Friday, June 8, 2012

ከዮሐንስ ምስክር የሚበልጥ ምስክር አለኝ- የዮሐንስ ወንጌል የ26ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.5፡30-ፍጻሜ)!


     በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

 አንድ ምንም እውቀቱና ልምዱ የሌለው ሰው ዝም ብሎ መሬት ስለ ቆፈረ ብቻ ወርቅ አያገኝም፡፡ ከዚያ ይልቅ ምንም ረብሕና ጥቅም የሌለውን ድካም ያተርፋል እንጂ፡፡ ባስ ካለም የቆፈረው ጉድጓድ ተደርምሶበት ሕይወቱን ሊያጣ ይችላል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንዴት እንደሚነበብና እንዴት መረዳት እንዳለበት ያለወቀ ሰውም ይህን ሰው ይመስላል፡፡ ይህንን የምንለው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ይልቁንም ቀጥለን የምንመለከተው ቃል በቀላሉ ሊረዱት የማይችሉና ሰም ለበስ ወርቅ ስለሆነ እንጂ፡፡ ጌታችን “እኔ ከራሴ አንዳች ላደርግ አይቻለኝም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ ፍርዴም ቅን ነው፥ የላከኝን ፈቃድ እንጂ ፈቃዴን አልሻምና።  እኔ ስለ እኔ ስለ ራሴ ብመሰክር ምስክሬ እውነት አይደለም” ስላለ ብቻ እንዲሁ ጥሬ ንባቡን በመያዝ ብዙ ሰዎች ይደናበራሉ /ቁ.30-31/፤ እውነት የሆነው “ክርስቶስ ስለ ራሱ የመሰከረው ምስክርነት እውነት አይደለም” ለማለት ይደፍራሉ፡፡ ሆኖም ግን ጌታችን ይህንን ሲል እነርሱ እንደሚሉት ማለቱ አልነበረም፡፡ አይሁድ “እግዚአብሔር አባቴ ነው፤ ከአባቴ ጋር የተስተካከልኩ ነኝ፤ አባቴ እስከ ዛሬ እንደሚሠራ እኔም በአንድ ፈቃዲት በአንዲት ሥልጣን እንዲህ አደርጋለሁ” ቢላቸው “አንተ ስለ ራስህ ትመሰክራለህ፤ ምስክርነትህ እውነት አይደለም፡፡ ስለዚህም አናምንህም” /ዮሐ.8፡13/ ስለሚሉትና ሊገድሉት ስለሚፈልጉ፡- “እኔ ምንም ምን ከራሴ ብቻ አንቅቼ አላስተምርም፤ በህልውና እንደሰማሁ የሰማሁትን አስተምራለሁ እንጂ፡፡ ትምህርቴም እውነት ነው፤ የእኔ ፈቃድ ከአባቴ ፈቃድ ልዩ ሆኖ የእኔ ፈቃድ ብቻ ሊደረግ አልወድም፤ ወልድ ያልወደደው አብም አይወደውም” ነው የሚላቸው /ወንጌል ቅዱስ አንድምታ ገጽ 481/፡፡

