Thursday, July 12, 2012

.......ብርሃናተ ዓለም......





ማነው በሁለት እግሩ ዓለምን የዞረ
ጽፎ ተናግሮ ዘክሮ ወንጌል የነገረ?
ይህች አለት ናት የቤቴ መሠረት
በሷ ቤቴን ሰራሁ ኮኩሐ ሐይማኖት

አባቴ ዼጥሮስ ...
እስኪንገረኝ...
የቱ ይበልጣል?
መረብ በባህሩ መወርወር
ወንጌል ለዓለሙ መናገር ?
ዓሣን ....ማደን
ሕዝብን ማዳን?
የቱ ይበልጣል አባቴ ...?
በጀልባ መዋሉ
ጌታን ማገልገሉ?

ተወው ዼጥሮስ ...
ለካ እኔ ሞኙ
ያልገባኝ ምስጢሩ
የበለጠውን በተግባር ነግረኸኝ
ዓለምን ተፍተህ ሞተህ አሳየኸኝ

ወዮ!......ወዮ!...
ወዮልሽ ሮም!
የኒሮን ዓለም
የቄሳሮች ሃገር
የግፍ ድንበር
የደም ባህር

ወዮልሽ ሮም ...
የዼጥሮስ ስቅለት ክስ ይሁንብሽ
የቅዱሱ ችንካር ምስክር ይጥራብሽ
በእጇ ያለ ወርቅ
............ሮም አልደመቀችበት

Wednesday, July 11, 2012

በዓለ ዕረፍቶሙ ለቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በታናሽ ኤስያ እየዞረ በቃሉ እያስተማረ በመልእክትም እየጻፈ ምእመናን በሃይማኖት እንዲጸኑ በመከራም እንዲታገሱ እየመከረ ካጽናናቸው በኋላ በሮሜ ለክርስቶስ መስክሮ እግዚአብሔርን የሚያመሰግንበት ዘመኑ ሲደርስ በ67 ዓ.ም ወደ ሮሜ ገብቶ ያስተምር ጀመር፡፡

ኔሮን ቄሳርም በዚያ ዘመን በክርስቲያን ላይ የሚቃጠለው የቁጣ እሳት ገና አልበረደለትም ነበርና ቅዱስ ጴጥሮስን አሲዞ አሰረው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ግን በምሴተ ሐሙስ ጌታው በተያዘ ጊዜ ስለ ደረሰበት ፈተና ጌታዉን አላውቀዉም ብሎ መካዱ ብቻ ትዝ እያለው ያዝን ነበር እንጂበመታሰሩ አላዘነም ነበር፡፡…

ኔሮን ቄሳርም ቅዱስ ጴጥሮስን አሲዞ ካሰረው በኋላ ወደ አካይያ ዘምቶ ነበርና በዘመቻው ድል አድርጎና ደስ ብሎት ወደ ሮሜ ሲመለስ አረማውያን የሆኑ መኳንንቱን ደስ ለማሰኘትና አማልክቱን ለማክበር ሲል በቅዱስ ጴጥሮስና በሌሎችም ክርስቲያኖች ሁሉ የሞት ፍርድ ፈረደባቸው፡፡ የቅዱስ ጴጥሮስም ሞት በመስቀል እንዲሆን ታዘዘ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት መፈረዱን በሰማ ጊዜ ጌታችን ወአመሰ ልሕቅ ባዕድ ያቀንተከ ሐቄከ ወይወስደከ ሀበ ኢፈቀድከ ብሎ የነገረው ቃል ትዝ አለውና አላውቀውም ብዬ መካዴን ሳያስብብኝ በዚህ ፍጹም ይቅርታ ያደርግልኛል በማለት እጅግ ደስ አለው፡፡

የሚቀልበትም ሰዓት በደረሰ ጊዜ ከግዞት ቤት አውጥተው ሲወስዱት ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ እኩል እንዳልሆን ራሴን ወደ ታች ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ ብሎ ለመነ፡፡

በሮማውያን ሥርዓት ቅጣት የተፈረደበት ወንጀለኛ የሮሜ ተወላጅ የሆነ እንደሆነ የወንጀሉ ትልቅነት እየታየ ግርፋት ወይም ሞት ይፈረድበታል እንጂ በአንድ ወንጀል ሁለት ቅጣት አይፈረድበትም፡፡
የውጭ ሀገር ወንጀለኛ እንደሆነ ግን ቅጣቱ ግርፋት እንደሆነገርፈው እስራት ይጨምሩበታል፡፡ ቅጣቱ ሞት እንደሆነ ግን አስቀድመው ገርፈው በኋላ በመስቀል ወይም በሌላ መሣርያ ይገድሉታል፡፡…

ስለዚህ ቅዱስ ጴጥሮስንም እንደ ሥርዓታቸው አስቀድመው ገርፈው በኋላ ራሱን ወደ ታች እግሩን ወደ ላይ አድርገው ሰቅለው ገደሉት፡፡ የተሰቀለውም በሐምሌ 5 /68 ዓ.ም ነው፡፡

ከሞተም በኋላ መርቄሎስ የሚባለው ደቀ መዝሙሩ ከመስቀል አውርዶ እንደ ሀገሩ ልማድ ሬሳውን በወተትና በወይን አጥቦ ሽቱ ቀብቶ በነጭ ልብስ ገንዞ ማር በተመላ ሣጥን ውስጥ አግብቶ አሁን ዛሬ ቫቲካን በሚባለው ሥፍራ ቀበረው፡፡
በረከቱና ረድኤቱ አይለየን!
+++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++
ቅዱስ ጳውሎስና ኔሮን ቄሳር በማናቸውም ነገር የማይስማሙ አጥፊና ጠፊ ነበሩ፡፡ ኔሮን ቄሳር ክፉና ዐመጸኛ ነበር፤ ቅ/ጳውሎስ ግን ደግና ፈቃደኛ ነበር፡፡ ኔሮን ቄሳር ከሐዲና ጨለማ በቃኝ የማይልንፉግ የሰይጣን ማደርያ ነበር፤ ቅ/ጳውሎስ ግን ሃይማኖታዊና ብርሃን በቃኝ የሚል ቸር የመንፈስ ቅዱስ ማደርያ ነበር፡፡

እነዚህ ሁለቱ ተጻራሪዎች በተገናኙና በተያዩ ጊዜ አንዱ የአንዱን ነገር አያስተውለውም ነበር፡፡ ስለዚህ ቅ/ጳውሎስ ወደ ፍርድ ሸንጎ ከቀረበ በኋላ ይፈታ ወይም ይቀጣ ሳይባል ወደ ግዞት ቤት መለሱት፡፡

ነገር ግን በሮሜ ከተማ ቅ/ጳውሎስ አስቀድሞ ያሳመናቸው ክርስቲያኖች እየበዙ ትምህርታቸውም እየበዛ መሔዱ በቅ/ጳውሎስ ምክንያት መሆኑን ኔሮን ቄሳር ስለተረዳው ይልቁንም ከቤተ መንግሥቱ ሹሞች ወገን ብዙ ሰዎች በክርስቶስ ስለ አሳመነበት የቤሮን ቄሳር ቁጣው ተመለሰበትና ጳውሎስን እንደገና ወደ ፍርድ ሸንጎ አቅርቡት ብሎ

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል አራት!


      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ውድ ክርስቲያኖች! የእግዚአብሔር ፍጹም ሰላም ይብዛላችሁ! አሜን!
በክፍል ሦስት ትምህርታችን ወደ ስድስት የሚሆኑ ነጥቦችን አይተን ነበር፡፡ ለዛሬም ቸሩ አምላካችን በፈቀደልን መጠን ካቆምንበት እንቀጥላለን፡፡
1. መሥዋዕትን አንዴ (አንድ ጊዜ) ያቀረበ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ለኃጢአት ሥርየት የሚያቀርቡት መሥዋዕት ፍጹም ድኅነትን ስለማይሰጥ ዕለት ዕለት ይሠዉ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን አንድ ቀን ስለ ዓለም ሁሉ መዳን በቀራንዮ ላይ መሥዋዕት አድርጎ ባቀረበ ጊዜ የዓለምን ኃጢአት ስላስወገደ በእርሱ ያመነ ሁሉ ተረፈ ኃጢአት (የማይደመሰስ ኃጢአት) ስለማይኖርበት በየጊዜው ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ አያስፈልገውም፡፡ ዓለም ሁሉ በእርሱ ካመነ በዕለተ ዐርቡ መሥዋዕት ይድናል እንጂ ሌላ ተጨማሪ መሥዋዕት አይቀርብለትም፡፡ የኃጢአተኛ ተለዋጭ ሆኖ የቀረበው የመሥዋዕቱ በግ ክርስቶስ አንድ ነውና /ዕብ.7፡27-28/፡፡ ስለዚህ አንድ ጊዜ አምነን ተጠምቀን የክርስቶስ ማደርያ ከሆንን በኋላ ክፉ ሐሳብ ወደ ራሳችን ሰብስበን ወይም ደግሞ ሰው አገብሮን ተጋፍቶን በገቢር ብንበድል (ሃይማኖታችንን  ክደን ቆይተን ብንመለስ እንኳን) ዳግመኛ ንስሐ ገብተን እንመለሳለን እንጂ ከእንግዲህ ወዲህ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ ሁለተኛ ጥምቀት ሁለተኛ መሥዋዕት አይቀርብልንም፤ ወልደ እግዚአብሔርንም ዳግመኛ ተሰቀልልን መከራ ተቀበልልን የለምንለው አይደለም /ዕብ.10፡26/፡፡
2. በአብ ቀኝ የተቀመጠ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ወደ ምድራዊቱ ቅድስት ሥፍራ በዓመት አንድ ጊዜ በብዙ ፍርሐትና ረዐድ ይገቡ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እንዲህ አልገባም፡፡ ሐዋርያው፡- “ከተናገርነውም ዋና ነገሩ ይህ ነው፡፡ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፡፡ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት” እንዲል /ዕብ.8፡1-2/፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ እንደ ወረደ ግልጽ ነው /ዮሐ.3፡13/፡፡ ሆኖም ግን “ወረደ” የሚለው አገላለጽ ለምልዓተ መለኰቱ ወሰን ለሌለው ለመለኰታዊ ቃል የሚስማማ አይደለም፡፡ ሰው ሆኖ፣ ሥጋ ለብሶ፣ ባጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ ለድኅነተ ዓለም መገለጡን፤ ለሕማም፣ ለሞት፣ ለመሥዋዕትነት መምጣቱን የሚገልጽ እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ሲናገር፡- “ወልድ ዋሕድ እንደ መላእክት ቦታውን የለቀቀ አይደለም፤ በአንድ ፈቃድ ከአባቱ ጋር እያለ ነው እንጂ፡፡ ከአንዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ በተላከ ጊዜ እንደ መላእክት ቦታውን ለቆ የሄደ አይደለም፤ እነዚያ በተላኩ ጊዜ ቦታቸውን ለቀው ይሄዳሉና፡፡ በምልዓት ሳለ እንደ መላእክት ቦታውን ሳይለቅ ሥጋን ተዋሐደ እንጂ” ይላል /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.3፡153-158/፡፡ ልክ እንደዚሁ “ተቀመጠ” የሚለው ቃልም ሥራዉን መጨረሱን፣ ወደ ቀደመ ክብሩ መመለሱን፣ ድኅነተ ዓለም መፈጸሙን የሚያመለክት እንጂ እንደተናገርነው ለምልዓተ መለኰቱ ቦታ ተወስኖለት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንትም ይህን ሲያመሰጥሩት፡- “ጌታ ከምልዓተ መለኰቱ የተወሰነበት ወቅት ኑሮ መንበረ ክብሩን ተቆጣጠረ ወይም ከመለኰታዊ ክብሩ ተራቁቶ ኑሮ ወደ መለኰታዊ ክብሩ በተመለሰ ጊዜ መለኰታዊ ክብሩን ተቆጣጠረ ማለት ሳይሆን ሰውን ለማዳን ሰው ሆኖ ሰማያዊ ያልነበረውን (ክብር የለሽ የነበረውን) የሰውን ባሕርይ ማክበሩንና በእርሱ ክብር መክበራችን፣ በክብር ቦታ መቀመጣችን፣ የሰው ልጅ ሁሉ በክርስቶስ መክበሩን ነው” ይላሉ /ኤፌ.2፡6-7/፡፡ “በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለበጉ ይሁን” አሜን /ራዕ.5፡14/፡፡
3. በገዛ ደሙ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የገባ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉዩ ሊቀ ካህናት ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈን ለሚቃጠል መሥዋዕትም አውራ በግ ይዞ የዚህ ዓለም (አፍአዊ) ወደ ሆነችው መቅደስ ይገባ ነበር፡፡ አገልግሎቱም ሁሉ ምድራዊ ዓለማዊ ነበር፤ ሥጋን እንጂ ነፍስን መቀደስ የማይቻለው ነበር /ዘሌ.16፡3/፡፡ እንደ ወንበዴ ከወንበዴዎች ጋር የተሰቀለው፣ የተናቀው፣ ገሊላዊ፣ የዓለምንም ኃጢአት ያስወገደው የእግዚአብሔር በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እንደተጻፈ በደመ በግዕ በደመ ላህም ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የገባ አይደለም፡፡ ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ ተወካፌ መሥዋዕት (መሥዋዕት ተቀባይ)፣ ራሱ ይቅር ባይ ሊቀ ካህናት አስታራቂ መሥዋዕት አቅራቢ ሆኖ ገባ እንጂ /ዮሐ.1፡29, St. Augustine, On Ps. 65./፡፡ ሐዋርያው፡- “ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን የዘለዓለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም” እንዲል /ዕብ.9፡11-13/፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጠቀም ብሎ ሳይሆን ቅዱሳንን ሊያገለግል ደሙን ይዞ የገባባት ቅድስተ ቅዱሳን ማን ናት? “ኢየሱስ ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ በምትበልጠውና በምትሻለው በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንጂ በዘር በሩካቤ ባልተከፈለች  /ማቴ.1፡20/ በሥጋው መሥዋዕት በኵል /ዕብ.10፡20/ ስለ እኛ ይታይ ዘንድ፣ እንደ አይሁድ ሐሳብ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ዕቅድ  መስቀል ላይ በሠዋው አንድ መሥዋዕት ከራሱ ከባሕርይ አባቱና ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያስታርቀን ዘንድ የገባባት ቅድስተ ቅዱሳን እዝነ አብ (የአብ ጀሮ) ገጸ አብ (የአብ ፊት) ናት” /St.John Chrysostom, Homily on the Epistle Of Hebrews, Hom.15፣ ዕብ.9፡24/፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው ጌታችን ወደ እዝነ አብ ወደ ገጸ አብ አቀረበን ስንል (በሥላሴ ዘንድ ተከፍሎ ስለሌለ) የታረቅነው ከሥላሴ ጋር መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ መሥዋዕት ተቀባዩ አብ ብቻ እንዳልሆነ የታወቀ የተረዳ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ሊቃውንትም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ይህን ክፍል በተረጐሙበት አንቀጽ፡- “ለምትመጣው ሕግ ለወንጌል ሊቀ ካህናት ሆኖ የመጣው ክርስቶስ ግን በምክንያተ ዘርዕ ያይደለ እንበለ ዘርዕ ወደተገኘች ወደ ደብተራ ርእሱ፣ በሰው ፈቃድ ያይደለ በእርሱ ፈቃድ ወደ ተተከለች ደብተራ መስቀል ደመ ላህም፣ ደመ ጠሊን ይዞ የገባ አይደለም፤ ደሙን ይዞ አንድ ጊዜ ወደ እዝነ አብ ወደ ገጸ አብ ገባ እንጂ” ብለዋል /የቅዱስ ጳውሎስ መጽሐፍ ንባቡ ከነትርጓሜው፣ ገጽ 441/፡፡ ተወዳጆች ሆይ! አንድ ፍጹም ልንረሳው የማይገባ መሠረታዊ ነገር አለ፡፡ እርሱም ምን እንደሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይነግረናል፡- “የጌታችን አገልግሎቱ እዚህ ምድር በመስቀል ላይ የተፈጸመ ቢሆንም እንደ ቀደሙት ሊቃነ ካህናት ምድራዊ አገልግሎት አልነበረም፤ ሰማያዊ እንጂ፡፡ ለምን ቢሉ ምእመናን በእርሱ አምነን መጠመቅን ገንዘብ አድርገን የሰማያውያን ሥራ እየሠራን የእርሱ ልጆች እንሆናለንና፡፡ ሐሳባችንም ሀገራችንም መንግሥተ ሰማያት ነውና፡፡  ምስጋናችንም ከመላእክት ጋር ኅብረት አንድነት ያለው ሰማያዊ ነውና፡፡ መሥዋዕታችንም እንጨት ማግዶ እሳት አንድዶ የሚቀርብ የላም የበግ ደም ሳይሆን ሰማያዊው መሥዋዕት (ክርስቶስ) ነውና፡፡ ሕጉም (ወንጌሉም) ክህነቱም ሰማያዊ ነውና፡፡ መሥዋዕታችን እንደ ቀደመው ኪዳን መሥዋዕት አመድና ጢስ እንዲሁም መዓዛ ሆኖ የሚቀር ሳይሆን ንጽሐ ሥጋ ንጽሐ ነፍስ የሚሆን ክብር ነውና፡፡ ይህን የምናከናውንበት ሥርዓተ ቅዳሴአችንም ሰማያዊ ነውና” /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.14፡58-77/፡፡ የስነ መለኰት ምሁራንም እንዲህ ሲሉ ይህን የቅዱሱ ሐሳብ ያጐለሙሱታል፡- “ምንም እንኳን በምድራዊቷ ድንኳን (ቅድስት ቤተ ክርስቲያን) ብንሆንም ክርስቲያኖች ወደዚሁ ቅዱስ መሥዋዕት (ወደ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ) በምንቀርብበት ሰዓት ወደ ቅድስተ ቅዱሳን እንገባለን፤ ማንነታችን ከጊዜና ከቦታ ቀመር ውጪ /Kairos/ ይሆናል፡፡ እዚህ ሆነን የመንግሥተ ሰማያትን ኑሮ እንለማመዳለን፡፡ ከመለኰታዊ ባሕርይ ተካፋይ እንሆናለን፡፡ ትላንት፣ ዛሬና ነገ ከሚለው ማንነታችን /Chronos/ ወጥተን “አሁን” /Kairos/ ወደሚለው ማንነታችን እንቀየራለን፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ትላንት፣ ዛሬ፣ ነገ የሚሉ አገላለጾች የሉምና፡፡ ወደ ፊት ደግሞ (ዓለም ሲያልፍ) ከጊዜ መፈራረቅ ውጪ ሆነን ለዘለዓለሙ ወደዚሁ ማንነታችን (ወደ Kairos) እንለወጣለን፡፡ ወደ ቅዱስ ቁርባን ስንቀርብ ከጠብና ከበቀል የራቅን እንሁን የሚባልበት ምሥጢርም ማንነታችን ከዚህ ምድር ስለሚለይ ነው፡፡ በሰማያዊ ሕይወት ጠብና በቀል የለምና፡፡ እነዚህን ሳናስወግድ ስንቀርብ ግን ያው እላይ መሆናችን ቀርቶ እታች ነን ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን የተቀበልን መስሎንም ሳንቀበል እንቀራለን፡፡ ሳይገባን ይህን እንጀራ ስለበላን ወይም የጌታን ጽዋ ስለጠጣንም ዕዳ ይሆንብናል” /1ቆሮ.11፡27/፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! ሳምንት ይቀጥላል!!

Saturday, July 7, 2012

መጥምቁ ዮሐንስ እና አገልግሎቱ!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

   የታሪክ መዛግብት እንደሚናገሩት አንድ ንጉሥ ወደ አንድ አከባቢ ከመሄዱ በፊት መንገዱን ያዘጋጁ ዘንድ አስቀድሞ መልእክተኞችን ይልካል፡፡ የፍጥረታት ሁሉ ጌታ እና ንጉሥ የሆነው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም እኛን ለማዳን ወደዚህ ዓለም ከመምጣቱ በፊት መንገዱን ይጠርጉ ዘንድ ብዙ ነቢያትን ልኳል፡፡ መጥምቁ ዮሐንስም በበረሐ ተገድዶ ሳይሆን የጌታ ፍቅር አስገድዶት ላንቃው እስኪሰነጠቅ ድረስ እየጮኸ መልእክተኛ ሆኖ የመጣ ታላቅ ነቢይም ሐዋርያም ነው፡፡ ለዚህም ነው ወንጌላዊው፡- “እነሆ፥ መንገድህን የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ ተብሎ በነቢዩ በኢሳይያስ እንደ ተጻፈያለው /ማር.12-3/፡፡

    ወንጌላዊው ስለዚሁ የጌታ መልእክተኛ የተነገሩትን ሁለቱም ትንቢቶች እያነሣ ይናገራል /ሚል.31 ኢሳ.403/፡፡ ሚልክያስየጌታ መልእክተኛብሎ የጠራው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለድኅነተ ዓለም ከመምጣቱ በፊት ሕዝቡን በንስሐ መንገድ እየጠረገ ስለ ነበረ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ጌታን ለመጀመርያ ጊዜ ያየው በሥጋ ማርያም ሳይሆን በዐይነ እምነት ነበረ፡፡ ምንም እንኳን በእናቱ ማሕፀን ውስጥ የነበረ ቢሆንም ጌታውን በዐይነ እምነት ሲመለከተው ግን በደስታ ዘሏል /ሉቃ.144/፡፡

   ጠርጡለስ የተባለ የሁለተኛው ክፍለ ዘመን ምሁርመዝሙረኛው ዳዊት፡- ለቀባሁትም ሰው መብራትን አዘጋጃለሁ እንዳለ መጥምቁ ዮሐንስ መልእክተኛ ብቻ ሳይሆን መብራትም ነበረብሏል፡፡ በእርግጥም መስማትን ለሰሙት ወገኖች የሚያበራ ፋና ነበረ፡፡

   “ወንጌላዊውኢሳይያስም ዮሐንስንበምድረ በዳ የሚጮህ ድምጽብሎታል፡፡ እርሱ አዳኙን ክርስቶስ ለመግለጥ እንደ ተላከ የምሕረት መልአክ፣ እንደ አንበሳ በበረሐ እየጮኸ በኃጢአት የጠነከረውን ልባችንን ይሰብር ዘንድ የመጣ መልእክተኛ ነውና፡፡ ሰውነታችንን መልእክተኛ ለሆነለት ለእግዚአብሔር በግ ለክርስቶስ ማኅደር እንድንሆን ያዘጋጅ ዘንድ የመጣ ነብይ ነውና፡፡

   “ዓምደ ተዋሕዶየተባለው ታለቁ ሊቅ ቅዱስ ቄርሎስምመጥምቁ ዮሐንስ ከንጋቱ ኰከብ በፊት የነበረ ፀሐይይሏል፡፡ ምክንያቱም ዮሐንስ ፀሐየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ እስኪመጣ ድረስ የሚያበራ ፋና ነበረና፡፡ በጨለማ ውስጥ ይመላለሱ ለነበሩት ሁሉ ወደ እውነተኛው ብርሃን ይደርሱ ዘንድ ያዘጋጅ ነበረና፡፡

   ዮሐንስ ያዘጋጀው የነበረው ጥርግያ የጌታን ወንጌል ነበረ፡፡ የትምህርቱ መሠረታዊ ዓላማም እያንዳንዱ ሰው የንስሐ ፍሬ እንዲያፈራ ማድረግ ነበር፡፡ የንስሐ ፍሬ ሲባልም የሠሩትን ኃጢአት መተው ብቻ ሳይሆን ፍሬም ጭምር ማፍራት ነው፡፡ ለምሳሌ፡-በሰረቁበት እጅ አለመስረቅ ብቻ ሳይሆን በዚያ ወዶ መስጠት፣ በዘፈኑበት ከንፈር ዘፈንን መተው ብቻ ሳይሆን በዚያ መዘመር፣ አመንዝረን እንደ ሆነም ይኸን መተው ብቻ ሳይሆን ከሕጋዊ ሚስታችንም ቢሆን ለተወሰነ ጊዜአት መቆጠብን የመሳሰለ ሁሉ ነው፡፡

    መጥምቁ ዮሐንስ በቃሉ ብቻ ሳይሆን በልብሱም ጭምር ይሰብክ ነበር፡፡ ምግባራችን እንደ ሞተ እንስሳ ቁርበት ጠፍር፣ ኃጢአታችንም እንደ ግመል ጠጉር ለበዛብን ለእኛ ክብር ይግባውና የእግዚአብሔር በግ እርሱ ክርስቶስ ይቆስልልን ዘንድ እንደ መጣ ይመሰክር ነበር፡፡

   እኛ ሁላችን ወደ ገዛ መንገዳችን ስናዘነብል፤ በከንቱም የማይበላውን በልተን ስንሞት እርሱ 30 ብር ተሸጦ እኛን ግን በማይተመን ዋጋ ገዝቶ ከዓለቱ ማር በልተን እንደሚያጠግበን ያውጅ ነበረ /መዝ.8116/፡፡

የመጥምቁ ረድኤትና በረከት አይለየን! የንስሐ ፍሬም እንድናፈራ ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን አሜን!

FeedBurner FeedCount