Wednesday, November 5, 2014

አምስቱ ስጦታዎች

በቀሲስ ፋሲል ታደሰ




(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጥቅምት 27 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! 

ሥርዓተ አምልኮ ከሚገለጥበት መንገድ አንዱ ስጦታ ነው፡፡ የሰው ልጅ ከራሱ የኾነ አንዳች የለውም፤ በጎ የኾነው ኹሉ ከፈጣሬ ዓለማት ከእግዚአብሔር ያገኘው ነው፡፡ በመኾኑም ፈጣሪያችን መስጠትን እንዳስተማረን ኹሉ እኛም ተገዥነታችንን ከምንገልጥበት አንዱ ከርሱ የተቀበልነውን በፈቃደኝነት በደስታ በመስጠት ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት ይኽን ሲያስረዳ “ኹ ከአንተ ዘንድ ነውና፡ ከእጅህ የተቀበልነውን ሰጥተንሃልና ይኽን ያኽል ልናቀርብልህ የቻልን ማነን? በፈቃዴ ይህን አቅርቤአለሁበማለት ከእግዚአብሔር ያገኘውን ሀብት በደስታ በፈቃዱ ለቤተ መቅደስ ሥራ እንዲውል መስጠቱን በመግለጽ ስለ ስጦታ ጽፏል /1ዜና 29÷9-16/፡፡


ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስነገር ግን ኹሉ በአግባብና  በሥርዓት  ይኹን” በማለት እንዳስተማረን ለእግዚአብሔር የምንሰጠውን የአምልኮ መግለጫ በሥርዓት ልናደርገው እና ከልብ  ሊኾን ይገባል፡፡ ለዚኽ ደግሞ መሠረቱ  የስጦታ ዓይነቶችንና የአቀራረብ ሥርዓቱን ማወቅ ነው፡፡ በዚህች አጭር ጽሑፍም በሥርዓተ ቤተክርስቲያን መሠረት መንፈሳዊ ምግባራት የኾኑት አምስቱ የስጦታ ዓይነቶች ምጽዋት፡ መባዕ፡ ስዕለት፡ በኩራት እና ዐሥራትን እንመለከታለን፡፡


1.     ምጽዋት፡-

ምጽዋት መስጠት ከገንዘብ፡ ከዕውቀት ከንብረትላይ  ለእግዚአብሔር ቤት መለገስ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንቀጸ ብጹዓን ትምህርቱብጹዓን መሐርያን የሚምሩ ብጹዓንናቸው ያለውን ለምጽዋት ሰጥተውት ሊቃውንት ሲተረጉሙት በሦስት መንገድ ያስቀምጡታል፡፡ እነዚኽም፡-
/ምህረት ሥጋዌ፡- ይኽ የሚያስረዳው ለሥጋ የሚኾን ነገርን መለገስን ሲኾን
/ምሕረት መንፈሳዌ፡- በምክር፡ በትምህርት…. ሥነ ልቡናን የሚያንጽ (የሚያበረታታ) ማድረግን ነው፡፡
/ምሕረት ነፍሳዊ፡- ደግሞ ራስን እስከ መስጠትመጥወተ ርእስመድረስን ነው /ማቴ 5÷7 ትርጓሜ ወንጌል/፡፡
ምጽዋት ካለን ነገር ላይ ማካፈልን ያመለክታል፡፡ ለፍጹምነትም የሚያበቃ ምግባር መኾኑ የተመሰከረለት ነው፡፡ፍጹም እንድትኾን ለድኻ ስጥእንዲል /ማቴ 19-21/፡፡የሚሰጥ ብጹዕ ነውየሚለውም ኃይለ ቃልኽን ያስረዳል /ሐዋ. 20÷35/፡፡ በነገረ ምጽአትም ከሕይወት ቃል አንዱ በምጽዋት የሚገኝ መኾኑ እሙን ነው /ማቴ.25-35/፡፡
ምጽዋትን በልብስ፡ በገንዘብ፡ እንጀራ በመቁረስ የመሳሰሉትን ለደሃ በመስጠት፡ በማካፈል መግለጽ ይቻላል፡፡ በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ምእመናን ሀብታቸውን ለደሃ ያካፍሉ ነበር /ሐዋ 4÷32 6÷1-6/፡፡ እንደዚኹም እውቀትን ማካፈል፡ ምክር መለገስ ከምጽዋት የሚቆጠር ሲኾን ለእግዚአብሔር ቤትም በገንዘብ፡ በጉልበትና በስጦታችን ማገልገል የምጽዋትን ዋጋ ያስገኛል /ኢሳ 58÷7 ሮሜ 12÷8 ዘዳ. 15÷11-15 ምሳ 3÷27/፡፡ በረከተ ሥጋ ወነፍስ የሚያስገኘውንና በደልን የሚያስወግደውን የልግስና  ስጦታ /ምጽዋትን/ ልማዳችን ማድረግ ይገባናል /ዳን. 4÷27/፡፡

2. መባዕ፡-

ለአምላካችን ለልዑል እግዚአብሔር ከሚቀርቡ የስጦታ ዓይነቶች አንዱ መባዕ ነው/ ዘሌ 1÷3 ዘኁ.7÷12/፡፡ ነቢዩ ዳዊት መባ ለእግዚአብሔር ቤት እንደሚገባ ሲገልጽእበውእ ቤተከ ምስለ መባእየ፡ መባዬን በመያዝ ወደቤትኅ እገባለኹ” ብሏል /መዝ 65÷13/፡፡ መባዕ ለቤተመቅደስ መገልገያ የሚኾንና ንዋያተ ቅድሳትን በመስጠት የሚፈጸም ሲኾን ለምሳሌ ጧፍ፡ ዕጣን፡ ዘቢብ፡የመሳሰሉት በአጥቢያችን እና በተለያዩ ገዳማት ስንሔድ ይዘን መግባት ይጠበቅብናል /ዘዳ. 13÷35 34÷20/፡፡
መባዕ ማቅረብ የተገዥነት መገለጫ በመኾኑ በረከት የሚያስገኝ ምግባር ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያንም በጸሎተ መባዕ በካህኑ በሚደርስው ሥርዐተ ጸሎት መሠረት የመንፈሳዊ ጸጋ ተሳታፊ ያደርጋል /ማቴ. 5÷24 ማር 7÷10-12/፡፡

3. ስዕለት፡-

ስዕለት  ሰው በፈቃዱ አንድ ነገር ለእግዚአብሔር ለማድረግ /ደስታውን ለመግለጥ/ ቃል የሚገባበት ሥርዓት ነው፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት በቅዱሳን አማላጅነት  በማመንና በመማጸንይኽ ቢደረግልገኝ ይኽን አደርጋለኁ” በሚል አገላለጽ ቃል የሚገቡበት የስጦታ ዓይነት ነው፡፡ ስዕለት እምነታችንን የምንገልጽበትም በመኾኑ በሥርዐት እና ከልብ ኾነው ስእለት ሊሳሉ ይገባል፡፡ ጠቢቡ ሰለሞን ይኽን “ለእግዚአብሔር በተሳልህ ጊዜ ትፈጽመው ዘንድ አትዘግይ፡ የተሳልከውን ፈጽም፡ የማትፈጽም ከኾነ አትሳልበማለት አስረድቶአል /መክ. 5÷4/፡፡ እመ ሳሙኤል ሐና እንደተሳለችና ስእለቷን እንደፈጸመች ይኽም ምግባር ቀድሞ የነበረና መጽሐፍ ቅዱሳዊ እንደኾነ የሚያስተምረን ነው /1ገኛ ሳሙ.1-1/፡፡ በረከት ለመቀበልና ፍላጎታቸው እንዲሟላ የሚሳሉም ነበሩ /ዘፍ. 28÷20 ዘሌ 20 7 ዘኁ. 21÷1-3 መሳ. 11÷30/፡፡
ስእለትን በአግባቡ መሳል እና በቃላችን መሠረት መፈጸም የሚገባ ሲኾን ነገር ግን ቃልን አለመጠበቅ ደግሞ ኃጥአት ስለመኾኑ እንዲኽ ተጽፏል፡- “ለአምላክህ ለእግዚአብሔር  ስእለት በተሳልህ ጊዜ አምላክህ እግዚአብሔር ከአንተ ፈጽሞ ይሻዋልና ኃጥአትም ይኾንብሃልና መክፈሉን አትዘገይ፡፡ ባትሳል ግን  ኃጥአት የለብኽም በአፍህ የተናገርኸውን ለአምላክህ ለእግዚአብሔር በፈቃድህ ተስለሃልና ከከንፈርህ የወጣውን ታደርግ ዘንድ ጠብቅ” /ዘዳ. 23÷21-23 ምሳ. 20÷25/፡፡

4. በኩራት

በኩር ማለት የመዠመሪያ ማለት ሲኾን የበኩራት ስጦታ ከልጅ፤ ከከብት፤ ከንብረት… ከመሳሰለው የመዠመሪያውን መስጠት ነው፡፡ የአዳም ልጅ አቤል መሥዋዕት ሲያቅርብ “መዠመሪያውን ለየ” የሚለው በኩራቱን ስለማቅረቡ ሲያስረዳ ሲኾን፡ ይኽም የተወደደ መሥዋዕት ኾኖለታል /ዘፍ. 4፡4/፡፡ ከዘመነ ኦሪት ዠምሮ ሕዝበ እግዚአብሔር አምልኮታቸውን ከሚገልጹበት አንዱ በኩራት ነበር፡፡ ከልጆቻቸው፤ ከምርታቸው.... በኩር  የኾነውን ለእግዚአብሔር ቤት ይሰጣሉ /ዘኁ 3፤42፤ 1ሳሙ 2፤ ዘኁ 18፤15-17/፡፡
በኩራትን ማቅረብ እጅግ የተወደደ እና ከኹሉ የሚበልጥ የስጦታ ዓይነት ነው /ዘዳ.23÷19፤ ዘዳ.26/፡፡ ክርስቲያኖችም ኹላችንም ሥርዓተ አምልኮ የምንገልጥበት አንዱ የኾነውን በኩራቱን በማቅረብ ሕገ አምላክን ልንጠብቅ ይገባል፡፡ ይኽንንም ከመዠመሪያ ምርታችን፡ ከመጀመሪያ ደሞዛችን ለእግዚአብሔር ቤት በመስጠት የተናገረውን ከማያስቀረው አምላካችን በረከት እንደምናገኝ በማመን ልንፈጽም ይገባናል /ዘዳ28÷1-15/፡፡

5. ዐሥራት

ዐሥራት አንድ አሥረኛ ማለት ነው፡፡ ከሚያገኙት ገቢ አንድ አሥረኛውን ለእግዚአብሔር ቤት መስጠትን ያመለክታል፡፡ ከሙሴ በፊት በዘመነ አበው የተዠመረ የእግዚአብሔር ሕግ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዐሥራት በስፋት ይገልጻል፡፡ ከነዚኽም ለአብነት ያኽል በጥቂቱ እንመልከት፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዐሥራት አበ ብዙሓን አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ መልከ ጼዴቅ በሔደ ጊዜ ዐሥራት ማውጣቱን “አብርሃምም ከኹሉ ዐሥራት ሰጠው” በማለት ዐሥራትን አበው እንደ ዠመሩት ያስረዳናል /ዘፍ 14÷20/፡፡ ያዕቆብ ከአባቶቹ የወረሰውን ሕገ አምላክ የኾነውን ዐሥራት ማውጣትን ሲገልጽ “ከሰጠኸኝ ኹሉ ለአንተ ከዐሥር አንዱን እሰጣለኹ” ብሏል /ዘፍ 28÷ 1-22/፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዐሥራት ሲያስረዳን ከእግዚአብሔር የታዘዘ መኾኑን አጽንኦት በመስጠት  ነው፡፡ “ከምታገኘው ኹሉ ዐሥራትን ታወጣለህ” የሚለው “ዐሥራት አስገቡ” ማለቱ እነደዚኹም የምድር ዐሥራት የእግዚአብሔር መኾኑን የሚገልጹ ማስረጃዎች ኹሉ ዐሥራት ሕገ አምላክ መኾኑን ያረጋግጣል /ዘዳ. 14÷22፤ ዘሌ.27÷30፤ ዘዳ.12÷17፤ ዘዳ.14÷23፤ ሚል.3÷10/፡፡
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ “የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ስጡ” ማለቱ አምላካዊ ትዕዛዝ መኾኑን ያስገነዝበናል /ማቴ 22÷17/፡፡ እንደዚኹም አንድ ቀራጭ ወደ ጌታችን ቀርቦ “ከማገኘው ዐሥራት አመጣለኹ” ማለቱ ቀድሞ የነበረ ሕግ መኾኑን የሚያመለክት ሲኾን ጌታችንም ቀራጩን በዐሥራት ጉዳይ ላይ መልስ አለመስጠቱ ዐሥራት ተገቢ የኾነ ሥርዓት መኾኑን የሚያመለክት ነው /ሉቃ 18÷12/፡፡