   ሰው ወዳጁ ጌታ ንግግሩን በዚህ አያቆምም፤ ይልቁንም እንዲህ ብሎ ይቀጥላል እንጂ፡- “የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ስላልሁ፣ አብ ልኮ ያዋሐደኝ አምላክ ነኝ ብላችሁ እናንተ ግን ትሳደባለህ ትሉኛላችሁ፡፡ ሆኖም እኔ የአባቴን ሥራ ባላደርግ፣ የአምላክነትን ሥራ ባላደርግ አትመኑኝ፤ ምስክርነቴንም አትቀበሉ፤ ባደርገው ግን እኔን እንኳ ባታምኑ አብ በእኔ ህልው እንደሆነ እኔም በአብ ህልው እንደሆንሁ ታውቁና ታስተውሉ ዘንድ ሥራውን እመኑ”/ዮሐ.10፡36/፤ አብ ሙታንን እንደሚያነሣ ሕይወትም እንደሚሰጣቸው እኔም ለምወዳቸው ለሚያምኑብኝ ሕይወትን የመስጠት ኃይልና ሥልጣን እንዳለኝ እመኑ፡፡ አንተ ስለራስህ የምትመሰክረው ምስክርነት አንቀበልም ብትሉ እንኳን አብ ስለ እኔ የሚመሰክረውን ለመቀበል አትቸገሩ፤ የማደርገውን ሥራ አይታችሁ እመኑ፡፡ እናንተ ወደ ዮሐንስ ልካችሁ አልነበረምን? እርሱስ፡-እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔረ በግ ብሎ እውነት ነግሯችሁ አልነበረምን? /ዮሐ.1፡29/:: እንግዲያውስ ዮሐንስ የመሰከረላችሁ ምስክርነት እመኑ፡፡ ስለ ራስህ ምን ትላለህ? ሳይሆን ስለ ክርስቶስ ምን ትላለህ? ብላችሁ ጠይቁትና እመኑ፡፡ እናንተ እንድትድኑ ይህን እላለሁ እንጂ እኔስ  ከሰው ምስክር አልቀበልም፡፡ እናንተ ትወዱት ስለ ነበረ እንደ ነብይም ታዩት ስለ ነበረ የእርሱን ትምህርት አድምጣችሁ በእኔ ታምኑ ዘንድ ትምህርቱን አስታወስኳችሁ እንጂ አምላክነቴን ለማረጋገጥስ የማደርገው ተአምራት ራሱ በቂ ነው /ቁ.34፣ Saint John Chrysostom  Homilies on ST. John, 41/፡፡

Wednesday, June 6, 2012

የወልድ ፍቅር!!


 
ባሕርይውን ዝቅ ብሎ የታየው ከሁላችንም በላይ ከዘመናት ሁሉ አስቀድሞ የነበረው ነው፤ ይህ ሰው የሆነው ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ውስጥ የሚኖረው ነው፡፡ የሆነው ሁሉ በእርሱ የተደረገ ነበር፤ የሆነው ሁሉ የተደረገው በምክንያት ነበር፡፡ ያለ ምክንያት የተደረገ አንዳችም ነገር የለም፡፡ እርሱም ለሰው ልጆች ዘላለማዊ ዋስትና ሲባል የተደረገ ነው፡፡ እርሱ ከመጀመርያው ያለ ምክንያት ነበር፡፡ ለእግዚአብሔር ሀልዎትስ ምን ምክንያት ይኖረዋል! ነገር ግን በምክንያት እርሱም የሰው ልጅን ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ሥጋ ለብሶ ሰው ሆነ፤ የተፈጸመውም የእኛ ድኅነት ነው፡፡ያዋረድነውን እግዚአብሔርነቱን፣ የናቅነውን መንግሥቱን፣ ያቃለልነውን ወገኖቹ ሊያደርገን ስለዚህ የእኛ ባሕርይን ነሣ፡፡ ሥጋ ዝቅ ያለ ሲሆን እግዚአብሔርን ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም የሰው ልጅ ሆነ፡፡በሥጋ ከድንግል ተወለደ፡፡ አስቀድሞ ግን ከባሕርይ አባቱ ከዘላለም የተወለደ የእግዚአብሔር ልጅ ነበረ፡፡ ከሴት ተወለደ፤ ነገር ግን ድንግል ነበረች፡፡ የመጀመርያው ሰው ሁለተኛው መለኰት ነው፤ ሁለት ባሕርያት ያሉት አይደለም፡፡ በፍጹም ተዋሕዶ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ የሆነ እንጂ፡፡ ሰው እንደ መሆኑ አባት የለውም፤ አምላክ እንደ መሆኑ እናት የለውም፡፡ በማሕጸነ ድንግል ተወሰነ፤ በነብያቱ አፍ አምላክነቱ ተመሰከረለት፡፡ ነቢያቱ ብቻ የመሰከሩ አይደለም፤ አብም የምወደው ልጄ ነው አለ፤ እርሱም አባቴ ነው አለ እንጂ፡፡ ሰው እንደ መሆኑ በጨርቅ ተጠቀለለ፤ አምላክ እንደ መሆኑ የተገነዘበትን ጨርቅ ጥሎት ተነሣ፡፡ በበረት

Tuesday, June 5, 2012

ጾም!!


ጾም መድኃኒት ናት፡፡ አወሳሰድዋን በትክክል ላላወቁ ግን ጥቅም የላትም፡፡ ይህችን መድኃኒት የሚወስድ ሰው በየስንት ሰዓቱ እንደምትወሰድ፣ በምን ያህል መጠን (Dosage) እንደምትዋጥ፣ ለምን ዓይነት በሽታ እንደምትጠቅም፣ በየትኛው ወራትና በየትኛው የአየር ሁናቴ እንደምትወሰድ፣ ከእርሷ ጋር የሚሄዱና የማይሄዱ ምግቦችን እንዲሁም ሌሎች ከእርሷ ጋር የማይስማሙ ነገሮችን ለይቶ ማወቅ አለበት፡፡ እነዚህን ግምት ውስጥ አስገብተን የማንወስዳት ከሆነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡ አንድ በሐኪም የታዘዘልንን የደዌ ሥጋ መድኃኒት በትክክል ከወሰድነው ከሕመማችን እንፈወሳለን፤ የነፍሳችንን ደዌ ለመፈወስ ብለን በምንወስደው መድኃኒት ደግሞ ከዚህ የበለጠ መጠንቀቅ አለብን፡፡

ጾም ሁለመናችንን የምንለውጥበት መሣርያ ነው፡፡ ምክንያቱም የጾም መሥዋዕት ማለት ከምግብ ብቻ መከልከል ሳይሆን ከኃጢአት ሁሉ መከልከል ነውና፡፡ ስለዚህ እየጾምኩ ነው እያለ ራሱን ከምግብ ብቻ የሚከለክል ሰው ካለ እርሱ ጾምን እያቃለለና እያጥላላ ነው ማለት ነው፡፡ እየጾማችሁ ነው? እንግዲያስ መጾማችሁን በተግባር አሳዩኝ፡፡ “እንዴት አድርገን እናሳይህ?” ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም እንዲህ ብዬ እመልስላችኋለሁ፡- ደሀው እርዳታችሁን ፈልጎ እንደሆነ ቸርነትን አድርጉለት፤ የጠላችሁት ሰው ካለ ፈጥናችሁ ታረቁ፤ ባልጀራችሁ ተሳክቶለት ስታዩት በእርሱ ላይ ቅናት አትያዙ፤ ቆነጃጅትን በመንገድ ሲያልፉ ስታዩ በዝሙት ዓይን አትመኙ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያደረጋችሁ በትክክል መጾማችሁን አሳዩኝ፡፡

 በሌላ አገላለጽ አፋችሁ ብቻ ሳይሆን ዐይኖቻችሁ፣ እግሮቻችሁ፣ እጆቻችሁና የሰውነታችሁ ሕዋሳቶች በሙሉ መጾም አለባቸው፡፡ እጆቻችሁ ከመስረቅና የእናንተ ያልሆነውን ከመውሰድ ይጹሙ፤ እግሮቻችሁ የኃጢአት ሥራን ለመፈፀም ከመፋጠን ይጹሙ፤ ዐይኖቻችሁ ውጫዊ በሆነ ውበት ምክንያት ከመቅበዝበዝ ይጹሙ፡፡ ጥሉላትን (የፍስክ ምግብ) እየበላችሁ አይደለም አይደል? እንግዲያስ በዐይኖቻችሁም ክፉ ነገርን አትብሉ፡፡ የሚታዩ ነገሮች ለዐይን ምግቦች ናቸውና፡፡ ጀሮዎቻችሁም ይጹሙ፡፡ የጀሮ ጾም ሐሰተኛ ወሬንና ሐሜትን አለመስማት የመሳሰለ ነው፡፡

