Friday, December 19, 2014

የንስሐ ልጆቼን እንዴት ላገልግል? (የመጨረሻው ክፍል)

በዳዊት አብርሃም
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ቅዳሜ ታኅሳስ 11 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የጽሑፉ ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፥ የግንቦት 2005 ዓ.ም. እትም ነው፡፡
ኃጢአትን በመናዘዝ ውስጥ የሚገኝ ፈውስ
ከኃጢአት እስራት በንስሐ ለመፈታት ፈልጐ ወደ ካህኑ የሚቀርብ ተነሳሒ የሚታይበትና ከዚያም በሒደት አልፎበት በመጨረሻ የሚደርስበት የመንፈስና የሥነ ልቡና ኹኔታ አለ፡፡ ይኽንን ኹኔታ ቀሲስ ፋሲል ታደሰ እንደሚከተለው ይገልፁታል፡፡
ደረጃ አንድ
ተነሳሒው ለመዠመሪያ ጊዜ ሲመጣ የተረበሸ ኹኔታ ፊቱ ላይ ይነበባል፡፡ ቁጣ ቁጣ የሚለው የዘለፋና ወቀሳ የሚያበዛ ለራሱ የሰጠውን ዝቅተኛ ግምትና ውስጡ ያደረውን ታላቅ ተስፋ መቁረጥ ቁልጭ አድርገው የሚያሳዩ ኹኔታዎች ከገጽታው ይነበባል፤ ካንደበቱ ይደመጣል፡፡

Wednesday, December 17, 2014

የንስሐ ልጆቼን እንዴት ላገልግል? (4)

በዳዊት አብርሃም
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐሙስ ታኅሳስ 9 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የጽሑፉ ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፥ የግንቦት 2005 ዓ.ም. እትም ነው፡፡
መንፈሳዊ ቤተ ሰብ
ቀሲስ ጥላኹን ታደሰ 110 ያኽል የንስሐ ልጆቻቸውን በጥንቃቄ መዝግበው ይዘዋል፡፡ ይኽም እያንዳንዱ የንስሐ ልጅ ያለበትን ደረጃ ለመከታተል አስችሏዋቸዋል፡፡ ከመዠመሪያው የንስሐ ልጆቻቸውን ለመቀበል መንፈሳዊ መስፈርቶችን በቅድመ ኹኔታነት ያስቀምጣሉ፡፡ በመዠመሪያ ግን የሚያቀርቡት ጥያቄ “ለምን የንስሐ አባት አስፈለገህ?” የሚል ነው፡፡ ይኽን ጥያቄ የሚያነሡት እያንዳንዱ የንስሐ ልጅ ትክክለኛውን ዓላማ ይዞ የንስሐ ሕይወቱን እንዲዠምር ለማድረግ ነው፡፡ ቀጥለው መስፈርቶቹን ይነግሩታል፡፡ ተስማምቶ ቢቀጥል እንኳ በየጊዜው ለመፈጸም የተስማማባቸውን መስፈርቶች በትክክል እየፈጸመ መኾኑን ከመመርመር አያቆሙም፡፡

Monday, December 15, 2014

የንስሐ ልጆቼን እንዴት ላገልግል? (3)

በዳዊት አብርሃም
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ማግሰኞ ታኅሳስ 7 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የጽሑፉ ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፥ የግንቦት 2005 ዓ.ም. እትም ነው፡፡
ወጣቶችን ለንስሐ መጥራት
ለንስሐ አባትና ልጅ ግንኙነት እንደ አንድ ተግዳሮት እየኾነ ያለው ነገር የትውልድ ክፍተትና የባሕል ልዩነት ነው፡፡ በተለይ በከተሞች ውስጥ የሚኖሩ ወጣቶችን ዘመን አመጣሽ ችግሮች ተገንዝቦ መፍትሔ መስጠት በዕድሜ ከፍ ላሉትና ከገጠሩ አከባቢ ለመጡት ካህናት አስቸጋሪ ነው፡፡
 ቀሲስ ፋሲል ታደሰ ሌሎች ችግሮችንም ያወሳሉ፡- “የንስሐ ልጆች ከአባቶች ጋር ተገናኝተው ለመወያየት አመቺ ቦታም የሚጠፋበት ጊዜ አለ፡፡ ብዙ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን አፀድ ስር እየተገናኘን ለመነጋገር ብንሞክርም በጕባኤ ሰዓት ወይም በሌሎች የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ሰዓት መወያየት ከባድ ይኾናል፡፡”
 ለዚኽ ችግር እንደ መፍትሔ ቢኾን ብለው ቀሲስ ፋሲል አንዲት ቢሮ ከፍተዋል፡፡ አራዳ ጊዮርጊስ አከባቢ የምትገኘው ቢሯቸው (በአኹኑ ሰዓት 5 ኪሎ በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ ውስጥ ነው) በመጠን አነስተኛ ብትኾንም በውስጧ በርካታ መጻሕፍትን የያዘች ናት፡፡ ቀሲስ ስለዚኽ ነገር ሲያስረዱ፡- “ተነሳሕያኑ ምክር ከተቀበሉ በኋላ ስለ ሃይማኖታቸውም ኾነ ስለ ግል መንፈሳዊ ሕይወታቸው ዕውቀታቸው እንዲዳብር የተመረጡ መጻሕፍትን አውሳቸዋለኹ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን የንባብ ፍቅር ስለሚያድርባቸው ራሳቸው እየገዙ ማንበብ ይዠምራሉ፤ እንዲያውም ለእኛ ያመጡልናል” ይላሉ፡፡

Wednesday, December 10, 2014

የንስሐ ልጆቼን እንዴት ላገልግል? (2)

በዳዊት አብርሃም
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐሙስ ታኅሳስ 2 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የጽሑፉ ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፥ የግንቦት 2005 ዓ.ም. እትም ነው፡፡
የንስሐ ልጆች ጕባኤ
 አኹን አኹን የንስሐ ልጆቻቸውን መንፈሳዊ ፍላጐት ለማሟላት ጕዳይ እያሳሰባቸው የመጡ ካህናት የንስሐ ልጆቻቸውን የሚያሳትፍ ወርሐዊ ጕባኤ ያዘጋጃሉ፡፡ ቀሲስ አንተነህ ጌጡ ከእነዚኽ ካህናት አንዱ ናቸው፡፡ ቀሲስ አንተነህ በማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም የትግበራ ቡድን አስተባባሪ ሲኾኑ በመደበኛ አገልግሎታቸው ተይዘው ዋነኛ የክህነት ተግባራቸውን ከፍጻሜ ሳያደርሱ እንዳይቀሩ በማለት 94 ለሚኾኑት የንስሐ ልጆቻቸው በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ ላይ ወርኃዊ ጕባኤ ማዘጋጀት ከዠመሩ ሦስት ዓመት ሞላቸው፡፡ አዠማመሩን ሲገልጹ “የንስሐ ልጆቼ ጥቂት በነበሩ ጊዜ መገናኘት ቀላል ነበር፡፡ እየበዙ ሲሔዱ ግን አንድ በአንድ ዘወትር ማግኘት ይቸግራል፡፡ በዚኽ ጊዜ ደግሞ የንስሐ ልጆች መንፈሳዊ ሕይወት እንዳይጐዳ ለማድረግ በግለሰብ ደረጃ ያለውን ግንኙነት እንደ አስፈላጊነቱ በቀጠሮ እያደረጉ ኹሉን ደግሞ በቋሚ መርሐ ግብር በየወሩ በሚሠራ ጕባኤ ማከናወን ጥሩ አማራጭ ኾኖ ተሰማኝ፡፡”

FeedBurner FeedCount