ዐሥራት በመስጠታችን የምናገኘው ጥቅም ምንድን ነው?
ሀ. በረከት ይበዛልናል
ዐሥራት ማውጣት ትዕዛዝን መፈጸም ነውና በአምላካዊ ቃሉ መሠረት በረከቱን ያበዛልናል፡፡ “ቃሌን ብትሰማ በረከቶች ኹሉ ላንተ ይኾናሉ” በማለት ቃል እንደገባልን ዐሥራት በማውጣት ለቃሉ ብንገዛ ሀገር፤ ቤት፤ ትዳር፤ ልጆች   ወዘተ ኹሉም እንደሚባረኩ የታመነ ነው /ዘዳ.28÷1-20/፡፡ በነብዩ በሚልክያስ የተጻፈው ቃለ እግዚአብሔር እንደሚያረጋግጥልን የእግዚአብሔር ገንዘብ የኾነውን ዐሥራት በማውጣት ብንታዘዝ “የሰማይ መስኮትን እከፍታለኹ በረከትን እሰጣለሁ” በማለት አስገንዝቦናል /ሚል. 3÷10/፡፡
ለ. ለጽድቅ ያበቃል
“ሕግን የሚሠሩ ይጸድቃሉ”  እንዳለ ዐሥራት ሕግን መፈጸም ነውና ለጽድቅ የሚያበቃ መኾኑን ልናምን ይገባል /ሮሜ12፤12/፡፡ ሕገ እግዚአብሔርን በመፈጸም ምሕረተ ሥጋ ወነፍስ የምናገኝ መኾኑንም በማይሻር ቃሉ እንዲኽ ብሏል፡- “ትዕዛዜን ለሚጠብቁ ምሕረትን የማደርግ እኔ ነኝ” /ዘዳ 20÷6/፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም ከልብ በኾነ ፈቃደኝነት ዐሥራት በመስጠት ክርስትናችንን እንድንገልጽና ለጽድቅ  እንድንበቃ መክረውናል፡፡ በመኾኑም ከምናገኘው ገቢ ላይ ከዐሥር አንድ አስበን ለእግዚአብሔር ቤት በመስጠት ለመንፈሳዊ ዋጋ ልንተጋ ይገባል፡፡ “በበረከት የሚዘራ በበረከት ያጭዳል” ተብሏልና /1ኛ ቆሮ.16÷14፤ 2ኛ ቆሮ.9÷6-12/፡፡
ነገር ግን በተቃራኒው ዐሥራት በስስትና በተለያዩ ምክንያቶች አለመክፈል ከእግዚአብሔር ጸጋ ያርቃል፡ መርገምንም ያመጣል፡፡ “ሰርቃችሁኛል…..ይኽም ዐሥራትና በኩራቴን ነው” የሚለው ኃይለ ቃል የሚያስረዳውም ዐሥራት አለመክፈል ከእግዚአብሔር ገንዘብ ላይ መስረቅ መኾኑን ነው፡፡ በነቢዩ በኢሳያስ የተነገረውም ያለመታዘዝን ጉዳት ያስረዳል “እምቢ ብትሉ ሰይፍ ይበላችኋል” /ኢሳ.1÷19/ እንዲል፡፡
ዐሥራት አከፋፈል
ዐሥራት መክፈል አምልኮተ እግዚአብሔርን ከምንገልጽበት ተግባር አንዱ መኾኑን ከተገነዘብን፡ አከፋፈሉንም በማስተዋል ልንፈጽም  ያስፈልጋል፡፡ ዐሥራት ከገቢ /ከደመወዝ/ ከዐሥር አንዱን በየወሩ ለቤተ ክርስቲያን በመምህር ንስሐ በኩል ወይም በቀጥታ በመሔድ በየወሩ ልንከፍል ይገባል፡፡ የምንከፍለውን ዐሥራት ለገጠርም ኾነ ለአጥቢያችን ስናበረክት ማረጋገጫ መቀበልም ሳንዘነጋ ነው፡፡
አገልግሎቱም፡-
ሀ.ሥርዓተ አምልኮ ለማስፈጸም
የምንከፍለው አሥራት ለሥርዓተ አምልኮ ማስፈጸሚያ ይኾናል፡፡ ከዘመነ ኦሪት ዠምሮ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስረዳን የቤተ መቅደስ መገልገያ እና አገልግሎቱ በዓሥራት ስጦታ ይሟላል /ዘዳ.27÷1/፡፡ ስለኾነም ለሥርዓተ ቅዳሴ የሚያስፈልጉ፡ እና ለመንፈሳዊ አገልግሎት የሚውሉ ነገሮችን ኹሉ በካህናት አስፈጻሚነት ይሟላበታል፡፡
ለ.አገልጋዮችን ለመርዳት
በዘመነ ኦሪት ሌዋውያን በዐሥራት እንዲጠቀሙና በአግባቡ እንዲያገለግሉ ፈቃደ እግዚአብሔር በመኾኑ ለአገልጋዮች ይውላል /ዘኁ.18÷21/፡፡ በዚኽም መሠረት በዘመነ ሐዲስም በፍትሐ ነገሥት እና በቃለ ዐዋዲ በተመዘገበው መሠረት የቤተ ክርስቲያን መደበኛ አገልጋዮች የኾኑ ካህናት ከሚገባው ዐሥራት ላይ ወርኃዊ ደመወዝ እያገኙ አገልግሎታቸውን እንዲፈጽሙበት ይውላል፡፡ ዐሥራትን ሳናስቀር በአግባቡ ብንከፍል እና አገልጋዮችም አግባብ ባለው ቦታ ላይ ቢያውሉት ዛሬ የምናየውን የአገልጋዮች መጉላላት፡ የአብነት ትምህርት ቤቶች መፈታት፡ በገጠር የካህናት እጥረት…. የመሳሰሉት ችግሮችን የሚቀርፍ ዋና አማራጭ መፍትሔ መኾኑ ሊስተዋል ይገባል፡፡
ሐ. ነዳያንና ጧሪ ቀባሪ የሌላቸው ይረዱበታል
ነዳያን ከሙዳየ ምጽዋት ብቻ እንደሚረዱ የሚስተምሩ መምህራን ያሉ ቢኾንም ከሕገ ቤተ ክርስቲያን ክፍል አንድ በኾነው በቃለ ዐዋዲ ላይ እንደተጻፈው በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ የሚገኙ ደካሞች እና በተለያዩ ምክንያቶች መሥራት የማይችሉ ነዳያን ከምእመናን ከሚመጣው ዐሥራት ላይ ተቀንሶ በበጎ አድራጎት ክፍል አስተባባሪነት እንዲረዱበት ያዛል፡፡ በሙሴ እና ሌዋውያንም በስፋት በቤተመቅደስ በሚያገለግሉበት ዘመን ከዐሥራት ላይ ለነዳያን እንዲሰጡ እግዚአብሔር ስለማዘዙ ተጽፏል፡፡ ስለዚኽም ዐሥራት ለነዳያን የሚውል መኾኑንም ያረጋግጣል /ዘዳ.14÷28፡ 26÷12/፡፡
ማጠቃለያ

 መንፈሳዊ ሕይወትን ለመምራት መንፈሳዊ ዕውቀትም ያስፈልገናል፡፡ ስለኾነም የመንፈሳዊ ሕይወት መገለጫ እና በረከት ማግኛ የኾኑትን ስጦታዎችን ለማበርከት ዓይነቶቹን እና ሥርዓቱን ለይተን ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡ “ቃሉን የምትፈጽሙ ኹኑ” እንደሚል ማወቅ ደግሞ ለመፈጸም ነውና ስጦታዎቹን በረከት ለሕገ እግዚአብሔር በመገዛት ወደተግባር ልንገባ ያስፈልጋል፡፡ ከእግዚአብሔር የተቀበልነውን ያለስስት፡ እና ያለ ጥርጥር ከልብ ኾነን ለእግዚአብሔር ቤት ልንሰጥ ይገባል፡፡ “በረከት እንደማልሰጥ ፈትኑኝ” ያለን አምላካችን በአግባቡ ለምንሰጥ በረከቱን ይሰጠን ዘንድ የታመነ አምላክ ነው /ሚል 3÷9፡ 1ቆሮ 9÷6/፡፡



ውድ አንባቢያን ይኽ ጽሑፍ በሐመር መጽሔት የየካቲት 2002 .. ዕትም ላይ ወጥቶ የነበረ መኾኑን እንገልጻለን!!!

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount