Saturday, June 9, 2012

.........ታጠቅ...!...


                            በልዑል ገ/እግዚአብሔር!

'ድው...ድው...ድው...'
ነጋሪት ተጎስሟል
መለከት ተነፍቷል

ጠላት ሸምቆ
ትጥቁን ታጥቆ
በጦር አውድማ ሊወጋህ
ለስቃይ ሊጥልህ ሊያደማህ
ወግቶ አድምቶ ሊገልህ
ከምድረ ገጽ ሊያጠፋህ

እሳት ለብሶ
እሳት ጎርሶ
በሜዳ ላይ ቆሟል
ሊበላህ ጎምዥቷል

'
ድው...ድው...ድው...'
ነጋሪት ተጎስሟል
መለከት ተነፍቷል

ታጠቅ:-
ጦር ምዝራቅህን ሰብቅ
ጠመንጃ ነፍጥህን ታጠቅ
ሰይፍ ሜሎስህን መርቅ

ትጥቅህ ኃይለኛው
የአንበሳ ክንድ ነው
ያደቃል ያበራያል
ያጠፋል ያወድማል

አይዞህ:-
አትፍራው በለው
ወደ ኃላ አባረው
ሲፎክር ሲሸልል

ሲባርቅ አለሁ ሲል
ጠላትህ ሲያገሳ
'
ማይገል አንበሳ
ሽለላ ብቻ አቅም የለው
የቀድሞ ጦር ኃይል ነሳው

በል:-
ሜዳው እዛው
ፈረሱም ያው
አንተ ታጥቀህ እሱም ታጥቖል
ጦር ስትሸምቅ ተሸማምቖል

በጦር አውድማ በደም ቦታ
ኃይል የያዘ ብርቱው ይርታ
አይዞህ:-
ወደ ፊትህ ገስግስ
ወደ ኃላ አትመለስ

ጦርህን ወርውረው
መሀል ልቡን ውጋው
ነፍጥህን ተኩሰው
ደረቱን ክፈለው
ሰይፍህን መትረው
አንገቱን ቀንጥሰው

እሱ:-
ያስታጠቀህ ያውቅበታል
ማሸነፉን ተክኖታል

ግና:-
በቁም ብትነፍዝ
ትጥቅ ባትይዝ
ተዘናግተህ ተሞኝተህ
ትጥቁን ጥለህ
ጦር ነፍጥህን
አሽቀንጥረህ ሰይፍህን

በጦር አውድማ
በደም ከተማ:-

እጅህን ወደ ላይ
ጉልበትህን ለድንጋይ
በቀላሉ ተማርከሀል
በማረከህ ተይዘሀል
በያዘህ እጅ ተገለሀል::
'ድው...ድው...ድው...'
ነጋሪት ተጎስሟል
መለከት ተነፍቷል
.........
ታጠቅ!.......

/
ጾም..ጸሎት..ስግደት../
(
ሰኔ01/2004..)

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount