Sunday, October 11, 2015

ዕለት ዕለት ቃለ እግዚአብሔርን ለማያነቡ ሰዎች የተሰጠ ተግሣፅ



በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 30 ቀን፣ 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ቃለ እግዚአብሔር መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡፡ ይህን መንፈሳዊ መሣሪያ እንዴት እንደምንጠቀምበትና እንደምንታጠቀው ካላወቅንበት ግን በእጃችን ስላለ ብቻ ምንም ሊጠቅመን አይችልም፡፡ ጠንካራ ጥሩርና ራስ ቍር፣ ጋሻና ሰይፍ አለ እንበል፡፡ አንድ ሰው መጥቶም እነዚህን ታጠቃቸው፡፡ ነገር ግን ጥሩሩን በእግሩ፣ ራስ ቍሩን በራሱ ላይ ሳይኾን በዓይኑ ላይ፣ ጋሻውን በደረቱ ላይ ሳይኾን በእግሩ ላይ አሰረው እንበል፡፡ እንግዲህ ይህ ሰው እነዚህን መሣሪያዎች ስለ ታጠቀ ብቻ ጥቅም ያገኛልን? ይባስኑ የሚጎዳ አይደለምን? ይህ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ይህ ሰው ተጠቃሚ ያልኾነው ግን ከመሣሪያው ድክመት አይደለም፤ እንዴት መጠቀም እንዳለበት ሰውዬው ስለማያውቅ እንጂ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ዘንድም እንደዚህ ነው፡፡ ትእዛዙን በአግባቡ የማንጠቀምበት ከኾነ የቃሉ ኃይል ምንም ባይቀንስም እኛ ግን ምንም የምንጠቀመው ነገር አይኖርም፡፡

Thursday, October 8, 2015

ዘመነ ጽጌ



በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 27 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ክኅሎቱ ከፍጡራን ኅሊና በላይ የሆነ የቅዱሳን አምላክ የመላው ዓለም ፈጣሪ "ይህን" የሚታየውንና "ያን" የማይታየውን ሁሉ መልካም አድርጎ ፈጥሮታል:: በዚህም ሁሉ ውስጥ ፍጥረታቱ ለመገኘታቸው ሦስት መንገዶች እና ሦስት አላማዎች ታይተዋል:: መንገድ ላልነው በኃልዮ(በማሰብ) የተፈጠሩ አሉ እንደመላእክት ያሉት ለዚህ ምሳሌ ሆነው ይቀርባሉ:: ደግሞም በነቢብ(በመናገር) የተፈጠሩ አሉ እንደ ብርሃን ያሉትን ለአብነት መጥቀስ የሚቻል ሲሆን በሦስተኛው መንገድ በገቢር (በሥራ) የሰውን ልጅ ብቻ ፈጥሮታል:: ለሦስት አላማ ያልነውን ስናይ ደግሞ፡-

Tuesday, October 6, 2015

የማክሰኞ ፍጥረታት



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 25 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ትምህርተ ሃይማኖት - ክፍል ዐሥራ አምስት
ሦስተኛይቱ ዕለት ዕለተ ሠሉስ ትባላለች፡፡ ሠሉስ ማለት ለፍጥረት ሦስተኛ ማለት ነው፡፡ በአማርኛ ማግሰኞ ትባላለች፤ የሰኞ ማግስት እንደ ማለት ነው፡፡ በተለምዶ ግን ማክሰኞ እንላለን፡፡ እኛም አንባብያንን ግራ ላለማጋባት በዚህ አካሔድ እንቀጥላለን፡፡
እግዚአብሔር አምላካችን ሰኞ ላይ ውኃዉን ከሦስት ከፍሎ ምድርን ግን ከውኃ እንዳልለያት ተነጋግረን ነበር፡፡ በዚህ ዕለት ማለትም ማክሰኞ ላይ ግን በዚህ ዓለም የነበረውን ውኃ ወደ አንድ ስፍራ እንዲሰበሰብ አድርጓል፡፡ ውኃው ሲሰበሰብም ምድር ተገልጣለች፡፡ ነገር ግን ተገለጠች እንጂ ቡቃያ አልነበረባትም፡፡ በመኾኑም በምሳር የሚቈረጡ (እንደ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ወዘተ)፣ በማጭድ የሚታጨዱ፣ በጥፍር የሚለቀሙ (እንደ ሎሚ፣ እንደ ትርንጎ ያሉ) አዝርእትን፣ አትክልትንና ዕፅዋትን እንድታስገኝ አዘዛት፡፡ ምድርም የቃሉን ትእዛዝ አድምጣ እነዚህን ሦስት ፍጥረታትን አምጣ ወለደች /ዘፍ.1፡12-14/፡፡

Sunday, October 4, 2015

የዘመናችን አጥማቂ ነን ባዮች፡- የሐሳዊው መሲሕ መንገድ ጠራጊዎች

በዲ/ን ዳንኤል ክብረት
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መስከረም 23 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ክፍል ሁለት
1.   ተአምራት ማድረግ የምን ውጤት ነው? ተአምራት ማድረግ ከሁለት ነገሮች ሊመጣ ይችላል፡፡ ከመንፈሳዊ ብቃትና ከሰይጣን አሠራር፡፡ በክርስትና ሕይወቱ የበረታ ሰው መንፈሳዊ ብቃቱ በሕይወቱ በሚገለጡ ተአምራት ሊታወቅ ይችላል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የምናገኛቸው ቅዱሳን በገድል ተቀጥቅጠው፣ ሰማዕትነት ከፍለው፣ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው በሚገባ ተጉዘው ዲያብሎስን ድል ሲነሡት በሕይወታቸው ውስጥ ተአምራት ይገለጣሉ፡፡ ይህም ማለት ተአምራት የመንፈሳዊ ብቃት መገለጫ ነው ማለት ነው፡፡ የተአምራት ስጦታ እንዲሁ በድንገት አይገለጥም፡፡ በዚያ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ እያደገ፣ እየተገለጠና እየተመሰከረለት በሚመጣ መንፈሳዊ ዕድገት ምክንያት እንጂ፡፡ ለዚህ ሁለት ምሳሌዎች እናንሣ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስና አቡነ ተክለ ሃይማኖት፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ በሐዋርያት ሥራ ውስጥ አራት ምዕራፍ ያለው መንፈሳዊ ዕድገቱ በየዘመናቱ ተገልጦልናል፡፡ በፍኖተ ደማስቆ መመለሱ(የሐዋ8) በአንጾኪያ በሱባኤ መኖሩ(የሐዋ13) ለአገልግሎት ተጠርቶ ከበርናባስ ጋር መውጣቱ እና ከአረማውያን፣ ከአይሁድና ከመናፍቃን ጋር ባደረገው ተጋድሎ የምናገኘው በትምህርትና በተአምራት የተገለጠ ሕይወቱ ናቸው፡፡ የቅዱስ ጳውሎስ ሕይወት ቀስ በቀስ እያደገ (ወየሐውር እም ኃይል ውስተ ኃይል እንዲል) የመጣ ነው፡፡

FeedBurner FeedCount