Wednesday, June 6, 2012

የወልድ ፍቅር!!


 
ባሕርይውን ዝቅ ብሎ የታየው ከሁላችንም በላይ ከዘመናት ሁሉ አስቀድሞ የነበረው ነው፤ ይህ ሰው የሆነው ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ውስጥ የሚኖረው ነው፡፡ የሆነው ሁሉ በእርሱ የተደረገ ነበር፤ የሆነው ሁሉ የተደረገው በምክንያት ነበር፡፡ ያለ ምክንያት የተደረገ አንዳችም ነገር የለም፡፡ እርሱም ለሰው ልጆች ዘላለማዊ ዋስትና ሲባል የተደረገ ነው፡፡ እርሱ ከመጀመርያው ያለ ምክንያት ነበር፡፡ ለእግዚአብሔር ሀልዎትስ ምን ምክንያት ይኖረዋል! ነገር ግን በምክንያት እርሱም የሰው ልጅን ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ሥጋ ለብሶ ሰው ሆነ፤ የተፈጸመውም የእኛ ድኅነት ነው፡፡ያዋረድነውን እግዚአብሔርነቱን፣ የናቅነውን መንግሥቱን፣ ያቃለልነውን ወገኖቹ ሊያደርገን ስለዚህ የእኛ ባሕርይን ነሣ፡፡ ሥጋ ዝቅ ያለ ሲሆን እግዚአብሔርን ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም የሰው ልጅ ሆነ፡፡በሥጋ ከድንግል ተወለደ፡፡ አስቀድሞ ግን ከባሕርይ አባቱ ከዘላለም የተወለደ የእግዚአብሔር ልጅ ነበረ፡፡ ከሴት ተወለደ፤ ነገር ግን ድንግል ነበረች፡፡ የመጀመርያው ሰው ሁለተኛው መለኰት ነው፤ ሁለት ባሕርያት ያሉት አይደለም፡፡ በፍጹም ተዋሕዶ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ የሆነ እንጂ፡፡ ሰው እንደ መሆኑ አባት የለውም፤ አምላክ እንደ መሆኑ እናት የለውም፡፡ በማሕጸነ ድንግል ተወሰነ፤ በነብያቱ አፍ አምላክነቱ ተመሰከረለት፡፡ ነቢያቱ ብቻ የመሰከሩ አይደለም፤ አብም የምወደው ልጄ ነው አለ፤ እርሱም አባቴ ነው አለ እንጂ፡፡ ሰው እንደ መሆኑ በጨርቅ ተጠቀለለ፤ አምላክ እንደ መሆኑ የተገነዘበትን ጨርቅ ጥሎት ተነሣ፡፡ በበረት

Tuesday, June 5, 2012

ጾም!!


ጾም መድኃኒት ናት፡፡ አወሳሰድዋን በትክክል ላላወቁ ግን ጥቅም የላትም፡፡ ይህችን መድኃኒት የሚወስድ ሰው በየስንት ሰዓቱ እንደምትወሰድ፣ በምን ያህል መጠን (Dosage) እንደምትዋጥ፣ ለምን ዓይነት በሽታ እንደምትጠቅም፣ በየትኛው ወራትና በየትኛው የአየር ሁናቴ እንደምትወሰድ፣ ከእርሷ ጋር የሚሄዱና የማይሄዱ ምግቦችን እንዲሁም ሌሎች ከእርሷ ጋር የማይስማሙ ነገሮችን ለይቶ ማወቅ አለበት፡፡ እነዚህን ግምት ውስጥ አስገብተን የማንወስዳት ከሆነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡ አንድ በሐኪም የታዘዘልንን የደዌ ሥጋ መድኃኒት በትክክል ከወሰድነው ከሕመማችን እንፈወሳለን፤ የነፍሳችንን ደዌ ለመፈወስ ብለን በምንወስደው መድኃኒት ደግሞ ከዚህ የበለጠ መጠንቀቅ አለብን፡፡

ጾም ሁለመናችንን የምንለውጥበት መሣርያ ነው፡፡ ምክንያቱም የጾም መሥዋዕት ማለት ከምግብ ብቻ መከልከል ሳይሆን ከኃጢአት ሁሉ መከልከል ነውና፡፡ ስለዚህ እየጾምኩ ነው እያለ ራሱን ከምግብ ብቻ የሚከለክል ሰው ካለ እርሱ ጾምን እያቃለለና እያጥላላ ነው ማለት ነው፡፡ እየጾማችሁ ነው? እንግዲያስ መጾማችሁን በተግባር አሳዩኝ፡፡ “እንዴት አድርገን እናሳይህ?” ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም እንዲህ ብዬ እመልስላችኋለሁ፡- ደሀው እርዳታችሁን ፈልጎ እንደሆነ ቸርነትን አድርጉለት፤ የጠላችሁት ሰው ካለ ፈጥናችሁ ታረቁ፤ ባልጀራችሁ ተሳክቶለት ስታዩት በእርሱ ላይ ቅናት አትያዙ፤ ቆነጃጅትን በመንገድ ሲያልፉ ስታዩ በዝሙት ዓይን አትመኙ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያደረጋችሁ በትክክል መጾማችሁን አሳዩኝ፡፡

 በሌላ አገላለጽ አፋችሁ ብቻ ሳይሆን ዐይኖቻችሁ፣ እግሮቻችሁ፣ እጆቻችሁና የሰውነታችሁ ሕዋሳቶች በሙሉ መጾም አለባቸው፡፡ እጆቻችሁ ከመስረቅና የእናንተ ያልሆነውን ከመውሰድ ይጹሙ፤ እግሮቻችሁ የኃጢአት ሥራን ለመፈፀም ከመፋጠን ይጹሙ፤ ዐይኖቻችሁ ውጫዊ በሆነ ውበት ምክንያት ከመቅበዝበዝ ይጹሙ፡፡ ጥሉላትን (የፍስክ ምግብ) እየበላችሁ አይደለም አይደል? እንግዲያስ በዐይኖቻችሁም ክፉ ነገርን አትብሉ፡፡ የሚታዩ ነገሮች ለዐይን ምግቦች ናቸውና፡፡ ጀሮዎቻችሁም ይጹሙ፡፡ የጀሮ ጾም ሐሰተኛ ወሬንና ሐሜትን አለመስማት የመሳሰለ ነው፡፡

 አንደበታችሁም ከከንቱ ንግግር ይጹም፡፡ ዓሣንና ሌሎች ጥሉላትን ከመብላት ተከልክለን ሳለ ነገር ግን ወንድሞቻችንን በሐሜት የምናኝካቸውና የምንበላቸው ከሆነ ምን ጥቅም አለው? ወንድሙን የሚያማና የሚነቅፍ ሰው እርሱ የወንድሙን አካል ያቆስላል ሥጋውንም ይበላል፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ይህን አስመልክቶ  እጅግ የሚያስደነግጥ ንግግርን እንዲህ ሲል የተናገረው፡- “እርስ በእርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በእርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ” /ገላ.5፡15/፡፡ ስታሙ በጥርሳችሁ የወንድማችሁን ሥጋ አትነክሱም፡፡ በክፉ ንግግራችሁ ግን የወንድማችሁን ነፍስ ትነክሳላችሁ፤ ታቆስሉትማላችሁ፡፡ እንዲህ በማድረጋችሁ ራሳችሁን፣ ወንድማችሁንና ሌሎች ብዙ ሰዎችን ትጎዳላችሁ፡፡” 

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ!

Saturday, June 2, 2012

ርደተ መንፈስ ቅዱስ - በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ!!


  መንፈሳዊ ጸጋቹ በዛሬው ዕለት በእኛ ላይ በምላት ወርዷልና መንፈስ ቅዱስን በመንፈሳዊ ጣዕመ ዝማሬ ከፍ ከፍ እናድርገው፡፡ ምንም እንኳን ያገኘነውን የጸጋ ታላቅነት ለመግለጽ የእኛ ቃላት በጣም ደካሞች ቢሆኑም እንደ አቅማችን ኃይሉንና ሥራውን ከማመስገን አንከልከል፡፡
  
 እያከበርን ያለነው የጴንጤ ቆስጤ በዐል ነው፤ የርደተ መንፈስ ቅዱስ ቀን፣ ተስፋ ፍጻሜ ያገኘበት ቀን፣ መጠበቅንና የመዳንን ናፍቆት ያበቃበት ቀን፣ ጸሎተ ሐዋርያት መልስ ያገኘበት ቀን፣ ዐስበ ትዕግሥትን ያየንበት ቀን፡፡ የዛሬው ዕለት በዔቦር ዘመን ቋንቋን የደበላለቀ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ የእሳት ላንቃዎችን ሲያሳይ የተመለከትንበት ነው /ዘፍ.10፡25/፡፡ በዔቦር ዘመን አስወቃሹንና አሳፋሪውን የሰው ልጅ ፈቃድ ለመግታት ቋንቋቸውን የደበላለቀ መንፈስ ቅዱስ ዛሬ ግን ደቀመዛሙርቱ ሁሉም በአንድ ቤት ሳሉ ድንገት እንደሚነጥቅ አውሎ ንፋስ መጥቶ ቤቱን ሲሞላው፤ እንደ እሳት የተከፋፈሉ ልሳኖችም ሲያሳያቸው፤ በፈቃዱም የሰባኪነትን ልሳን ሲሰጣቸው አየን፡፡
  
 ይህ ቅዱስ መንፈስ በሥነ ፍጥረት መጀመርያ በውኃ ላይ ሲሰፍ አየነው፤ በኋላ በዘመነ ሐዲስም በጌታችን ራስ ላይ ሲያርፍ አየነው፡፡
  
 ይህ በርግብ አምሳል በጥፋት ውኃ ላይ በርሮ የንፍር ውኃ መጉደሉን ለኖኅ ያበሰረ መንፈስ ቅዱስ በኋላም በርግብ አምሳል በዮርዳኖስ ውኆች ላይ በመታየት ሲጠመቅ የነበረውን በግ ለዓለም ሁሉ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ መሆኑን ሲገልጥ ሲመሰክር አየነው፡፡
   

Friday, June 1, 2012

ጾመ ሐዋርያት- በዲያቆን ኅብረት የሺጥላ


በየአመቱ በዕለተ ሰኑይ ብቻ (ሰኞ ቀን ብቻ) የሚጀምሩ ሦስት አጽዋማት አሉ፡፡ እነርሱም ዓቢይ ጾም፣ ጾመ ነነዌ እና ጾመ ሐዋርያት ናቸው፡፡ እነዚህ አጽዋማት ምን ጊዜም ቅበላቸው እሁድ ሲሆን የሚገቡት ደግሞ ሰኞ ቀን ነው፡፡ በየትኛውም አመት ይህን ዕለት አይለቁም፡፡

ስለዚህ 2004 ጾም ሐዋርያት ግንቦት 27 የፊታችን ሰኞ ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ በየግላችንም ያጋጠሙንን መንፈሳዊና ሥጋዊ ውጊያዎች በማሰብ ድል የምናደርግበትን ኃይል ፈጣሪያችን ይሰጠን ጾሙን ከወትሮው በበለጠ ጥንቃቄ ልንጾመው ይገባናል፡፡

የጾሙን ታላቅነት ተረድተን እንድንጾመው የትመጣውን፣ ትንቢቱን፣ ምሳሌውንና ምሥጢሩን መረዳት አጋዥ ስለሚሆነን አስቀድመን ስለጾሙ እንማር ዘንድ በአጭሩ አቅርቤዋለሁ! የምችለውን ያህል እጽፍ ዘንድ ብርታቱንና ጥበቡን የሰጠኝ አምላከ ቅዱሳን ሐዋርያት ክብር ምስጋና ይድረሰው! አሜን!

ጾመ ሐዋርያት በራሳቸው በሐዋርያት የተጀመረ ጾም እንደመሆኑ መጠን በአንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን ማለትም ከዛሬ አንድ ሺህ ዘጠኝ መቶ ዓመታት በፊት ጀምሮ ሲጾም የኖረ ጾም ነው፡፡ ለዚህም የመጽሐፍ ቅዱስ፣ የአዋልድ መጻሕፍትና የታሪክ በርካታ ምስክሮች አሉ፡፡ ስለዚህ ጾሙን እንደ እንግዳ ነገር መቁጠርና ዘመን አመጣሽ አድርጎ ማየት የራስን አላዋቂነት ያሳያል፡፡ ይህን ማለት ያስፈለገው ጥቂቶች ጾሙን ድሮ ያልነበረና ዘመን አመጣሽ አድርገው ስለሚናገሩ ነው፡፡

      ጾመ ሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ዕድሜያቸው ለጾም የደረሱ ምእመናን በሙሉ እንዲጾሙአቸው ካወጀቻቸው ሰባት የአዋጅ አጽዋማት መካከል አንዱ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በጌታችንና በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አንደበት ቀን የተቀጠረለት፣ ትንቢት የተነገረለትና ምሳሌ የተመሰለለት ጾም መሆኑ ከአጽዋማት ሁሉ ለየት ያደርገዋል፡፡

  ጌታችን ስለዚህ ጾም ትንቢተ በመናገር፣ ምሳሌ በመመሰል ሰፊ ትምህርት የሰጠው ፈሪሳውያን ወደ እርሱ ቀርበው ‹‹ደቀ መዛሙርትህ የማይጦሙት ስለ ምንድር ነው?›› ብለው በጠየቁት ጊዜ ነው፡፡ እርሱም ሲመልስ እንዲህ አላቸው፡- ‹‹ሚዜዎች ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሊያዝኑ ይችላሉን? ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወሰድበት ወራት ይመጣል በዚያ ጊዜም ይጦማሉ፡፡ በአረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚያኖር የለም፤ መጣፊያው ልብሱን ይቦጭቀዋልና መቀደዱም የባሰ ይሆናል፡፡ በአረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን አቁማዳው ይፈነዳል የወይን ጠጁም ይፈሳል፡፡ አቁማዳውም ይጠፋል፡፡ ነገር ግን አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ያኖረዋል ሁለቱም ይጠባበቃሉ፡፡›› (ማቴ9.14-17)

በመቀጠል እስከ መጨረሻ የምንመለከተው ከላይ የሰፈረውን የማቴዎስ ወንጌል አጭር ገጸ ንባብ ሐሳብ በመሆኑ መለስ እያሉ ታሪኩን ማንበብ ወይም በልብ ከመዘገቡ በኋላ ቀጣዩን ክፍል ማንበብ ምሥጢሩን ለመረዳት ያግዛል፡፡

FeedBurner FeedCount