 አንደበታችሁም ከከንቱ ንግግር ይጹም፡፡ ዓሣንና ሌሎች ጥሉላትን ከመብላት ተከልክለን ሳለ ነገር ግን ወንድሞቻችንን በሐሜት የምናኝካቸውና የምንበላቸው ከሆነ ምን ጥቅም አለው? ወንድሙን የሚያማና የሚነቅፍ ሰው እርሱ የወንድሙን አካል ያቆስላል ሥጋውንም ይበላል፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ይህን አስመልክቶ  እጅግ የሚያስደነግጥ ንግግርን እንዲህ ሲል የተናገረው፡- “እርስ በእርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በእርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ” /ገላ.5፡15/፡፡ ስታሙ በጥርሳችሁ የወንድማችሁን ሥጋ አትነክሱም፡፡ በክፉ ንግግራችሁ ግን የወንድማችሁን ነፍስ ትነክሳላችሁ፤ ታቆስሉትማላችሁ፡፡ እንዲህ በማድረጋችሁ ራሳችሁን፣ ወንድማችሁንና ሌሎች ብዙ ሰዎችን ትጎዳላችሁ፡፡” 

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ!

Saturday, June 2, 2012

ርደተ መንፈስ ቅዱስ - በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ!!


  መንፈሳዊ ጸጋቹ በዛሬው ዕለት በእኛ ላይ በምላት ወርዷልና መንፈስ ቅዱስን በመንፈሳዊ ጣዕመ ዝማሬ ከፍ ከፍ እናድርገው፡፡ ምንም እንኳን ያገኘነውን የጸጋ ታላቅነት ለመግለጽ የእኛ ቃላት በጣም ደካሞች ቢሆኑም እንደ አቅማችን ኃይሉንና ሥራውን ከማመስገን አንከልከል፡፡
  
 እያከበርን ያለነው የጴንጤ ቆስጤ በዐል ነው፤ የርደተ መንፈስ ቅዱስ ቀን፣ ተስፋ ፍጻሜ ያገኘበት ቀን፣ መጠበቅንና የመዳንን ናፍቆት ያበቃበት ቀን፣ ጸሎተ ሐዋርያት መልስ ያገኘበት ቀን፣ ዐስበ ትዕግሥትን ያየንበት ቀን፡፡ የዛሬው ዕለት በዔቦር ዘመን ቋንቋን የደበላለቀ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ የእሳት ላንቃዎችን ሲያሳይ የተመለከትንበት ነው /ዘፍ.10፡25/፡፡ በዔቦር ዘመን አስወቃሹንና አሳፋሪውን የሰው ልጅ ፈቃድ ለመግታት ቋንቋቸውን የደበላለቀ መንፈስ ቅዱስ ዛሬ ግን ደቀመዛሙርቱ ሁሉም በአንድ ቤት ሳሉ ድንገት እንደሚነጥቅ አውሎ ንፋስ መጥቶ ቤቱን ሲሞላው፤ እንደ እሳት የተከፋፈሉ ልሳኖችም ሲያሳያቸው፤ በፈቃዱም የሰባኪነትን ልሳን ሲሰጣቸው አየን፡፡
  
 ይህ ቅዱስ መንፈስ በሥነ ፍጥረት መጀመርያ በውኃ ላይ ሲሰፍ አየነው፤ በኋላ በዘመነ ሐዲስም በጌታችን ራስ ላይ ሲያርፍ አየነው፡፡
  
 ይህ በርግብ አምሳል በጥፋት ውኃ ላይ በርሮ የንፍር ውኃ መጉደሉን ለኖኅ ያበሰረ መንፈስ ቅዱስ በኋላም በርግብ አምሳል በዮርዳኖስ ውኆች ላይ በመታየት ሲጠመቅ የነበረውን በግ ለዓለም ሁሉ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ መሆኑን ሲገልጥ ሲመሰክር አየነው፡፡
   

FeedBurner FeedCount