Tuesday, September 30, 2014

ለይሖዋ ምስክሮች ኑፋቄ የተሰጠ ምላሽ (ክፍል አንድ)

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 21 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
  የይሖዋ ምስክሮች የተባለው ተቋም እ.ኤ.አ. በ1870 ላይ የተመሠረተ ሲኾን፥ መሥራቹም ፔንሳልቫንያ በምትባለው የአሜሪካ ግዛት እ.ኤ.አ. በ1854 ላይ የተወለደው ቻርለስ ራስል የተባለ ግለሰብ ነው፡፡ ይኽ ሰው ከጓደኞቹ ጋር በየጊዜው እየተገናኘ መጽሐፍ ቅዱስ ያጠና ነበር፡፡ የኋላ ኋላ ግን በተለያዩ የክሕደት ትምህርቶች ውስጥ ወደቀ፡፡ ከክሕደቶቹ መካከልም “ነፍስ ትሞታለች፤ ሥላሴ የሚባል ትምህርት የለም፤ ወልድ ፍጡር በመለኮቱ፤ ክርስቶስ በሥጋ አልተነሣም፥ በፍጹም ሥጋም ወደ ሰማይ አላረገም፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ሚካኤል ነው፤ ዘለዓለማዊቷ ገነት ይኽቺ የምንኖርባት ምድር ነች፤ ኃጢአተኞች ፈጽመው ከመኖር ወዳለመኖር ይጠፋሉ እንጂ የዘለዓለም ስቃይ የሚባል አያገኛቸውም፥ ሰይጣንም ቢኾን ወደአለመኖር ይጠፋል እንጂ አይሰቃይም፤ መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ኃይል እንጂ አካላዊ አይደለም” የሚሉ ይገኙበታል፡፡ ለዚኹ ትምህርቱ ይረዳው ዘንድም መጽሐፍ ቅዱስን በማጣመም “የአዲሲቱ ዓለም መጽሐፍ ቅዱስ” በማለት የራሱ የኾነ መጽሐፍ አዘጋጅቷል፡፡ በአኹኑ ሰዓትም ይኽን የክሕደት ትምህርታቸውን በተለያዩ ቋንቋዎች በማዘጋጀት ብዙ ሰዎችን እያታለሉ ይገኛሉ፡፡ እኛም፥ እግዚአብሔር በፈቀደልን መጠን፥ እነዚኽ ተረፈ አርዮሳውያን በትምህርተ ሥላሴ ዠምረን ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች አንድ በአንድ መልስ እንሰጥበታለን፡፡ ለዚኽም እግዚአብሔር ዓይነ ልቡናችንን ያብራልን፤ አሜን!!!

Monday, September 29, 2014

ሥነ ፍጥረት (ለሕፃናት)- ክፍል ኹለት



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 19 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 እንደምን ናችኁ ልጆች? ትምህርት በደምብ ዠመራችኁ? እንዴት ነው ታድያ ትምህርት? በጉጉት እየተከታተላችኁ ነው አይደል? ጐበዞች፡፡ አኹን የምትማሩት ትምህርት ለወደፊት ኑሮአችኁ መሠረት በመኾኑ ተግታችኁ ተማሩ፤ እሺ?! እግዚአብሔር ብርታትን እንዲሰጣችኁ፣ የእናንተንና የቤተ ሰቦቻችኁ ጤንነት እንዲጠብቅላችኁም ዘወትር ጸልዩ፡፡ እግዚአብሔር ጸሎታችኁን እንዲሰማችኁም ለወላጆቻችኁና ለታላላቆቻችኁ በቅንነት ታዘዙ፡፡ ይኽን ካደረጋችኁ፥ ዕቅዳችኁና ምኞታችኁ ይሳካላችኋል፡፡
 ልጆች! ባለፈው ሳምንት የተማርነውን ታስታውሳላችኁ? እስኪ ምን ምን ተማርን? ጐበዞች!!! ጥያቄውንስ ሠራችኁት? ስንት አመጣችኁ? እናንተ ጐበዞች ስለኾናችሁ ደፍናችኁታል አይደል? በጣም ጐበዞች፡፡ ለዛሬ ደግሞ እግዚአብሔር ረቡዕ፣ ሐሙስ እና ዓርብ ምን ምን እንደፈጠረ እንማራለን፡፡ እግዚአብሔር ልቡናችንን ይክፈትልን፡፡ አሜን!!!

Tuesday, September 23, 2014

ትምህርተ ሃይማኖት (ክፍል ኹለት)

 (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 13፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

የሃይማኖት አዠማመርና ዕድገት

 የተለያዩ ሰብአ ዓለም (የዚኽ ዓለም ሰዎች) የሃይማኖት አመጣጥን በተመለከተ የተለያየ ዓይነት አመለካከት ቢኖራቸውም፥ እኛ ኦርቶዶክሳውያን ግን ሃይማኖት ገና ከፍጥረት መዠመሪያ (ከዓለመ መላዕክት) ዠምሮ የነበረ መለኮታዊ ስጦታ ነው ብለን እናምናለን /ሐዋ.17፡26/፡፡ የመዠመሪያዎቹ ምእመናንም ቅዱሳን መላዕክት ናቸው፡፡ ይኽ እንዴት እንደኾነም በሥነ ፍጥረት ትምህርታችን የምንመለስበት ይኾናል፡፡
ከቅዱሳን መላዕክት በኋላ ይኽቺው ነቅዕ፣ ኑፋቄ የሌለባት ንጽሕት ሃይማኖት አዳምና ሔዋን በተፈጠሩ በ40 እና በ80 ቀናቸው ተቀብለዋታል፡፡

Monday, September 22, 2014

ሥነ ፍጥረት (ለሕፃናት)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 12 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ልጆች እንደምን ከረማችኁ? የዕረፍት ጊዜአችኁ እንዴት አለፈ? መልካም ልጆች፡፡ እንግዲኽ ዘመነ ማርቆስ አልፎ አኹን ዘመነ ሉቃስ ገብተናል፡፡ ለአዲሱ ዓመት ያደረሰንን አምላክ እያመሰገንን በዚኽ ዓመት ደግሞ ጊዜያችንን በአግባቡ ተጠቅመን፣ በትምህርታችንም በርትተን ለጥሩ ውጤት መብቃት አለብን እሺ፡፡ ምክንያቱም ጊዜውን በአግባቡ የማይጠቀም ልጅ መጨረሻው አያምርም እሺ ልጆች፡፡ ስለዚኽ ጊዜአችንን በአግባቡ መጠቀም አለብን፡፡ ለዚኽም እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

FeedBurner FeedCount