Wednesday, July 11, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል አራት!


      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ውድ ክርስቲያኖች! የእግዚአብሔር ፍጹም ሰላም ይብዛላችሁ! አሜን!
በክፍል ሦስት ትምህርታችን ወደ ስድስት የሚሆኑ ነጥቦችን አይተን ነበር፡፡ ለዛሬም ቸሩ አምላካችን በፈቀደልን መጠን ካቆምንበት እንቀጥላለን፡፡
1. መሥዋዕትን አንዴ (አንድ ጊዜ) ያቀረበ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ለኃጢአት ሥርየት የሚያቀርቡት መሥዋዕት ፍጹም ድኅነትን ስለማይሰጥ ዕለት ዕለት ይሠዉ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን አንድ ቀን ስለ ዓለም ሁሉ መዳን በቀራንዮ ላይ መሥዋዕት አድርጎ ባቀረበ ጊዜ የዓለምን ኃጢአት ስላስወገደ በእርሱ ያመነ ሁሉ ተረፈ ኃጢአት (የማይደመሰስ ኃጢአት) ስለማይኖርበት በየጊዜው ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ አያስፈልገውም፡፡ ዓለም ሁሉ በእርሱ ካመነ በዕለተ ዐርቡ መሥዋዕት ይድናል እንጂ ሌላ ተጨማሪ መሥዋዕት አይቀርብለትም፡፡ የኃጢአተኛ ተለዋጭ ሆኖ የቀረበው የመሥዋዕቱ በግ ክርስቶስ አንድ ነውና /ዕብ.7፡27-28/፡፡ ስለዚህ አንድ ጊዜ አምነን ተጠምቀን የክርስቶስ ማደርያ ከሆንን በኋላ ክፉ ሐሳብ ወደ ራሳችን ሰብስበን ወይም ደግሞ ሰው አገብሮን ተጋፍቶን በገቢር ብንበድል (ሃይማኖታችንን  ክደን ቆይተን ብንመለስ እንኳን) ዳግመኛ ንስሐ ገብተን እንመለሳለን እንጂ ከእንግዲህ ወዲህ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ ሁለተኛ ጥምቀት ሁለተኛ መሥዋዕት አይቀርብልንም፤ ወልደ እግዚአብሔርንም ዳግመኛ ተሰቀልልን መከራ ተቀበልልን የለምንለው አይደለም /ዕብ.10፡26/፡፡
2. በአብ ቀኝ የተቀመጠ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ወደ ምድራዊቱ ቅድስት ሥፍራ በዓመት አንድ ጊዜ በብዙ ፍርሐትና ረዐድ ይገቡ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እንዲህ አልገባም፡፡ ሐዋርያው፡- “ከተናገርነውም ዋና ነገሩ ይህ ነው፡፡ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፡፡ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት” እንዲል /ዕብ.8፡1-2/፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ እንደ ወረደ ግልጽ ነው /ዮሐ.3፡13/፡፡ ሆኖም ግን “ወረደ” የሚለው አገላለጽ ለምልዓተ መለኰቱ ወሰን ለሌለው ለመለኰታዊ ቃል የሚስማማ አይደለም፡፡ ሰው ሆኖ፣ ሥጋ ለብሶ፣ ባጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ ለድኅነተ ዓለም መገለጡን፤ ለሕማም፣ ለሞት፣ ለመሥዋዕትነት መምጣቱን የሚገልጽ እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ሲናገር፡- “ወልድ ዋሕድ እንደ መላእክት ቦታውን የለቀቀ አይደለም፤ በአንድ ፈቃድ ከአባቱ ጋር እያለ ነው እንጂ፡፡ ከአንዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ በተላከ ጊዜ እንደ መላእክት ቦታውን ለቆ የሄደ አይደለም፤ እነዚያ በተላኩ ጊዜ ቦታቸውን ለቀው ይሄዳሉና፡፡ በምልዓት ሳለ እንደ መላእክት ቦታውን ሳይለቅ ሥጋን ተዋሐደ እንጂ” ይላል /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.3፡153-158/፡፡ ልክ እንደዚሁ “ተቀመጠ” የሚለው ቃልም ሥራዉን መጨረሱን፣ ወደ ቀደመ ክብሩ መመለሱን፣ ድኅነተ ዓለም መፈጸሙን የሚያመለክት እንጂ እንደተናገርነው ለምልዓተ መለኰቱ ቦታ ተወስኖለት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንትም ይህን ሲያመሰጥሩት፡- “ጌታ ከምልዓተ መለኰቱ የተወሰነበት ወቅት ኑሮ መንበረ ክብሩን ተቆጣጠረ ወይም ከመለኰታዊ ክብሩ ተራቁቶ ኑሮ ወደ መለኰታዊ ክብሩ በተመለሰ ጊዜ መለኰታዊ ክብሩን ተቆጣጠረ ማለት ሳይሆን ሰውን ለማዳን ሰው ሆኖ ሰማያዊ ያልነበረውን (ክብር የለሽ የነበረውን) የሰውን ባሕርይ ማክበሩንና በእርሱ ክብር መክበራችን፣ በክብር ቦታ መቀመጣችን፣ የሰው ልጅ ሁሉ በክርስቶስ መክበሩን ነው” ይላሉ /ኤፌ.2፡6-7/፡፡ “በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለበጉ ይሁን” አሜን /ራዕ.5፡14/፡፡
3. በገዛ ደሙ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የገባ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉዩ ሊቀ ካህናት ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈን ለሚቃጠል መሥዋዕትም አውራ በግ ይዞ የዚህ ዓለም (አፍአዊ) ወደ ሆነችው መቅደስ ይገባ ነበር፡፡ አገልግሎቱም ሁሉ ምድራዊ ዓለማዊ ነበር፤ ሥጋን እንጂ ነፍስን መቀደስ የማይቻለው ነበር /ዘሌ.16፡3/፡፡ እንደ ወንበዴ ከወንበዴዎች ጋር የተሰቀለው፣ የተናቀው፣ ገሊላዊ፣ የዓለምንም ኃጢአት ያስወገደው የእግዚአብሔር በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እንደተጻፈ በደመ በግዕ በደመ ላህም ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የገባ አይደለም፡፡ ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ ተወካፌ መሥዋዕት (መሥዋዕት ተቀባይ)፣ ራሱ ይቅር ባይ ሊቀ ካህናት አስታራቂ መሥዋዕት አቅራቢ ሆኖ ገባ እንጂ /ዮሐ.1፡29, St. Augustine, On Ps. 65./፡፡ ሐዋርያው፡- “ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን የዘለዓለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም” እንዲል /ዕብ.9፡11-13/፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጠቀም ብሎ ሳይሆን ቅዱሳንን ሊያገለግል ደሙን ይዞ የገባባት ቅድስተ ቅዱሳን ማን ናት? “ኢየሱስ ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ በምትበልጠውና በምትሻለው በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንጂ በዘር በሩካቤ ባልተከፈለች  /ማቴ.1፡20/ በሥጋው መሥዋዕት በኵል /ዕብ.10፡20/ ስለ እኛ ይታይ ዘንድ፣ እንደ አይሁድ ሐሳብ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ዕቅድ  መስቀል ላይ በሠዋው አንድ መሥዋዕት ከራሱ ከባሕርይ አባቱና ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያስታርቀን ዘንድ የገባባት ቅድስተ ቅዱሳን እዝነ አብ (የአብ ጀሮ) ገጸ አብ (የአብ ፊት) ናት” /St.John Chrysostom, Homily on the Epistle Of Hebrews, Hom.15፣ ዕብ.9፡24/፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው ጌታችን ወደ እዝነ አብ ወደ ገጸ አብ አቀረበን ስንል (በሥላሴ ዘንድ ተከፍሎ ስለሌለ) የታረቅነው ከሥላሴ ጋር መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ መሥዋዕት ተቀባዩ አብ ብቻ እንዳልሆነ የታወቀ የተረዳ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ሊቃውንትም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ይህን ክፍል በተረጐሙበት አንቀጽ፡- “ለምትመጣው ሕግ ለወንጌል ሊቀ ካህናት ሆኖ የመጣው ክርስቶስ ግን በምክንያተ ዘርዕ ያይደለ እንበለ ዘርዕ ወደተገኘች ወደ ደብተራ ርእሱ፣ በሰው ፈቃድ ያይደለ በእርሱ ፈቃድ ወደ ተተከለች ደብተራ መስቀል ደመ ላህም፣ ደመ ጠሊን ይዞ የገባ አይደለም፤ ደሙን ይዞ አንድ ጊዜ ወደ እዝነ አብ ወደ ገጸ አብ ገባ እንጂ” ብለዋል /የቅዱስ ጳውሎስ መጽሐፍ ንባቡ ከነትርጓሜው፣ ገጽ 441/፡፡ ተወዳጆች ሆይ! አንድ ፍጹም ልንረሳው የማይገባ መሠረታዊ ነገር አለ፡፡ እርሱም ምን እንደሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይነግረናል፡- “የጌታችን አገልግሎቱ እዚህ ምድር በመስቀል ላይ የተፈጸመ ቢሆንም እንደ ቀደሙት ሊቃነ ካህናት ምድራዊ አገልግሎት አልነበረም፤ ሰማያዊ እንጂ፡፡ ለምን ቢሉ ምእመናን በእርሱ አምነን መጠመቅን ገንዘብ አድርገን የሰማያውያን ሥራ እየሠራን የእርሱ ልጆች እንሆናለንና፡፡ ሐሳባችንም ሀገራችንም መንግሥተ ሰማያት ነውና፡፡  ምስጋናችንም ከመላእክት ጋር ኅብረት አንድነት ያለው ሰማያዊ ነውና፡፡ መሥዋዕታችንም እንጨት ማግዶ እሳት አንድዶ የሚቀርብ የላም የበግ ደም ሳይሆን ሰማያዊው መሥዋዕት (ክርስቶስ) ነውና፡፡ ሕጉም (ወንጌሉም) ክህነቱም ሰማያዊ ነውና፡፡ መሥዋዕታችን እንደ ቀደመው ኪዳን መሥዋዕት አመድና ጢስ እንዲሁም መዓዛ ሆኖ የሚቀር ሳይሆን ንጽሐ ሥጋ ንጽሐ ነፍስ የሚሆን ክብር ነውና፡፡ ይህን የምናከናውንበት ሥርዓተ ቅዳሴአችንም ሰማያዊ ነውና” /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.14፡58-77/፡፡ የስነ መለኰት ምሁራንም እንዲህ ሲሉ ይህን የቅዱሱ ሐሳብ ያጐለሙሱታል፡- “ምንም እንኳን በምድራዊቷ ድንኳን (ቅድስት ቤተ ክርስቲያን) ብንሆንም ክርስቲያኖች ወደዚሁ ቅዱስ መሥዋዕት (ወደ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ) በምንቀርብበት ሰዓት ወደ ቅድስተ ቅዱሳን እንገባለን፤ ማንነታችን ከጊዜና ከቦታ ቀመር ውጪ /Kairos/ ይሆናል፡፡ እዚህ ሆነን የመንግሥተ ሰማያትን ኑሮ እንለማመዳለን፡፡ ከመለኰታዊ ባሕርይ ተካፋይ እንሆናለን፡፡ ትላንት፣ ዛሬና ነገ ከሚለው ማንነታችን /Chronos/ ወጥተን “አሁን” /Kairos/ ወደሚለው ማንነታችን እንቀየራለን፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ትላንት፣ ዛሬ፣ ነገ የሚሉ አገላለጾች የሉምና፡፡ ወደ ፊት ደግሞ (ዓለም ሲያልፍ) ከጊዜ መፈራረቅ ውጪ ሆነን ለዘለዓለሙ ወደዚሁ ማንነታችን (ወደ Kairos) እንለወጣለን፡፡ ወደ ቅዱስ ቁርባን ስንቀርብ ከጠብና ከበቀል የራቅን እንሁን የሚባልበት ምሥጢርም ማንነታችን ከዚህ ምድር ስለሚለይ ነው፡፡ በሰማያዊ ሕይወት ጠብና በቀል የለምና፡፡ እነዚህን ሳናስወግድ ስንቀርብ ግን ያው እላይ መሆናችን ቀርቶ እታች ነን ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን የተቀበልን መስሎንም ሳንቀበል እንቀራለን፡፡ ሳይገባን ይህን እንጀራ ስለበላን ወይም የጌታን ጽዋ ስለጠጣንም ዕዳ ይሆንብናል” /1ቆሮ.11፡27/፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! ሳምንት ይቀጥላል!!

7 comments:

  1. ተመልክቼዋለሁ ወድጄዋለሁም ጥሩ አገላለጽ ነው፡፡ ቃለ ሕይወት ያሰማንኝ ወንድሜ፡፡

    ReplyDelete
  2. Ejig astemari new, bizu tiyakewochin melsolignal! Qale hiwot yasemalin!!

    ReplyDelete
  3. wow, Qale hiwot yasemalin!!
    AMLAK EJIHN YABERTA ,TIBEBN ,MASTEWALN YCHEMR!!!!!!!!!

    ReplyDelete
  4. ቃለ ህይወት ያሰማልን

    ReplyDelete

FeedBurner FeedCount