደለም) ከአሁን በኋላ "ዘላለማዊ ጊዜ " ወይም እንደኛ ሊቃውንት "ዮም " የምንለው ሌሎቹም በእንግሊዝኛ "የተቀደሰ ወይም ዘላለማዊ ጊዜ" (Sacred time) የሚሉት ጊዜ ነው፡፡ ዮም የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጓሜውም ዛሬ ማለት ነው፡፡ ይህ ሁለተኛው ጊዜ በእኛ ሊቃውንት ዘንድ "ዮም" የሚባልበት ምክንያት ከመዝሙረ ዳዊት "እግዚአብሔር ይቤለኒ ወልድየ አንተ፤ ወአነ ዮም ወለድኩከ" ፤ እግዚአብሔር አንተ ልጄ ነህ፤ እኔ ዛሬ ወለድሁህ (መዝ 2፤7)የሚለውን ጥቅስ መነሻ አድርገው ትርጓሜውን ሲያብራሩ እግዚአብሔር ስለ ራሱ የገለጸው የጊዜ መጠሪያ ዮም ወይም ዛሬ መሆኑን ስለሚያመሰጥሩ ነው፡፡ ይህም ማለት በእግዚአብሔር ዘንድ ትናንት እና ነገ፤ አምናና ከርሞ፤ ጥንትና መጪው ጊዜ ወይም ከዚህ ዘመን በኋላ የሚባል ነገር የለም ማለት ነው፡፡ ለእርሱ ሁሉም "ዛሬ" ነው፤ ምክንያቱም እርሱ በፍጥረት ጊዜ ሊለካና ሊታወቅ የሚችል አይደለምና፡፡ ስለዚህም ነው ስለ እግዚአብሔር ሲሆን "ዮም" ወይም ምዕራባውያን እንደሚሉት ልዩ፤ ቅዱስ ጊዜ (sacred time) የሚለውን ለመጠቀም የምንገደደው፡፡ ከላይ በተገለጸው ጥቅስ ላይ ‹‹እኔ ዛሬ ወለድሁህ›› የሚለው የሚገልጸውም የወልድን ሁለቱንም ልደታት ነው፡፡ በእኛ ሊቃውንት ዘንድ ይህ ኃይለ ቃል ሲብራራ ሁለቱም ጊዜዎች አብረው የሚነሡትም ለዚህ ነው፡፡ የጌታችንን ሁለት ልደታት የመጀመሪያው ‹‹ ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት›› ሁለተኛውን ደግሞ ‹‹ድኅረ ዓለም ከእመቤታችን ያለ አባት›› ሲሉ ይገልጹታል፡፡ ይህ አገላለጽ ሙሉ በሙሉ በፍጥረት ጊዜ ማለትም እኛ ድርጊቶችን በምንለካበትና እግዚአብሔር ሥነ ፍጥረትን ሲፈጥር በፈጠረው ጊዜ ከላይ እንዳልነው በታሪክ መለኪያው ጊዜ (Historical time) የተገለጸ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፤ ›› / ዕብ 1 ፤ 1-2/ እያለ የሚናገረው በዚሁ ጊዜ ስሌት ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ በፍጥረት ጊዜ ሲለካ የእግዚአብሔር ወልድ ቀዳማዊ ልደት ‹‹ቅድመ ዓለም›› ወይም ከዓለም መፈጠር በፊት ከሚለው ውጭ መግለጫ የለውም፡፡ ምክንያቱም ከዚያ በፊት ያለውን የሚለካ የፍጥረት ጊዜ ( Historical time ) የለምና፡፡ ከዚሁ ጋር አብረውም ልክ የእርሱን ቀዳማዊ ልደት በፈጣሪ ቅዱስ ጊዜ እንደገለጹት ሁለተኛውን ልደቱን ማለትም ከእመቤታችን በታወቀ ጊዜ የተወለደውንም በእኛ አቆጣጠር የሚገልጹትን ያህል በእግዚአብሔር ቅዱስ ጊዜ ‹‹ዮም›› ዛሬ ብለው ከታሪካዊው ወይም ከታሪክ መነገሪያው ፍጥረታዊ ጊዜ አውጥተው ይነግሩናል፡፡ ምክንያቱም በእግዚአብሔር ዘንድ ሁሉም ዛሬ ነውና፡፡ ‹‹ዛሬ ወለድኩህ›› ማለትም ቀዳማዊ ልደቱም ደኃራዊ ልደቱም በእርሱ ዘንድ ዛሬ ስለሆነ ነው፡፡ ለሊቃውንቶቻችን ምስጋና ይድረሳቸውና ‹‹ ዘመን የማይቆጠርለት ዘመን ተቆጠረለት›› የሚለው ግሩም አገላለጻቸውም በዘላለማዊ ጊዜ ያለው በፍጥረታዊው ወይም በታሪክ መሰነጃው ጊዜና ዓለም ውስጥ መገለጹን የሚያስረዱበት እጅግ ድነቅ አገላለጽ ነው፡፡

Tuesday, September 8, 2015

Wednesday, August 26, 2015

ትምህርተ ሃይማኖት - ክፍለ ዐሥራ አራት



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ 21 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የሰኞ (ሠኞ) ፍጥረት
ሰኞ የሚለው ቃል “ሰነየ - ሰኑይ” ከሚል የግእዝ ቃል የተገኘ ሲኾን፥ ትርጓሜውም መሰነይ፣ ኹለት ማድረግ፣ ኹለተኛ ዕለት ማለት ነው፤ ሥነ ፍጥረትን ለመፍጠር ኹለተኛ ቀን ነውና፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ፥ ሠኑይ ማለት ሠነየ፣ ሠናይ፣ አማረ፣ ተዋበ፣ በጌጥ በመልክ ደስ አሰኘ ማለት ነው፤ ይኸውም በዚህ ዕለት ብርሃን ስለ ተፈጠረ ነው፡፡
      ለሰኞ አጥቢያ በጊዜ ሠርክ (የመጀመሪያው ሰዓተ ሌሊት) እግዚአብሔር በዕለተ እሑድ “ብዢ ተባዢ፤ ስፊ ተስፋፊ” ብሏት የነበረችው ውኃ ከምድር ጀምራ እስከ ኤረር ድረስ መልታ ነበር፡፡ በዚሁ ዕለት ማለትም በዕለተ ሰኑይም፥ ጠፈርን ፈጠረ /ዘፍ.1፡6-9/፡፡ እግዚአብሔር ጠፈርን በፈጠረ ጊዜም በዓለም መልቶ የነበረው ውኃ በአራት ተከፍሏል፡-
ü  የምናየው ሰማይ (ጠፈር) (ሥዕለ ማይ)፣
ü  ከጠፈር በላይ የተሰቀለው ሐኖስ፣
ü  ለምድር ምንጣፍ የኾነ ውኃና፣
ü  በምድር ዙርያ እንደ መቀነት የተጠመጠመው ውኃ (ውቅያኖስ) ተብሎ፡፡ በምድር ላይ የምናያቸው ውኆች በምድር ዙርያ ከተጠመጠመው ከዚህ ውቅያኖስ የቀሩ እንጥፍጣፊ ናቸው፡፡

Tuesday, August 18, 2015

መንፈሳዊ አገልግሎት



በዲ/ን ሕሊና በለጠ ዘኆኅተብርሃን
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ 12 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
አገልግሎት የሚለው ቃል ገልገለ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ እንደሆነ ይጠቁማል፡፡ ገልገለ (አገለገለ) ማለት ተገዛ፣ ታዘዘ፣ ዐገዘ፣ ረዳ፣ ጠቀመ፣ ማንኛውንም ሥራ ሠርቶ ጌታውን  ደስ አሰኘ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ አገልግሎት ማለት መታዘዝ፣ መገዛት፣ መርዳት፣ መጥቀም…ማለት ይሆናል፡፡  ማንኛውም ሥጋዊና መንፈሳዊ ሥራ አገልግሎት ነው፡፡ ለመንግሥት የሚሠራ የመንግሥት አገልጋይ፣ ለግለሰብ የሚሠራ የግለሰብ አገልጋይ፣ ለእግዚአብሔርም የሚሠራ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ አገልጋዮችን በተለያየ ስያሜ ጠርቷል፡፡ ምንም አይነት መብት በራሱ ላይ የሌለውንና በጌታው ሐሳብ ፍፁም አዳሪ የሆነውን ተገዢ ባሪያ በማለት ገልፆታል፡፡ ንዋይ ኅሩይ ቅዱስ ጳውሎስ ‘ከሰው ሁሉ አርነት የወጣሁ ስሆን የሚበልጡትን እንድጠቅም እንደባሪያ ራሴን ለሁሉ አስገዛለሁ’ በማለት የተናረው ይህን ያጠናክራል፡፡ (1ቆሮ. 9÷19) አብሮት የሚያገለግለውን ቲኪቆስንም  ‘በጌታም አብሮኝ ባሪያ የሆነ’ በማለት ጠርቶታል፡፡ (ቁላ 4፡7) ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም አርነት ወጥታችሁ እንደ እግዚአብሔር ቅዱሳን ባሪያዎች ሁኑ በማለት አገልግሎታችን በፍፁም መገዛት እንዲሆን ይመክረናል፡፡ (1ጴጥ. 2‘፡16) በራሱ ላይ ሙሉ ነፃነት ያለውን አገልጋይ መጽሐፍ ቅዱስ ሠራተኛ ይለዋል፡፡ (ሉቃ 10፡2፣ ቁላ 4፡11፣ 2ጴጥ 1፡8) ይህ ከባሪያ ይልቅ በራሱ ላይ የመወሰን ሥልጣን ያለው ነው፡፡ ከፈለገ አለማገልገል ይችላል፡፡ በባሪያና በሠራተኛ መካከል ነፃነቱ መካከለኛ የሆነው ደግሞ ብላቴና፣ ሎሌ ተብሎ የተጠራው ነው፡፡

FeedBurner FeedCount